Sunday, December 18, 2022

በቅርቡ የሚሆነውን ልንገርህ!! ዳግማዊ ጉዱ ካሣ Ethiopian Semay 12/18/22

 

በቅርቡ የሚሆነውን ልንገርህ!!

ዳግማዊ ጉዱ ካሣ

Ethiopian Semay

12/18/22


ሰው ነህና ከሰው ጋር መጣላትህ አይቀርም፡፡ የለዬለት ጠብ ውስጥ ላትገባ ብትችልም እንኳን ከጓደኛና ከዘመድ ወይንም ከመሥሪያ ቤት ባልደረባህ ጋር መቀያየምህና መኮራረፍህ ለተወሰነ ጊዜም ቢሆን ፊት መጠቋቆርህ የሚጠበቅ ነው፡፡ መቼም መልኣክ አይደለህም፡፡ ስትጣላ ደግሞ አንዳንዱ ጠብ ሊያስፈግግህ ወይም ሊያስቅህ፣ አንዳንዱ ደግሞ ከምር ሊያሳዝንህና ሊያሰቆጣህ ይችላል፡፡

ጠቦች ዓይነታቸው ብዙ ነው፡፡ አንዳንዶቹን ገፍተህ ትሄድባቸዋለህ፤ አንዳንዶቹ ብትሸሻቸውም ገፍተው ይመጡብሃል፡፡ ችግር ነው፡፡ ገፍተህ የምትሄድባቸው ጠቦች ጉልበትህን ፈትሸህ እንደምታሸንፍ ስታውቅና ምናልባትም በቂ ምክንያት ሲኖርህ ነው፡፡ ገፍተው የሚመጡብህ ግን አያድርስብህ እንጂ የተለዬ ባሕርይ ያላቸውና ጉልበትህንና ጥበብህን ትግስትህንም የሚፈትሹ ናቸው፡፡

 ኢትዮጵያውያንን በተለይም አማራን የገጠመው ጠብ ሲፈተሸ አስቂኝም አሳዛኝም ነው፡፡ ከት ብለን እንዳንስቅ የጠቡ መንስኤ ከድራማዊነቱ የተነሣ አስቂኝ ይሁን እንጂ ውጤቱ የሰውን ሕይወት የሚቀጥፍና ሀብት ንብረትን በእሳት የሚያጋይ፣ በዘረፋና በቅሚያም የዘመናት ጥሪትን የሚያሳጣ እጅግ አደገኛ ጠብ በመሆኑ መሣቅ ይከብዳል፡፡ በሀዘን ድንኳን ጥለን እንዳንቀመጥና እንዳናዝን ደግሞ የጠቡ ቧልታይ ድንቃይ ተፈጥሮ ዕድል አይሰጠንም፡፡ ስለዚህ እንደ እያነቡ እስክስታ ዓይነት ሆኖብን ተቸግረናል፡፡ አያድርስ ነው፡፡ በዚያ ላይ አማራ ነኝ የሚለው የቀድሞ ትግርኛ የአሁን ኦሮምኛ ተናጋሪው ብአዴን ጉዳይ ሲጨመርበት የገጠመን ነገር ፍቺ አልባ ዕንቆቅልሽ ይሆንብናል፡፡ ያለንበት ሀገራዊና ማኅበራዊ ቀውስ ለዘፋኝም ለአልቃሽም አስቸጋሪ ነው፡፡ ዓለም ብትፈተሸ እንደኛ ያለ ችግር የገጠመው አንድም ሀገር የለም፡፡ ለኛ እንደተሰጠን መሪ ማንም አልተሰጠም - ልብ አድርግ፤ “ለእንደዚህ ያለ ሀገርና ለእንደዚህ ያለ ድርጅት ስሰልል ነበር” ብሎ በመናገር በሀገር ክህደት ሞት የሚያስቀጣ ወንጀል መሥራቱን በግልጽ የሚያውጅ የሀገር መሪ በየትኛውም የሰው ልጅ ታሪክ አልተመዘገበም፡፡ ይህን መሰሉ ትዕቢት አይሉት ድንቁርና በለየለት የአጋንንቱ ሰፈርም የለም፡፡ ፍጹማዊ ድንቁርና ማለት እንግዲህ እንደዚህ ነው፤ ድምበር የለሽ ትምክህት ይሉሃል ይሄ ነው - ግን ቀን አለው፤ ሲከፍላት ታያለህ!

አቢይ ሸኔ የተባለ የመንግሥት ቅልብ ሰው አራጅ ከወለጋ ደምቢዶሎ እስከአዲስ አበባ ዙሪያና እስከአራት ኪሎ ቤተ መንግሥት መሽጎ ወገናችንን በተለይም አማራን እያረደ ባለበት ሁኔታ አርፎ የተቀመጠውንና ለሀገሩ ዝመት በተባለበት ጊዜ ሁሉ ካለስንቅና ትጥቅ እየዘመተ ከፊትም ከጀርባውም በሚተኮስበት የጠላትና የወዳጅ መሳይ መሠሪ ጥይት ውድ ሕይወቱን የሚገብረውን ፋኖ በጽንፈኝነት በመክሰስ ለእስርና ለሞት ሲዳርጉት ማየት ከትያትሮች ሁሉ እጅግ የተለዬ ትራጄዲ ተውኔት ነው፡፡ ለአዲስ አበባ የተመሠረተ የክልል 14 መንግሥት ወንበሩን በ“የዘሬን ብተው ያንዘርዝረኝ” ህገ አራዊት ተመርቶ ለአክራሪ ኦሮሞ ሲያስረክብና የሌላ ክልል ባንዲራ አዲስ አበባ ላይ እንዲውለበለብ፣ የአዲስ አበባን ሕዝብ ከፍ ዝቅ አድርጎ የሚሳደብ የሌላ ክልል መዝሙር በአዲስ አበባ ተማሪዎች እንዲዘመር በኃይል ማስገደድና ተማሪንና ንጹሕ ዜጋን እያሰሩ መደብደብ፣ ማሰቃየትና መግደል ከተውኔቶች ሁሉ በእጅጉ የሚለይ አስቂኝ፣ አስገራሚና አሳዛኝም የሆነ አሳፋሪ ድርሰት ነው፡፡ በውነቱ በወደፊቱ የአብሮነት ታሪካችን ኦሮሞ በነዚህ ልጆች ምን ያህል አንገቱን እንደሚደፋ ከአሁኑ ሳስበው እኔም የሀፍረቱ ተጋሪ ሆኜ የሚሰማኝ ያህል ከወዲሁ እሳቀቃለሁ፡፡ ለአዲስ አበባ ተብሎ የተመረጠ የመንግሥት ባለሥልጣንና የምክር ቤት አባል የቆመበትን ዓላማ ስቶ የመኪናን ታርጋና የሌላውንም የመንግሥት መሥሪያ ቤት ሁሉ ወደ “ኦሮ” በመለወጥ አዲስ አበቤን ባይተዋር ማድረግ ስም የሌለው ድንቁርናና ነገን ያለመረዳት ድድብና ነው፡፡ ከቦሌ እስከ ባሌ የሚገኙ መሥሪያ ቤቶችን ሁሉ በኬኛ ፖለቲካ ጠቅልሎ ሌሎችን ጎሣዎች ሙልጭ ማውጣት ምን የሚሉት የዕውቀት ባዶነት እንደሆነ ፈጣሪ ይወቀው፡፡ በዚህ በያዙት መንገድ ሰማንያ ስድስቱን ነገድና ብሔር በአምስት ዓመታት ጊዜ ውስጥ ሳይወድ በግዱ - በዱላና በጥይት - ወደ ኦሮሞነት መቀየር እንደሚችሉ ማመናቸው በእጅጉ ይገርመኛል፡፡ ሰው መሆናቸውን ክፉኛ የምጠራጠረው ለዚህ ነው፡፡ አሁን ያለንበት ሁኔታ እንዳንስቅም እንዳናለቅስም የሚከለክል ድንግርግር ያለ መቼት ውስጥ ከቶናል፡፡ በርግጥ እነዚህ ሰዎች ሰዎች ናቸው ወይንስ ዐውሬዎች እያልን ነው፡፡ ሰዎች እንዳንላቸው የሰው ጠባይ አንድም የላቸውም፡፡ ዐውሬ እንዳንላቸው ብዙ ዐውሬዎች እንደነዚህኞቹ መረን አይለቁም፤ ተፈጥሯቸውንም አይስቱም፡፡ እነዚህኞቹ ግን ከበፊተኞቹ ወያኔዎችም ሆነ ከሌላው የእንስሳት ዓለም ይለያሉ፡፡

ለሀብትና ለገንዘብ መጓጓት ዱሮም ያለ ነው፡፡ ለቤትና ለንብረት መንሰፍሰፍ ጥንትም የነበረ ነው፡፡ ነገር ግን ገንዘብም ሆነ ሀብትና ንብረት የፈለግኸውን ያህል አፍቅር እንጂ ልክ እንደሸመልስና አቢይ ግሪሣ በጠራራ ፀሐይ የዜጎችን ጥሪት እየቀማህና እየገደልክ የምታራምደው የሀብትና የሥልጣን ክምችት የትም እንደማያደርስ መረዳት ይገባል፡፡ በኑሮ ውድነት ሕዝብን ማስለቀሱም ገደብ ቢበጅለት ቅድሚያ ተጠቃሚው አሻጥረኛውና ሙሰኛው ባለሥልጣን ነው፡፡ እኛስ የማንለምደው ችግር የለም፤ ጤፍ ስድስት ሽህ ቀርቶ ስልሳ ሽህ ብር ቢገባ ደንታ የሌለው ሕዝብና መንግሥት የመፈጠሩ ምሥጢር ኢትዮጵያ ውስጥ መንግሥትን ገርስሶ የሚጥለው ዕንባና በግፍ የሚፈስ ደም እንጂ መሪር አገዛዝን በጠበንጃ ታግሎ የሚጥል ሕዝባዊ እንቅስቃሴ አለመኖሩ ስለሚታወቅ ነው፡፡ ግን ደግነቱ ሁሉም የሥራውን ያገኛል፡፡ “ትዕቢተኛው መንጌ ከየት ወዴት ወርዶ ተፈጠፈጠ? አሁንስ የት ነው ያለው? ትዕቢተኛው መለስ አሁን የት ነው ያለው? አስመሳዩ፣ ዐረመኔውና ውሸታሙ ማሙሽ አቢይ አህመድስ ነገ የት ይገባል? ምንስ ይደርስበታል?” ብሎ መጠየቅ ብልኅነት ነው፡፡ የአቢይን መጨረሻ እርሱና መሰሎቹ ባያውቁት እኛ ጠንቅቀን እናውቃለን፡፡ የርሱ መጨረሻ ከቀደሙትም ይከፋል፡፡

አንድ ነገር ልንገርህማ፡፡ አንድ ሰው  ባስኬቶ ከሚባል የሙዝ ሀገር ሙዝ ገዝቶ በራሱ የጭነት መኪና ያመጣል፡፡ አንዱን ኪሎ በስድስት ብር፡፡ ሰሞኑን ነው ታዲያ፡፡ ገዝቶ ያመጣልህና ልሽጥ ብሎ አዲስ አበባ ላይ ሲሞክር የሙሰኞቹ ቁንጮ - ማን እንደሆነ አላውቅም - ስልክ ይደውልለትና “አርፈህ ትቀመጥ እንደሆነ ተቀመጥ! እሱን ያመጣሃውንም ሙዝ አምጣና ለኛ ሽጥ፡፡ ራሴው እሸጣለሁ ብትል እንገድልሃለን፤ መኪናህንም እናጋይልሃለን” ብለው አስፈራሩት፡፡ እርሱም መኖርን ይፈልጋልና ያመጣውን ሙዝ ለነሱ ኪሎውን በአምስት ብር በርካሽ ሸጦ ሥራ ቀየረ፡፡ አንድ ሌላ ሰው ደግሞ አቮካዶ ኪሎውን በ3 ብር አምጥቶ በርካሽ ሊሸጥ ሲል እነዚሁ ሸቀጥ አስወዳጆች ደረሱበትና በሰጡት ማሰጠንቀቂያ መሠረት ለነሱው በ2 ብር ከሃምሳ ሸጦ ተገላግሏል - “ጎመን በጤና ወንድሜ” በማለት ከግድያ አመለጠ፡፡ እነዚህ የንግዱ ዘርፍ ደላሎችና ወምበዴዎች አንዱን ኪሎ ሙዝ አዲስ አበባ ላይ እስከ 80 ብር፣ አንዱን ኪሎ አቮካዶ እስከ 65 ብር እንደሚሸጡና ብዙዎቻችንን ከአትክልት ተራ እንዳስወጡን ልብ አድርጉልን፡፡ ይህ ክስተት የሚጠቁመን የኑሮ ውድነቱና የዕቃው ሁሉ ዋጋ መጦዝ ሰው ሰራሽ መሆኑን ነው፡፡ እንጂ የ200 እና 300 ብር ኩንታል ስሚንቶ 2000 ብርን የሚያልፍበት፣ የሦስት መቶና አራት መቶ ሽህ ብር መኪና ሁለትና ሦስት ሚሊዮን የሚገባበት፣ የአርባና ስልሳ ብር 12 ቁጥር ፌሮ ብረት 1400 ብር የሚገባበት አዲስ ምሥጢር የለም፡፡ ይሄ የዶላር መወደድ ምንትስ የሚሉት ማስመሰያ ነው - እርሱ ችግር መሆኑ ባይካድም ያን ያህል ኑሮን አያጦዝም፡፡ ዋናው ችግር ፖለቲከኞችና ነጋዴዎች የሚያደርጉት በአጭር ጊዜ ውስጥ የመክበር አባዜ የወለደው አሻጥር ነው፡፡ ስለዚህ ፖለቲካውና ንግዱ በጋንግስተሮች ተይዞ አሣራችንን እየበላን እንደሆነ ይታወቅልን፡፡ በጥይት የሚሞቱትስ ተገላገሉ፡፡ በጥይት የማያገኙንን ደግሞ በየቀኑ ሊባል በሚችል ደረጃ በኑሮ ውድነት እየገደሉን ነው፡፡ በአንዴ መሞት ይሻላል፤ እርሱ ግልግል ነው፡፡ በየቀኑ መሞት ግን ከፈጣሪም፣ ከኅሊናም፣ ከባህልና ከሃይማኖታዊ ቀኖናም ለሚለይ ኃጢኣትና ወንጀል ይዳርጋልና መጥፎ ነው - ሰው ሁሉ ግራ ተጋብቶ በ“ዛሬ ከምሞት ነገ ልሙት” ዓይነት አካሄድ እየሆነ ያለውን እያየነው ነው፡፡ ለኛ እየደረሰ ያለው ለጠላትም አይድረስ፡፡ ጅል ሰው አያሸንፍህ ወንድሜ፤ ሞኝ ሰው ጋር ትግል አይግጠምሽ እህቴ፡፡ ሰውን አደነዘዙት፤ ብቻውን የሚያወራው በዝቷል፡፡ በሰካራምና በዕብድ ብዛትም የዓለምን ሪከርድ (ክብረ ወሰን) ሳንሰብር አንቀርም፡፡ እንደማኅረሰብም፣ እንደሀገርም እየጠፋን ነው፡፡ አጠፉን፡፡

በመጨረሻ አንድ ነገር ልናገርና ላብቃ፡፡ እውነተኛ ታሪክ ነው፡፡ አንድ ወንደላጤ ነበር፡፡ ከአንዲት የሚወዳትና የምትወደው ድመቱ ጋር ነው ይኖር የነበረው፡፡ ገና አላገባም፡፡ አንድ ወቅት ከሥራ ሲመለስ ድመቱ አንድ ጥፋት አጥፋታ ያገኛታል፡፡ በጣም ይናደድና ቤቱን ዘግቶ ሊደበድባት ይነሳል፡፡ ድብደባውንም ባለ በሌለ እልሁ ወብርቶ ይጀምራል፡፡ ያቺ መውጫ ያጣች ምስኪን ድመት ዱላው ሲበዛባት በመጨረሻ የሞት ሞቷን የደብዳቢውን ጉሮሮ ታንቅና የአቅሟን ትታገላለች፡፡ ምን ዋጋ አለው - በማንም አይድረስ - በሦስተኛው ቀን የወንደላጤው ቤት ሽታ በማምጣቱ ጎረቤት ተሰብስቦ ከፍተው ቢገቡ የልጁ ሬሣ ተጋድሞ ድመቷም በርሀብ ተቆራምዳ ግን አንገቱን አንቃ ይዛ አገኙ፡፡ አዎ፣ ቀን አይጉደልብህ ወንድሜ፡፡ ያሳደግኸው ውሻና ድመት ግፍ ከበዛበት አንቆ እንደሚገድልህ እወቅ፡፡ ተፈጥሯዊ ነው፡፡

መጪው ጊዜም ለአክራሪው ኦሮሞ ልክ እንደዚሁ ነው፡፡ ጅላጅል ኦሮሞ ቀን ሰጠኝ ብሎ አማራን በያለበት እያረደ የሚቀጥል እንዳይመስለው - እንኳንስ የክፋት ሥራ የደግ ሥራም መጨረሻ አለው፡፡ የመረረው አማራ እንደድመቷ ይነሳል፤ መነሳትም ጀምሯል፡፡ “የማይቀጡት ልጅ ሲቆጡት ያለቅሳል” እንዲሉ ሆኖ አሁን አማራው አትግደሉኝ ብሎ ሲናገር በምን ተደፈርኩ ቁጣ የሚያስገመግመው አክራሪ ኦሮሞ አማራው ከእውነት ሲነሳ መግቢያ ቀዳዳ ያጣል፤ በአማራ ላይ የሠራውንም ግፍ ሁሉ ይራገማል፡፡ አንድ እጅግ የሚገርም ነገር ላስታውስህ - አማራ በወለጋ “አትግደሉኝ” ብሎ መናገር እንደቅንጦት ይቆጠራል፡፡ የአማራ ብቸኛ መብት እንደበግ መታረድ ብቻ ነው - እርዱን በቃልም ሆነ በሰውነት እንቅስቃሴ መቃወም እንደጥጋብና እንደድፍረት ይቆጠርበታል፣ “ኧረ! ለዚህም ተደርሶልኛል?” በማለት የአገዳደላቸውን ሥልትና ብቀላቸውን ያከፉታል፡፡ የጅሎቹ ጅልነት የሚለካው በዚህ አዲስ ክስተትም ነው እንግዲህ፡፡ በየትም ሀገር ሰው ሲሰቃይና ሲገደል ተፈጥሯዊ የሆነ አጸፋውን ያሳያል፤ ያም ያለ ነገር ነው፡፡ ይህ ግን ለአማራ አይፈቀድም፡፡ እንደድፍረት ይቆጠራልና፡፡ አማራ ሲገድሉት “እሰይ! ጎሽ! እንዲያ ነው አገዳደል ማለት፡፡ በል በቶሎ ግደሉኝና ከምድር ልሰናበት” ብሎ እንዲለምናቸው ሳይጠብቁ አይቀሩም እነዚህ ጅሎች፡፡ ጅሎች አልኩ? - ጅቦች ለማለት ነው፡፡ ወይ የኢትዮጵያ ምድር - ምኑን አፈራ በል፡፡

አማራ ሲገደል ዝም ያለው አንድም ሁነኛ አመራር ስለሌለውና በሌላ በኩል ሀገሩ እንዳትፈርስበት፣ በድራቦሹም የትም ያሉ ወገኖቹ በነውጠኞች እየተገደሉ እንዳያልቁበት ሰግቶ እንጂ ጠላቶቹን ፈርቶ እንዳልሆነ መታወቅ አለበት፡፡ አማራ ጊዜው ሲደርስ ምን ማድረግ እንዳለበት ጠንቅቆ ያውቃል - አማራ ከድመት እንደማያንስ መቼም ሁሉም እንደሚረዳ እገምታለሁ፡፡ ያም ጊዜ በእጅጉ ደርሷል፡፡ ብአዴን የተባለው የአህያ ባልም ዋጋውን ያገኛል፡፡ እርሱ እያለ ደግሞ አማራና የአማራ የነጻነት ትግል ስንዝር መንቀሳቀስ አይችልም፡፡

ብልህና አስተዋይ ኦሮሞዎች ወንድሞቻችሁን እንድትመክሩ በዚህ አጋጣሚ ላስታውስ፡፡ ጥጋብ ወደራብ ይነዳልና ከዚያ ማዶ ጠብ አድርሰኝ እያሉ በጠብ ያለሽ በዳቦ ንጹሓንን እያረዱ ያሉ ኦሮሞዎች ከዚህ ሰይጣናዊ ድርጊታቸው እንዲታቀቡ የሚሰሟችሁ ከሆነ ምከሯቸው፡፡ ነገ እዬዬ ማለት ለማንም አይጠቅምም፡፡ አብሮነታችን በነዚህ ባለጌዎች ከአሁኑ በበለጠ መበላሸት የለበትም፡፡  በእርግጠኝነት ነው የምነግራችሁ ነገ ሌላ ቀን ነው፡፡ ግፈኛ ደግሞ ባረደበት ቢላዎ ይታረዳል - ፈጣሪ እኮ ውሉን አይስትም - እናም እነዚህ የአጋንንት ውላጆች እንዲህ በአማራ ደም እንደዋኙና በሰው ነፍስና ሥጋ እንደተጫወቱ - በሽመልስ አገላለጽ እንደቆመሩ - ይቀጥላሉ ብሎ ማሰብ ከነሱው ባልተናነሰ ገልቱ መሆን ነው፡፡ ዋናው ጦርነት ደግሞ ገና አልተጀመረም፡፡ ኦነግ/ኦህዲድ የሚፈነጨውና ግዳይ እያስቆጠረ ያለ የሚመስለው ከወንዶች ጋር ተዋግቶ ሳይሆን ሕጻናትንና ሴቶችን፣ አእሩግንና በአልጋ ቁራኛ የተመቱ ህሙማንን እያረደና በቤት ውስጥ ዘግቶ እያቃጠለ ፊልም በመሥራት በሚያገኘው ደስታ ነው፡፡ ከታጠቀ ኃይል ጋር ተዋግቶ በሚገኝ ድል መፈንጨት እኮ ወግ ነው፡፡ ሕጻናትንና ነፍሰ ጡሮችን ቤት ውስጥ ዘግቶ በማቃጠል፣ በውጤቱም የማሕጸን የስምንትና የዘጠኝ ወር ጽንስ ሲፈነዳ በሣቅና በደስታ መፈንጠዝ ምን ይባላል? እነዚህ ጉዶች ከየት መጡብን? ፈጣሪንስ ምን ያህል ብንበድለው ይሆን አቢይና ሽመልስ ለሚባሉ ለነዚህ ጉግማንጉጎች አጋልጦ የሰጠኝ? ይሄኔ አዋቂና አስተዋይ ሰው ተግኘቶ ካልመከረ መቼ ሊመክር ነው? ከሕጻናትና ነፍሰ ጡሮች ጋር ደግሞ ውጊያ የለም፡፡

ለማንኛውም ወንድ ሲገጥመው ልናይ ቀናት ብቻ ይቀራሉ - ምናልትባም ሣምንታት፡፡ ዝም ማለት ስለሰለቸኝ ነው ዛሬ ብቅ ያልኩት፡፡ በዚያ ላይ ሰሚ ሳይኖር ጩኸት ጊዜንና ንዴትን ማባከን ነው ከሚልም ነው ዝምታየን ያጸናሁት፡፡ ጸሎቴ ያቺን ቀን ለማየት ነው፡፡…