Saturday, October 19, 2019

የጎሳ ድርጅቶች አነሳስና የፖለቲካ መስመራቸው ዓላማና አደጋው አገሬ አዲስ (Ethio Semay) ጥቅምት 8 ቀን 2012 ዓም(19-10-2019)


የጎሳ ድርጅቶች አነሳስና የፖለቲካ መስመራቸው ዓላማና አደጋው
አገሬ አዲስ
(Ethio Semay)
ጥቅምት 8 ቀን 2012 ዓም(19-10-2019)
የጎሳ ፖለቲካ በማንና ለምን ዓላማ ተነሳ?አገር ወዳዱ የጎሳ የፖለቲካ  ድርጅቶችን  እንዴት ያያቸዋል?በእነሱስ ላይ የነበረውና  ያለው አቋም ምን ይመስላል?ምንስ መሆን አለበት?”ብሔርና ብሔረሰብ”  የሚለው አወዛጋቢ ስያሜና  የብሔር መብትን የሚመለከተው  የፖለቲካ አቋምና ውሳኔ ከየት፣መቼና  ለምን ተነሳ(መጣ)?፣ይህስ አቋም  ከዓለም አቀፍ ሕግና ስምምነት አንዲሁም   ከኢትዮጵያ አንድነትና ነጻነት  አንጻር እንዴት ይታያል?ያመጣው ጉዳትና ጥቅም ምን ይመስላል?


ለእነዚህ ጥያቄዎች ተገቢ መልስ መስጠት የማንኛውም የኢትዮጵያን አንድነትና ነጻነት የሚሻ በጎ አሳቢ ዜጋና  የፖለቲካ ስብስብ አላፊነት ነው። እኔም አንድ አገር ወዳድ ዜጋ በመሆኔ በዚህ ጥያቄ ላይ የጠራ አቋም መያዝ ይገባል ብዬ ስለማምን ጉዳዩ ትኩረት እንዲያገኝና  በጥናት ላይ የተመሰረተ ማብራሪያ እንዲሰጥበት እያሳሰብኩ ለመነሻ ያህል የበኩሌን ለመሰንዘር ይህንን ጽሁፍ አበረክታለሁ።ሌላው ከእኔ በበለጠ ጥልቀት ያለው ጥናታዊ ጽሁፍ እንደሚያቀርብ እተማመናለሁ።


በቅድሚያ መታወቅ ያለበት ጉዳይ በአንድ ወቅት ላይ የተከሰተ አመለካከት ወይም የተላለፈ ውሳኔ በሌላ ጊዜ ሊታይና ሊታረም አይገባውም ማለት አይደለም።በተለይም  የፖለቲካ ጥያቄን በሚመለከት የሚከሰቱ ሁኔታዎችን ተከታትሎና ተገንዝቦ ለወቅቱ ጥያቄ ተስማሚ መልስ የመስጠትና አቋም መያዝ ፣ ቀደም ሲል በተወሰደ ውሳኔ የአተረጓጎምና የአቋም  ስህተትም ቢኖር የማስተካከል የአንድ ዜጋ፣ የፖለቲካ ድርጅት ወይም ስብስብ ሃላፊነትና ግዴታ ነው።«ቃሌ ቃል ነው!» ብሎ ከነስህተቱ መንጎድ ካለፈው አሰራር ባህል ያለመላቀቅ ድክመት ነው። በራሱ ዙሪያ ብቻም ሳይሆን በህብረተሰቡ ያመለካከትና የግንዛቤ ስህተትም ካለ እንዲታረም የማስተማርና የማስረዳት ሃላፊነት አለበት።ከሕዝቡ ላለመነጠል ወይም የተወሰነ ቡድን ጋር ላለመጋጨት ሲል ስህተትን ተሸክሞ መጓዝ አይኖርበትም።ደፍሮ ስህተትን ፈልቅቆ የማሳየት ሃላፊነት አለበት።

ወደ ዋናው እርእሱ ከማምራቴ በፊት፣በቂ ትንታኔ ያልተሰጠውን የኢትዮጵያ  የግዛት አንድነት ሲባል ምን ማለት እንደሆነ ማብራራት ተገቢ ነው። የኢትዮጵያ አንድነት ስንል ወያኔ ቆራርሶ በካርታ ያስቀመጣትን የአሁኗን  ኢትዮጵያን ነው? ወይስ የእኛ ትውልድ የተረከባትን ቅድመ ወያኔ ኢትዮጵያ? በዚህ ላይ ግልጽ ግንዛቤ ሊኖር ይገባል።


 እስከ አሁን ድረስ ግን ጥያቄው ሳይነሳ በመቅረቱና ከዚህ ጋር የተያያዘው አደጋ እያደገ በመምጣቱ፣ብሎም አዲሱ ትውልድ ባለፈው ትውልድ በተፈጸመ የስህተት ባህር ውስጥ ተዘፈቆ ተመሳሳይ ስህተት ሲፈጽም ማየቱ ተገቢ ስላለመሰለኝ ያለፍንበትን የትግል  መንገድና የአመለካከትና የአቋም ዝንባሌ በማሰስ የሚታረመውን አርመን  ትክክለኛውን አጠንክረን መያዝና ማውረስ ተገቢ ነው ከሚለው ድምዳሜ ላይ ደርሻለሁ።ስለሆነም  አሁን መታየት እንዳለበት በማመን ጥያቄውን ለማንሳት ተገድጃለሁ።  በእኔ አስተያየትም፦


የአገራት  አንድነትና ልዑላዊነት አደጋ ውስጥ የገባው የቅኝ ግዛት መርሆ  በሆነው፣የተለያዩ አገሮችን ለመውረር በሚደረገው ጉዞ ሕዝቡን ለመከፋፈል የብሔር ብሔረሰብ ጽንሰሃሳብ  እንደ አንድ ስልት መጠቀም ሲጀመር ነው።ጣልያን ድንበር ጥሳ ኢትዮጵያን በወረረችበት ጊዜ  ለአገዛዝዋ እንዲያመቻት የኢትዮጵያን አስተዳደር በጎሳ መስመር ከፋፍላ  እንደነበር ታሪክ ይመሰክራል። በቀጥታ አገራትን ማንበርከክ ካልተቻለ አገራት በውስጥ ትርምስ እንዲዳከሙና ሰርጎ ለመግባት ወይም በተዘዋዋሪ በእጃዙር ቅኝ አገዛዝ ስር እንዲወድቁ የተገለገሉበት መሳሪያ ነው።በመካከለኛው ክፍለዘመን አውሮፓውያን ድንበር ዘለል አሰሳና መስፋፋት ሲጀምሩ ኢትዮጵያን ለመያዝ ብዙ ሙከራ ቢያደርጉም በመሪዎቹ ቆራጥነትና በሕዝቡ አልበገር ባይነት ፍላጎታቸው ሊሰምር አልቻለም። ይኸው ዓላማቸው ግን በሌላ መልኩ ጊዜ ጠብቆ ለመነሳትና ለማንሰራራት ችሉዋል። በተለይም ከሃምሳ ዓመት ወዲህ  «በብሄር  መብትና እኩልነት» ስም መርዛማ የጎሳ ፖለቲካ ተጠንስሶ  ሲረጭና የሚያራምዱ የጎሳ ድርጅቶች ከተፈለፈሉ በዃላ ችግሩ ሊያድግ ችሎዋል።


ቀደም ሲል አገራችንን ለመያዝ የሞከሩ የውጭ ሃይሎች በተለይም ጣሊያኖችና እንግሊዞች የተጠቀሙበት አንዱ ስልት ህዝቡ በአንድነት ቆሞ ያገሩን አንድነትና ነጻነቱን እንዳያስከብር በቋንቋና በእምነት ከፋፍለው በከባቢ ላይ ያተኮረ ቅስቀሳና አደረጃጀት በመዘርጋት ነበር።አሁን በአገራችን የሚታየው የፖለቲካ ትርምስና የመበታተን ስጋት፣ የህዝብ መፈናቀል፣የከባቢ አለመረጋጋት፣ ክልል የሚል የልዩነት ድንበር ፈጥሮ መስፋፋትና የመሬት ነጠቃ መነሻው ጣልያንና እንግሊዞች ተክለውት ከሄዱት መርዛማ አስተሳሰብ የመነጨ ነው።የውጭ ሃይሎች በእነሱ ስር ዓላማቸው ባይሳካም ዓላማቸውን አስፈጻሚ አገር በቀል ባንዳዎችን ለመፍጠር አላቃታቸውም፤ የተማረውን ክፍል በጎሰኝነት ጠበል አጥምቀው በነጻነት ስም የገዛ አገሩን ለማፈራረስ እንዲሰለፍ የሞራል ፣የፖለቲካና የገንዘብ ድጎማ በማድረግ አጠናክረውታል። ኢትዮጵያ የምዕራብ አገሮች በቅኝ አገዛዝ የጫኑትን ቀንበር ለመስበር የመጀመሪያና ለሌሎቹም ምሳሌ የሆነች አገር በመሆኗ የበቀል ክንዳቸውን የዘረጉባት አገር መሆኗን መዘንጋት አይኖርብንም።


ከሃምሳ ዓመት በፊት በተማሪው እንቅስቃሴ ዙሪያ የተነሳውን አገር ወዳድና ለዲሞክራቲክ ለውጥ የተነሳ   ትግል ተገን አድርገው አጋጣሚ ይጠብቁ የነበሩ በተለይም በኤርትራ፣በትግራይና  በወለጋ ጠ/ግዛት የተወለዱና ለከፍተኛ ትምህርት የታደሉት ጥቂት ተማሪዎች ከአገር አፍራሽ የውጭ ሃይሎች በተለይም ከጣልያንና ከእንግሊዝ እንዲሁም ከአረብ መንግስታትና ሃይማኖትን ተገን አድርገው ሰርገው በገቡ ሚሲዮናውያን የተቀበሉትን«የተጎዳህና መብትህ የተገፈፈ ነሀና ለነጻነትህ ተነሳ»የሚል  ቅስቀሳና ስብከት ለመተግበር በውጭ አገርና በአገር ውስጥ «የብሄር ጥያቄ»በሚል በዴሞክራሲና በግራ ፖለቲካ ሽፋን  ብዙ ግድፈቶችና ስህተቶች የተሸከመ አተረጓጎም በመስጠት አደገኛ የጎሳ ፖለቲካ በማራገብና በማስፋፋት፣አገራችንን አሁን ላለችበት አደጋ  አጋልጠዋታል። ከነዚህም ዋናዋናዎቹ ተዋናውያን ቀደም ያሉትና የአሁኖቹ የኤርትራ(ሻእቢያና ጀበሃ)የህወሃትና የኦነግ መስራቾችና  መሪዎች ናቸው። የነሱንም ዓላማ በማወቅም ሆነ ባለማወቅ የሚያራግቡ አልጠፉም፤አልጠፋንም።ይህንን ታሪክ ተገንዝቦ ሳይፈሩ ለአዲሱ ትውልድ ማሳወቅና  የመበታተኑን አደጋ ማሶገድ የአንድነት ሃይሉ ሃላፊነት ነው።


በዚህ «የብሄር መብት»በሚል ስም የተደራጁትና ወጣቱንም በመርዘኛ የዘር ፖለቲካ ያጠመቁት ግለሰቦችና ቡድኖች አሁን  እንደ እስስት ቀለማቸውን ቢለውጡም ኢትዮጵያን የማፈራረሱን ውስጣዊ ዓላማና እምነታቸውን አልቀየሩም።አሁንም በተለያዬ የጎሳ ስምና ማንነት ፖለቲካቸውን እያራመዱ ይገኛሉ፤ በፊት ያደረሱትን ጥፋትና ስህተት አምኖ ከመታረም ይልቅ ለዚያ ካባ የሚሆን ስመብዙ ድርጅት እየመሰረቱ መጓዙን መርጠዋል።አሁንም የብሔር ጭቆና አለ ብለው ያምናሉ።


እስከ አሁን በዓለም ላይ የተቀሰቀሱትን ጦርነቶች መነሻ ምክንያት ብንመለከት አብዛኛዎቹ  በሃይማኖትና በዘር/በጎሳ  ዙሪያ የተቀሰቀሱት ከፍተኛውን ድርሻ ይይዛሉ፤ያደረሱትም ጉዳት ከፍተኛ ነው።ጉዳቱን የተገነዘቡትና ሰለባ የሆኑት አገሮች በዘርና በሃይማኖት ዙሪያ የሚካሄደውን ፖለቲካ በህግ ከልክለዋል።ከነዚህም ውስጥ አንዷ ከአስራ ሶስት ዓመት በፊት በሚሊዮን የሚቆጠር ህዝብ ያጣችው፣የ ጎሳ ፖለቲካ ሰለባ የሆነችው  ሩዋንዳ ነች። እኛስ  ጎሳና ሃይማኖትን መሰረት ያደረገ ፖለቲካ አሁን እየደረሰብን ካለው የበለጠ ጉዳት እንደ ሩዋንዳ እስኪያደርስብን ድረስ ይሆን የመንጠብቀው? እውነቱ ይነገር ከተባለ እንደሩዋንዳው እልቂት ይፋ ሆኖ ባይታይም  ባለፉት ሃምሳ ዓመታት  በገሃድና በስውር ያለቀው ህዝብ በሩዋንዳ ውስጥ ካለቀው ህዝብ ቁጥር ይበዛ እንደሆነ እንጂ አያንስም።ጀበሃና ሻእብያ ከዚያም በዃላ እህወሃትና ኦነግ ሌሎቹም ጎሰኛ ድርጅቶች ከተፈጠሩበት ጊዜ ጀምሮ እስከ አሁን ድረስ ምናልባትም እስከወደፊቱ በህዝባዊ ክርን እስኪንበረከኩ ድረስ አገር ወዳድ ኢትዮጵያውያኖች ከኖሩበት ያገራቸው መሬት እየተፈናቀሉ ለእልቂት የተጋለጡ መሆናቸውን ወደፊትም ሊጋለጡ እንደሚችሉ መካድ ወይም መዘንጋት አይገባም።አሁን ያለው ሁኔታና የጎሰኞች በላይነት ካልተቀጨ ኢትዮጵያ ፈራርሳ ሁሉም ጎሳ በድንበር ግጭት የሚተላለቅበት ዕድሉ ሰፊ ነው።ለዛም ምሳሌ የምትሆነን ዩጎዝላቪያ ነች።


የአገራችን አንድነት በአደጋ ውስጥ ስለሚገኝ ያንን ለመከላከል መነሳት የአገር ወዳዱ ዋና ተግባር መሆን አለበት።አደጋው መኖሩን ብቻ ሳይሆን ከየት በኩል እንደመጣና እንደሚመጣም በመገንዘብ ወዳጅና ጠላቱን ለይቶ ማወቅ ይኖርበታል።ትግሉ በአንድነትና በጸረ አንድነት ጎራ የሚካሄድ ፍልሚያ ነው። በአንድነት ጎራ ስር የሚሰለፉት  ድርጅቶችና ግለሰቦች የኢትዮጵያ አንድነት የተናጋውና ሊናጋም የሚችለው በጎሳና የክልል የፖለቲካ እንዲሁም በሃይማኖት ዙሪያ በሚነሳ አስተሳሰብና አደረጃጀት መሆኑን ማመን አለባቸው።የአሁኑም ስርዓት  አንቀሳቃሾችም ሆኑ በተመሳሳይ የጎሳ አደረጃጀት በተቃዋሚ ስም የሚንቀሳቀሱትም የዚያ አካል  መሆናቸውን መካድ አይኖርባቸውም። ስለሆነም እነሱን ታግሎ ማሸነፍ እንጂ አጋር ማድረግ አይቻልም።እሳት በብብት ውስጥ አያቅፉምና!የአገራትም አንድነት የተገነባው በጸረ አንድነት ውድቀትና መቃብር ላይ ነው።


በእኔ ግንዛቤ የጎሳ ድርጅቶችን በሁለት መልክ ከፍሎ የማዬት ዝንባሌ እንዳለ እረዳለሁ።አንዱን ለአንድነት የቆመ፣ሌላውን በጸረ አንድነት ጎራ የተሰለፈ በማድረግ።ይህ አመለካከት በእኔ በኩል ትክክል አይመስለኝም።የጎሳ ጥያቄ ከሰብአዊ መብት ጥያቄ ተነጥሎ የፖለቲካ ጥያቄና መዘውር ከሆነ፣በጎሳም ስም የፖለቲካ ድርጅት ተፈጥሮ መንቀሳቀስ ከጀመረ አደገኛ ነው።ስለሆነም አንዱ የጎሳ የፖለቲካ ድርጅት አገር አጥፊ ሌላው አገር ገንቢ ተብሎ መለየት አይገባውም።ግራም ነፈሰ ቀኝ ጎሰኛ ጎሰኛ ነው።ከራሱ ቋንቋ ተናጋሪና ስሜታዊ የድንበር መስመር ከዘረጋበት መሬት አልፎ አይሄድም።


በጎሳ የተደራጀ ድርጅት መነሻና መድረሻው ጎሳና ክልሉ መሆኑን በገሃድ አይተነዋል።የጎሳ ፖለቲካ አራማጆች ሃይል ለመሰብሰብ ሲሉ ቅድሚያና የፖለቲካ እንቅስቃሴ መነሻ የሚያደርጉትና  ትኩረት የሚሰጡት በስሙ ለተቋቋሙበት አካባቢ(በአሁኑ አጠራር ክልል)እና ማህበረሰብ መሆኑን የሚክድ የለም።ከተቆናጠጡ በዃላ ግን የመከራ ገፈታ ቀማሹ የሚሆነው በስሙ የተነሱበት ጎሳ ነው።


ይህንን በተመለከተ ፕሮፌሰር ተስፋጽዮን መድሃኔ(ብሬመን ዩኒቨርሲቲ፣ጀርመን)በጃንዋሪ 2013   ኤርትራ እንደእናት አገር፣ችግሮችና ፈተናዎች ትናንትም ዛሬም”በሚለው መጽሃፋቸው በገጽ 18-19 ላይ የጠቀሱት የትግራይ ተወላጆችን  በሚመለከት በአጼ ዩሃንስና በአሁኖቹ  በኢህአዴግ/ህወሃት መሪዎች መካከል ስለእናት አገር ያላቸው ግንዛቤና አመለካከት የተለያዬ መሆኑንና ቅድሚያ የሚሰጡት ማንነታቸው ምን እንደሆነ እንዲህ ሲሉ አቅርበዋል።


”የዛሬው የትግራይ ፖለቲከኞች ወይም የፖለቲካ ተዋንያን ወይም እሊት እናት አገራችሁ ማነች? ለሚለው ጥያቄ የሰጡት መልስ በመንፈስም በአስተሳሰብም አሳሳቢ በሆነ መጠን ይለያል።በጥያቄው ከተሳተፉት የትግራይ ፖለቲከኞች መሃል እናት አገራችን ኢትዮጵያ ነች ብለው የመለሱ 3.6%፣ከመቶ ሶስት ነጥብ 6 ብቻ ናቸው።አብዛኛዎቹ በጥያቄው የተሳተፉ የትግራይ ፖለቲከኞች ግን እናት አገራችን ትግራይ ነች ነበር ያሉት፤ኢትዮጵያ አላሉም።አቶ ስብሃት ነጋ ይህንን ጥያቄ  ለአንድ አፍታ ዝግ ካለና ካመነታ በዃላ ሲመልስ እናት አገር ሲባል በአእምሮው ውስጥ ድቅን የምትልበት ትግራይ መሆንዋን ገልጽዋል።እንደዚሁም አቶ ጸጋዬ በርሄ እስከቅርብ ጊዜ ድረስ የትግራይ ክልል ፕሬዚደንት የነበረና የአሁኑ የህዝባዊ ወያኔ ማዕከላዊ ኮሚቴ ስራአስፈጻሚ አባል የሆነው ይህ ጥያቄ ቀርቦለት ሲመልስ ሳያመነታ በቀጥታ እናት አገሬ ትግራይ ነች ነው ያለው፤ኢትዮጵያ ነች አላለም።በትግራይነቴ በኩል አድርጌ ነው ኢትዮጵያዊ የምሆነው በማለት መልሱን  ስስ በሆነች ኢትዮጵያዊነት ሸፍኑዋታል።ይህ እናት አገራችን ትግራይ እንጂ ኢትዮጵያ አይደለችም የሚል መልስ ከታወቁ የህዝባዊ ወያኔ አመራር አካሎች ሲደመጥ የሚያሳስብ ክስተት ነው።በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ የኢትዮጵያ ነገሥታት እናት አገር ሲሉ ሃሳቡ ኢትዮጵያን የሚያመላክት እየሆነ ነው የመጣው።ኢትዮጵያን እናት አገር ብለው ነው የሚጠሩዋት። ለምሳሌ አጼ ዩሃንስ እንኳን የተምቤን ተወላጅ ፣የትግራይ ሰው ሆነው ኢትዮጵያን ነበር እናት አገር የሚሉዋት።ይህንን በግልጽ የምታመለክት በብዙ የታሪክ መጽሃፍ ዘወትር የምትጠቀስ ፣በጣም ጥልቅ ይዘት ያላት የኚህ አጼ ንግግር አለች።ንጉሱ በ1887 ዓም ከጣልያን ጋር ጦርነት ለመግጠም ወደ ሰሓጢ ዘመቻ ሲነሱ ለመኳንንቶቻቸውና ለሰራዊታቸው “ እኔም ስለእናቴ ስለኢትዮጵያ ህይወቴን ልሰዋላት ሙሉ ፈቃድ አለኝ”ካሉ በዃላ የሚከተለውን አወ። ”የኢትዮጵያ ልጅ ሆይ! ልብ አድርገህ ተመልከት!ኢትዮጵያ የተባለችው አንደኛ እናትህ ናት፣ሁለተኛ ዘውድህ ናት፣ሶስተኛ ሚስትህ ናት፣አራተኛም ልጅህ ናት፣አምስተኛም መቃብርህ ናት።እንግዲህ የእናት ፍቅር፣የዘውድ ክብር፣የሚስት ደግነት፣የልጅ ደስታ የመቃብር ካባነት(ታቃፊነት)እንደዚህ መሆኑን አውቀህ ተነሳ “
እዚህ በላይ በሰፈረው ታሪካዊ ማስረጃ ላይ በግልጽ እንደምናዬው ጎሰኞች ከመንደራቸው ያለፈ አገራዊ ፍቅርና ስሜት እንደሌላቸውና ጎሰኞች ያልሆኑት ደገሞ በኢትዮጵያዊነት መንፈስና ኩራት ለአገራቸው አንድነትና ነጻነት እስከመጨረሻው ህይወታቸውን ለመስጠት ቆርጠው የሚነሱ መሆናቸውን ነው።


ከላይ በቀረበው ማስረጃ ስንነሳ የጎሳ ፖለቲከኞች ምንም ጊዜ ቢሆን ለስልት መጠቀሚያ ካልሆነ በስተቀር ኢትዮጵያዊነታቸውን እንደማያምኑበትና እንደማይቀበሉት ነው።ታዲያ ከህወሃትና ህወሃት ጠፍጥፎ ከሰራቸው የጎሳ ፖለቲካ ድርጅቶች ምን አይነት ኢትዮጵያዊነት ይጠበቃል? 


 አሁን በአገራችን የሚታየው ምስቅልቅል ሁኔታና አለመረጋጋት የመጣው በጎሳ ድርጅቶች ምክንያት መሆኑን መካድ አይቻልም።ለስልጣን አቋራጩና ቀላሉ መንገድ በጎሳና በክልል መልክ መደራጀቱ በመሆኑና ኢትዮጵያንም ለማፈራረስ የሚፈልጉ የውጭ ጠላቶች የሚገቡበት ቀላሉ ቀዳዳ ይኸው ስለሆነ ለጎሳ ድርጅቶች ድጋፍና እርዳታ ይሰጣሉ።የአውሮፓና የአረብ አገሮችን የቆዬና እስከ አሁንም ድረስ የዘለቀ ጸረ ኢትዮጵያ ታሪክ ማዬቱ ተገቢ ነው።የእነሱ ኢትዮጵያን የማፈራረስ ሴራ የሚከናወነው በጎሰኞች ጫንቃ መሆኑን ያምናሉ።ቀደም ሲል በርበራና ዘይላ ቀጥሎ ጂቡቲ ከዚያም ኤርትራና የሃሰብ የምጽዋና አዶሊስ የባህር በሮችና ወደቦች ማጣት የዚህ ውጤቶች ናቸው።አሁን አገራችን ኢትዮጵያ ዙሪያዋ በውጭ ሃይሎች በተለይም በአክራሪ የአረብ አገራት ጦር የተከበበች የጦር ዒላማ ሆናለች። የቀድሞ ወደቦቿ ለአረብና ለሃያላን መንግስታት የጦር ሰፈሮች ሆነው በሚፋጠጡበት የጦር ቀጠና ውስጥ ገብታለች። ከስልጣናቸው ባሻገር የወደፊቱን አደጋ አርቆ ማየት የሚሳናቸው መሪዎች ክብርና ድንበራቸውን ለገንዘብ እየሸጡ እንመራዋለን የሚሉትን አገርና ህዝብ ለአደጋ አጋልጠውታል።ለእልቂት አሳልፈው ሰጥተውታል።የዛ ጥቅም ተቋዳሽ ለመሆን በተቃዋሚ ጎራ የተሰለፉትም የጎሳ ድርጅቶችና ስብስቦች የተሻልን ጥቅም አስከባሪዎች ነን እያሉ ለወዶ ገባ ባርነት ነጮቹንና አረቦቹን  ሲማጠኑ ይታያሉ።ለህልውናቸውና ለህዝብ ጥቅም፣ላገራቸው ክብርና አንድነት እንዳይቆሙ የስልጣን ፍቅር ዓይናቸውን ሳይሆን ህሊናቸውን ጋርዶታል።


የጎሳ ፖለቲካና የጎሰኞችን ምንነት የሚያሳዬው ሌላው የምሁር ጥናት ውጤት ደግሞ የሚከተለው ነው።

ፍራንስ ፋኖን የተባሉት ምሁር በ1968 ዓም (እ.አ.አ)”The WRetched of the Earth” በሚለው ርዕስ በጻፉት መጽሃፍ ላይ በገጽ 183-184 እንዲህ ይላሉ


“ወደፊት የከበርቴ አምባገነን አናይም፤የምናዬው የጎሳ አምባገነንነትን ነው። የሚኒስትር ካቢኔ አባላት፣አምባሳደሮች፣ከፍተኛ የጦርና የደህንነት ሹማምንት (አዛዦች) ሥልጣን ከጨበጠው ሰው ወይም ቡድን ቤተሰብ ወይም ጎሳ የተመረጡ ይሆናሉ።ይህ በጎሰኞች የተሞላ የስልጣን ማዕከል የከባቢ ስሜትንና የመገንጠልን ፍላጎት እንዲያድግ ያበረታታል።በመሆኑም ጎጠኞች (ከባቢያውያን) ተጠናክረው ሃይል ይፈጥሩና አገር ብትንትኑ ይወጣል። ጎሰኝነት የተጠናወተው አምባገነን መሪ ጎሰኞች የአገር ንብረትና ሃብት እንከፋፈል የሚለውን ጥያቄ እንዲያነሱ ይገፋፋቸዋል። ሆኖም ጎሰኛው አምባገነን ለሥልጣኑም ስለሚሰጋ ምንም እንኳን ከመቸውም በላይ አላፊነት የጎደለው፣አደጋውን ያልተገነዘበና የተናቀ ቢሆንም ይህንን ጥያቄያቸውን እንደ ክህደት ቆጥሮ  ያወግዛል እንጂ አይቀበልም።ማንኛውም አምባገነን የትልቅ አገር መሪ ለመሆን ይመርጣል፤ ለዚያም የሕዝቡን ስሜት የሚቀሰቅሱ አባባሎችንና እርምጃዎችን ይወስዳል፤ጎሰኝነትን የሚቃወም መስሎ ሲምልና ሲገዘት የዋሁ እያጨበጨበለት ይከተለዋል“በማለት ዛሬ በአገራችን ላይ የተከሰተውን ከሃምሳ ዓመት በፊት በትንቢት መልኩ አቅርበውታል። 


ወደወቅቱ ያገራችን ሁኔታ ስንመለስ
በልማት ስም  የመሬት ነጠቃውና ወረራውእንዲሁም ችብቸባው በገጠርና በከተማ እዬተስፋፋ መምጣቱ፣ በአገሪቱ አንጡራ ሃብትና በህዝቡ ላብ የተገነቡ ተቋማትን በርካሽ ዋጋ በመሸጥ ለውጭ አገር ከበርቴ አሳልፎ መስጠቱ በስፋት በመካሄድ ወይም ለመካሄድ ዝግጅቱ በመጠናቀቅ  ላይ ነው።ለዚያ ማስረጃ ዓለም አቀፍ ውልና ስምምነት አስፈጻሚ ድርጅቶች በአማካሪነት ስም ብዙ ያሜሪካ ብር ተክፍሉዋቸው ሥራቸውን ጀምረዋል።


 አገራችን ኢትዮጵያ  ጎሰኞች በቀደዱት ቦይ  እንድትጓዝ  መንገዱ ከተቀየሰ ውሎ አድሯል።ለዚያ ፊትአውራሪዎቹ በኢሕአዴግ ድንኳን ውስጥ የተሰገሰጉት በስልጣን ላይ ያሉት ሲሆኑ በተቃዋሚ ጎራ ያሉትም በጎሳ የተደራጁት ቡድኖች ከዚህ የተለዬ ብሔራዊ ጥቅምንና ያገሪቱን አንድነት ለማስከበር የተነሱ  አይደሉም።የጎሰኞቹ ምኞትና ፍላጎት ተሳክቶላቸው አገር ብትበታተን የማታማታ ጨዋታ ፈረሰ ዳቦ ተቆረሰ ይሉና አገሪቱን እንደዳቦ ቆራርሰው በደረሳቸው መሬት በሚተከለውየጎሳ ድንኳናቸው ውስጥ ይሰባሰባሉ።ለኢትዮጵያ አንድነትና ለዴሞክራሲ ስርዓት መስፈን ቆመናል የሚሉ አንዳንድ የፖለቲካ ድርጅቶችም ካለው ስርዓት ጎን በተፎካካሪ ስም ሆነው ሕዝቡን እያጭበረበሩት ፣ጎሰኞችን መታገል ሳይሆን በማገም ላይ ተሰማርተው ይገኛሉ።ሕዝቡ የሚፈልገው የጎሳን ስርዓት የሚያሶግድ አማራጭ የሆነ አገር ወዳድ የፖለቲካ ድርጅት እንጂ ተለጣፊና አጃቢ ድርጅት አይደለም።


ወራሪዎች በተለያዬ መልክ እንደሚመጡ በታሪክ ታይቷል፤ጥንት በሃይማኖት ስም፣ከዛም በዃላ በወታደር ሃይል ድንበር ሰብሮ በመውረር፣ አሁን ደግሞ በአንቨስትመንት ስም በገንዘብ ሃይል አገሮችን  በቁጥጥራቸው ስር የማድረጋቸው ስልት በስፋት ተግባር ላይ ውሉዋል።አገር ወዳድ ተቃዋሚ እንዳይነሳም ህዝቡን በጎሳ መከፋፈልና መበታተን አንዱ ስልት ነው። ያንን ደግሞ የሚያስፈጽሙላቸው ብሄራዊ ስሜት የሌላቸው፣የጥቅም ተካፋይ የሆኑ  የወያኔ፣ የኦነግ፣የኦህዴድ፣የብአዴን፣የደህዴንና ና የመሳሰሉት ጎሰኛ ቡድኖች ናቸው።


ጎሰኞች ለጥቅማቸው እንጂ እንታገልለታለን ለሚሉት ጎሳ አይጨነቁም።ለሚፈልጉት ዓላማ ጥቂቱን በመጥቀም  መረማመጃ ወይም መሳሪያ ከማድረግ ያለፈ ቁም ነገር ሊሰሩለት እንደማይችሉ ለስልጣን የበቁትን ማየቱ ይበቃል።የጎሳቸውን ታላቅነት ከማራገብና ለጥቂቶቹ ብቻ የተረፈ ለውጥ ከማምጣት የዘለለ ለብዙሃኑ ቁም ነገር አይሰሩም። በወገንተኝነት ስሜት ሰክሮ አጃቢያቸው የሚሆነውም የጥቅሙ ተካፋይ አይሆንም፤ስለእኩልነትና ስለዲሞክራሲ ቢጠይቅ የቅጣት ክንዳቸው ያርፍበታል እንጂ የጎሳዬ ተወላጅ ነው ተብሎ ምህረት አይደረግለትም። ጎሰኞች ብሔራዊ ስሜትና ያገር ፍቅር ስለሌላቸው ከውጭ መዝባሪዎች ጋር በመመሳጠር የሃገር ንብረት በመዝረፍ ወደውጭ በማውጣት በራሳቸው ወይም በቤተሰብ ስም ድርሻና (Share)ቋሚ ንብረት (Property) በመግዛት ተግባር ላይ የሚውሉ፣ ብሄራዊ ካዝና የሚያራቁቱ ሌቦች መሆናቸውን በገሃድ አይተናል፤እያየንም ነው።


 በጎሳ የተደራጁ ስብስቦችን ለዴሞክራሲ እንደቆሙ አድርጎ መቁጠር ላለፉት ሃምሳ ዓመታት የተሰራውን ስህተት ተሸክሞ መጓዝ ይሆናል። የጎሳም ሆነ የክልል ችግር ቢኖር ስርዓት ያመጣው ችግር እንጂ ሕዝብ በሕዝብ ላይ የጣለው ሸክም አይደለም።ሁሉም የኢትዮጵያ ሕዝብ በስርዓቱ የተጎዳና የተበደለ ስለሆነ መፍትሔው የስርዓት ለውጥ ማምጣት ብቻ ነው።የጎሳ ልዩነት የአገር ችግር አካል ስለሆነ  ህብረህዝብ(አገር አቀፍ) የሆነ አመለካከት ያለው የፖለቲካ ድርጅት ሊፈታው ይችላል፣የመፍታትም ግዴታ አለበት።የጎሳ ድርጅት አገር አቀፍ የሆነ ችግር ከመፍጠር በስተቀረ  አገር አቀፍ መፍትሔ ሊያመጣ  አይችልም።


የአገር የግዛት አንድነትን ማስከበር ሲባል ፣አገር በውጭ ሃይል እንዳይደፈር  መከላከል ብቻ ሳይሆን በአገር በቀል ጸረ አንድነት ሃይሎችም የሚነሳውን እንቅስቃሴ መቋቋምና ማሶገድ ብሎም ለስልጣን የሚያደርጉትን ሩጫና መቅበዝበዝ ማጨናገፍንም ይጨምራል።የጠላቴ ጠላት ወዳጄ ነው  በሚለው የጅሎች ቀቢጸተስፋ ለተመሳሳይ ቡድን አገርን አሳልፎ መስጠት ያው በገሌ ይሆናል።የጎሳን መብት ተገንና ምክንያት አድርጎ በሚነሳ ውዝግብ የአገር አንድነት፣ የህዝቡ ኑሮ ፣ግንኙነት፣አሰፋፈር፣ባህል፣ታሪክ እንዳይናጋና  የተፈጥሮ ሃብት እንዳይወድም መከላከል  የትግሉ አካል ሊሆን ይገባዋል።


ከሃምሳ ዓመት ወዲህ በብሄርና በሃይማኖት ስም የተነሱት ሃይሎች ሲወድቁ ሲነሱ አገራችን መሪ ባጣችበት ሰዓት ከሃያ ስድስት ዓመት በፊት በቅርብና በሩቅ የኢትዮጵያ ጠላቶች እርዳታ   የስልጣኑ ባለቤት የሆነውን የጎሰኞች ስብስብ ቡድን ፈጥረው የአገራችንን አንድነትና ነጻነት አሁን ካለበት አደገኛ ሁኔታ ላይ አድርሰውታል።ሁኔታው በዚህ ከቀጠለ ኢትዮጵያ የምትባል አገር ቀርቶ ስለ ኢትዮጵያ የሚያወራ ዜጋ የሚቀር አይመስልም።ሁሉም በየመንደሩ ተሰግስጎ  የጠባብ ክልል እስረኛ የመሆኑ ዕድሉ ከፍተኛ ነው።በየመንደሩም ቢሰገሰግ በሰላም ይኖራል ማለት አደለም፤በየጊዜው በድንበርና በጥቅም እየተጋጨ፣እየተዋጋ  ማቆሚያ በሌለው የጦርነት ሰንሰለት ውስጥ የሚማቅቅበት ዕድሉ ከፍተኛ ነው።ከዚያ አደጋ መውጣት የሚቻለው ጸረ ኢትዮጵያዊነትና ጸረ አንድነት የሆነውን ጎሰኝነትንና ጠባብነትን ታግለን ስናሸንፍ ብቻ ነው።በጎሳ የተደራጁት ወደ ህሊናቸው ተመልሰው በኢትዮጵያዊነት  በመቆም አትዮጵያዊነትን የሚገልጹ እሴቶችን ማለትም ሰንደቅ ዓላማዋን፣ዳር ድንበሯን፣ የህዝቡን ስብጥርነትና በየትኛውም ቦታ ሰረቶ የመኖሩን መብት ማወቅና ያንንም አክብሮ  ለማስከበር በይፋ እስካላሳዩ ድረስ በልዩ ልዩ ስም እየተደራጁ መምጣታቸውና ከአንገት በላይ አንድነት እያሉ ቢናገሩ ዋስትና እንደማይሆን፣ጊዜ መግዣና ማዘናጊያ ሊሆን እንደሚችል መታወቅ አለበት።ምንም እንኳን የጎሳ ድርጅት መሪዎቹ ኢትዮጵያዊነታቸውን  ለመቀበል ድፍረቱ ይኖራቸዋል ተብሎ ባይጠበቅም የአንድነት ሃይሉ በጎሰኞች የተጭበረበረውን ሕዝብ ከእነሱ መንጋጋ ለማውጣት ተግቶ መስራትና መታገል ይኖርበታል።


በልዩልዩ ስም የተደራጁት የጎሳ ስብስቦች በመካከላቸው ያለው ልዩነት ቢኖር በስልጣን ድርሻና ዓላማቸውን ለማሳካት በሚሄዱበት ስልት  ላይ ያተኮረ እንጂ ኢትዮጵያን በማፈራረሱ ግባቸው ላይ አይደለም።ሁሉም ጎሰኛ  ከክልሉ ውጭ ኢትዮጵያን አጉልቶ የሚያይበት የህሊና መነጽር የለውም።
አንዱ አክራሪ መገንጠልን በይፋ ሲለፍፍ ሌላው በተራዘመ ስልት አዘናግቶ ከባቢውን አሳድጎና በቂ ሃይል ፈጥሮ ፣ሌላውን አዳክሞና ከቻለም አጥፍቶ መገንጠልን ይመርጣል።ለዚህ ደግሞ «ፌዴራሊዝም»የሚለው እንደ ፈለጉ ሊወጡ ሊገቡ የሚችሉበት ስልታዊ ስርዓት የተመቸ ነው።ትክክለኛው የፖለቲካ  ፌዴራሊዝም የተለያዩ ሁለት ወይም ከዚያ በላይ የሆኑ አገሮች የየራሳቸውን ድንበርና መንግስት እንዳስከበሩ በተወሰነ ደረጃ ተቀራርበው በጋራ ጥቅም ላይ ለመተባበርና  ለመስራት ማለትም በንግድ ልውውጥ፣ በመገናኛ፣በህዝብ የመዘዋወርና የመኖር መብት፣የጋራ የመከላከያ ተቋምን በሚመለከተው ዙሪያ የሚስማሙበትየአገሮች ትስስር  ሲሆን ከሁለት አንደኛው ፌዴራሊዝሙን በቃኝ ካለ ሊነጠልና የራሱን መንገድ ሊከተል የሚችልበትን መብት የሚረጋገጥበት ነው።


 በሌላም በኩል በኩታ ገጠም መሬት ውስጥ እየኖሩ  የተለያዬ ጎሳ፣ባህል፣ቋንቋና  እምነት ያላቸው ማህበረሰቦች በተለያየ ጠባብ መሬትና   በልዩነትና እየተዋጉ  ከመኖር ይልቅ  በጋርዮሽ አንድ አገር መስርተው መኖራቸው ጥቅም እንዳለው በመረዳት በፌዴራል ደረጃ  ማእከላዊ መንግስት በማቋቋም በአንድ ሰንደቅ ዓላማ ስር መተዳደራቸውም የተለመደና  የተመረጠ ነው።ለዚህ ምሳሌ የምትሆነው በ1291 እ.አ.አ. ከጣሊያን፣ከጀርመንና ከፈረንሳይ ድንበሮች ተቦጫጭቃ  የተፈጠረችው ስዊዘርላንድ ነች።የረጅም ዘመኑ ቅልቅል በህዝቡ መንፈስ ውስጥ የአንድ አገር ዜግነትን እያጎለበተ የዘር ግንዱን ስሜት እያቀጨጨው መጥቷል።ዛሬ ስዊዘርላንድ ውስጥ በቋንቋውና በዘር ግንዱ የተለየሁ ነኝ ብሎ የሚያወራ ቀርቶ የሚያስብ የለም።


ቋንቋንና ጎሳን መሰረት ያደረገ ፌዴራሊዝም ከንትርክና አለመግባባት ብሎም ከመለያየት አደጋ የራቀ አይደለም።ለምሳሌ ዩጎዝላቪያን መጥቀሱ በቂ ነው።ዩጎዝላቪያ ከተለያዩ ማህበረሰቦች ውህደት የተመሰረተች አገር ስትሆን ውህደቱ እንደ ስዊዘርላንዱ እረጅም ዕድሜ የለውም፤ግፋ ቢል የአንድ መቶ ዓመት ዕድሜ ነው።ቅርጽና መልክ የያዘው ግን ከሁለተኛው ዓለም ጦርነት በዃላ ነው።በዚህ አጭር ዘመን የከበርቴው ዓለምና የሶሻሊስቱ ዓለም በመዳፉቸው ለማስገባት መረባቸውን የዘረጉባት አገር ነበረች።በነማርሻል ብሮዝ ቲቶ በመሰሉ አገር ወዳድ መሪዎች ጥንካሬ ነጻነቷን አስከብራ ለመኖር ብትችልም ከማርሻል ብሮስ ቲቶ ህልፈት በዃላ በተፈጠረው የመሪ ክፍተትና የፖለቲካው ውጥረት እየጦዘ መምጣት አገሪቱን እንዳገር እንዳትሆን አድርጓት አልፏል።የቀድሞዋ ዩጎዝላቪያ ተብላ ለመጠራት አብቅቷታል።አብሮ የነበረው የአንድ አገር ህዝብ አሁን በጠላትነት የሚተያዩ የተለያዩ አገሮች ህዝቦች አድርጓቸዋል።የጦርነትና የእርስ በርስ እልቂት የማስፈራሪያ ተምሳሌት ሆነዋል፤መጭው ትውልድ በበቀልና በጥላቻ እንዲተያይ አድርጎታል።ያ በዘር፣ በቋንቋና በሃይማኖት ሰበብ የመጣ ችግርና ቀውስ ነው።ውጤቱ ግን ሁሉም የውጭ አገር ሃይሎች እንደልባቸው የሚቦርቁበት እድል ከመፍጠሩ በቀር ያገሩ ህዝብ ለበለጠ ድህነት፣ስጋት፣ስደት ተጋልጦ ይገኛል።


እኛስ ምን አይነት ፌዴራሊዝም ቢኖረን ይሻላል?
 በአንድ አገራዊ መንግስት ተዋቅሮ የሚኖር ህዝብ  ለከባቢው ጉዳይ የራሱን ምክር ቤትና  አስተዳደር መስርቶ ከመካከለኛው መንግስት ጋር በስርዓት ሰንሰለት ተሳስሮና ተመካክሮ  መስራቱ ከቀናው የፌደራሊዝም አኳያ የሚታይ ይሆናል።አነዚህ የክፍለሃገር አስተዳደሮችና ማህበረሰቦች ግን ተገንጥሎ አገር የመሆን መብት ሊኖራቸው አይችልም።ሙሉ ለሙሉ ለማዕከላዊው መንግስት ህግና ስርዓት ያደሩ ናቸው።ያላቸው መብት በከባቢ ጉዳይ ላይ የመወሰን ነጻነት ብቻ  ነው።ይህ አይነቱ የከባቢ አስተዳደር  በውስጡ የሚኖረው ህዝብ ስርዓቱን ከቅርበት እንዲከታተለው፣ጉዳዩ በአጭር ጊዜ ውስጥ እንዲጠናቀቅለት፣ ውጣ ውረድ እንዳይገጥመው፣አስተዳደሩና ባለስልጣኖቹ ከህዝቡ ቁጥጥርና እይታ እንዳይርቁ፣ከሙስና የጸዳ፣ ግልጽነት እንዲኖር የሚረዳ የመንግስት አወቃቀር ነው። የአሜሪካንና የጀርመን አገራዊ አወቃቀር ለዚህ ምሳሌ ነው።በየክልሉም ሆነ በየክፍላተ ሃገሩ የስልጣን እርካብ ላይ የሚሰየሙት በክልል  ወይም በጎሳ ትውልዳቸው ሳይሆን በሚከተሉት የፖለቲካ አመለካከታቸው ነው።የሚወዳደሩትና ሥልጣኑን የሚይዙት የፖለቲካ ድርጅቶች ስለሆኑ ፕሮግራማቸው አገር አቀፋዊ  እንጂ በክልል ደረጃ የሚነደፍ አይደለም።የሚተዳደሩበትም ሕግ አጠቃላዩ አገራዊው ሕገመንግስት ነው።


ኢትዮጵያም በዚህ አይነቱ አሰራር እንዳለፈች መግለጹ በጎሳ ፖለቲካ ንፋስ በሚነፍስበት ዘመን የተወለደው ትውልድ እንዲያውቀው ማድረግ የአንጋፋው ትውልድ አላፊነት ነው። ምንም እንኳን አንደ አሜሪካኖቹና ጀርመኖቹ በህግ የተደነገገ የስራና የስልጣን ክፍፍል ባይኖርም በኢትዮጵያ ውስጥ የጠቅላይ ግዛቶች ወይም የክፍለሃገሮች አመሰራረት ለዚያ ተግባር ታስቦ እንደነበር መግለጹ ተገቢ ነው።በዛም አገራዊ አወቃቀር  ዜጋ በፈለገበት ያገሪቱ ክፍል ተንቀሳቅሶ፣ሰርቶና ንብረት አፍርቶ፣ከሚፈልገው ጋር ትዳር መስርቶ በሰላም ኑሮ ፣የጥምር ጎሳ ልጆችን ወልዶ ለመሳም ችሉዋል።በዚህ መልክ የተወለዱት ኢትዮጵያውያን ቁጥር ከመብዛቱ የተነሳ እንገንጠል ብለው አገር ከሚያምሱት ቁጥር በላይ ነው።የቀረው ነገር ቢኖር የጠቅላይ ግዛቱ ወይም የክፍለ ሃገሩ አስተዳደር በህዝቡ ቁጥጥርና ህዝቡም  የሚሳተፍበት አለመሆኑ ነው።የስልጣኑ ሁሉ ባለቤት ግለሰቦችና  ቡድኖች መሆናቸው ነው። ፊትም ሆነ አሁን የህዝቡ ጥያቄና ፍላጎት ልገነጣጠል ሳይሆን እኔም ባለድርሻ ነኝና የከባቢዬን ጉዳይና የራሴን  ኑሮ እራሴው ልወስን፣አስተዳዳሪዎቼን እኔው ልምረጥ፣የመንግስትን አሰራር የምቃወምበት  ወይም የምደግፍበት ነጻ መስክ ይኑር ፣በየትኛውም ያገሬ መሬት ሰርቼ የመኖር መብቴ ይረጋገጥ፣ባህልና ሃይማኖቴን በነጻነት የማራምድበት መብት አይነፈገኝ፣የሰብአዊና የዜግነት መብቴ ይከበር የሚል ነው።ተገንጣዮች እንደሚሉት ሳይሆን አብዛኛው ሕዝብ ለአገሩ አንድነት፣ሰላምና ነጻነት እንዲሁም ክብርና  እድገት ዘብ የቆመ ነው።


የጎሳ ድርጅቶችና መሪዎቻቸው ይህንን የህዝብ ፍላጎትና ጥያቄ አይቀበሉም ። በኢትዮጵያ አንድነት ስለማያምኑም የአንድ አህዳዊ መንግስትን መኖር  አይፈልጉም። በአገራዊ አስተዳደር ውስጥ ከመሳተፍና የአንድ ጠንካራ አገር ዜጋ ከመሆን ይልቅ ኢትዮጵያ ተበታትና  የከባቢ ሹምባሽ መሆንን ይመርጣሉ። አንድ ብሔራዊ ሰንደቅ ዓላማ ከማውለብለብና ህዝብ ሊግባባበት የሚችለውን አንድ ብሔራዊ ቋንቋ ከመናገር ይልቅ የተለያዬ ባንዲራ ተሸክሞ የተለያዬ ቋንቋ እየተናገረ ሳይግባባ በጠላትነት እንዲሰለፍ ይመርጣሉ። የኢትዮጵያን ህዝብ ፍላጎት ሳይሆን የኢትዮጵያ ጠላቶችን ፍላጎት ከግቡ ማድረስን ይመርጣሉ።ከፍ ያለ ፍላጎት ቢኖራቸው ደግሞ ሙሉ ለሙሉ ስልጣኑን ተቆጣጥረው በወያኔ ምትክ  የወያኔን ስራ መስራት ይሆናል። ያም ከውጭ አገር ባርነት የራቀ አይደለም።   


ኦፒዲኦ የሚባለውን ድርጅት የሚቃወሙ የኦሮሞ ድርጅቶች ለጎሳቸው የሚሰጡት መልስ ተመሳሳይ ነው። ከሆነላቸው ስልጣኑን ሙሉ ለሙሉ ተቆጣጥረው መግዛት ካልሆነላቸው ከኢትዮጵያ ተገንጥሎ መኖር ነው።ሌሎቹም በጎሳቸው ስም መጠቀም የሚሹ የየጎሳ ድርጅታቸውን መስርተው ከማን አንሼ ውድድር ውስጥ የገቡት ጥቂቶች አይደሉም።ቀላሉና አቋራጩ መንገድ የጎሳ ባቡር ሃዲድ መዘርጋት ስለሆነ በዚያው አቅጣጫ እየነጎዱ ነው።በሃይማኖቱም አንጻር እንዲሁ።እንደተለያዩት የኦሮሞ የጎሳ ድርጅቶች ወያኔንም የሚቃወሙት የትግራይ ጎሰኞች እንዲሁ ለትግራይ እንጂ ለቀረው የኢትዮጵያ ህዝብ አይጨነቁም፤ገና ከጅምሩ የትግራይ ነጻ አውጭ ብለው ሲጀምሩና ወያኔ የስልጣን ባለቤት ከሆነ በዃላ በስልጣን ላይ የነበሩ ግለሰቦች በተፈጠረ ውስጣዊ ችግር የተነሳ ስለተለያዩ ጫካ የገቡበትን ዓላማ አሽቀንጥረው ጥለው ለአንድነት የሚታገሉ ናቸው ብሎ መቁጠር ጅልነት ነው።አሁንም አደረጃጀታቸው ያንኑ የአንድ ጎሳ ስምና ክልል ጥቅም የሚያስከብር ነው።ያማ ባይሆን  ኖሮ የትግራይን መስፋፋትና  በወሎና በጎንደር የተፈጸመውን የመሬት ዘረፋ በተቃወሙ ነበር፤ ነባሩ ተፈናቅሎ አዲስ የትግራይ ሰፋሪ ቦታውን እንደሚቆጣጠረው አልፎም አካባቢው በትግራይ አስተዳደር ስር መውደቁ በታሪክም ያልነበረ የወራሪ ውሳኔ መሆኑን እያወቁ የተቃውሞ ድምጻቸውን ባሰሙ ነበር።ውጤቱ ምን ሊሆን እንደሚችል እያወቁም ለለበጣ ያህል አዲስ መጡ ሰፋሪ በሚቆጣጠረው መሬት ላይ   ድምጽ ይሰጥበት(በሬፍሬንደም ይወሰን) አይሉም ነበር።ይህ አቋም ታላቋ ትግራይን ከመመስረቱ ዓላማ ተነጥሎ ሊታይ አይገባውም።


የጎሳ ማንነት የኢትዮጵያዊነትን መንፈስ እየተጠናወተው መሄዱ በአማራውም ማህበረሰብ ላይ ድባቡን እየጣለበት መጥቷል።አማራው ለሁሉም ጎሳ እንደጠላት ተቆጥሮ የሚደርስበት ጥቃትና በደል ባይካድም ያንን ለመከላከል ሲባል ግን የራሱን የቀበሮ ጉድጓድ ከመቆፈር ይልቅ የኖረ የኢትዮጵያዊነቱን አቋም ይዞ ቢታገል የሚያዋጣው ይሆናል።በሱ ላይ የሚደርሰውን ጥቃት ከሌሎቹ ኢትዮጵያውያን ነን ከሚሉት ጋር በመተባበር ሊያሶግድ ይችላል።ሌሎቹም የአማራው መጠቃት የእኔ መጠቃት ነው ብለው ከጎኑ ሊሰለፉ ይገባል።በግንባር ቀደምትነት የህይወት መስዋዕት ከፍሎ አሁን የሚኖሩባትን አገር ባለቤት ያደረጋቸው አማራው መሆኑን ሊገነዘቡት ይገባል።  አልፎ አልፎም በዚህ በተጠቃ የአማራው ማህበረሰብ ስም አማራው እንደኦሮሞው፣እንደትግሬውና ሌሎቹም ተገንጣዮች ተገንጥሎ የራሱን ነጻ አገር መመስረት አለበት የሚሉ እንዲነሱ የሚደረግም አሻጥር እንዳለና እንደሚኖር መዘንጋት አይገባም።መነሳታቸው የሚያስገርም ቢሆንም የወያኔ መልእክተኞች እንጂ የአማራው እውነተኛ ተቆርቋሪዎች ናቸው ተብለው አይቆጠሩም።አማራውና የኢትዮጵያ አንድነት የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጾች ናቸው፤አማራውን ለጥቃት ያበቃው ለኢትዮጵያ አንድነት ካለው ፍቅርና ከሚከፍለው መስዋእትነት የተነሳ መሆኑ ሊዘነጋ አይገባም።አማራን ከጥፋት መታደግ ኢትዮጵያን ከጥፋት መታደግ ነው። በኢትዮጵያዊነቱ የሚያምነውና ለኢትዮጵያ አንድነት የሚቆመው የሌላው ማህበረሰብ ተወላጅ የሆነው ኢትዮጵያዊ በአማራው ላይ  የሚደርስበትን በደልና መከራ መታደግ ብሔራዊ ግዳጁ እንደሆነ ሊያውቀው ይገባል።ዛሬ በአማራው ላይ የተመዘዘ የጥፋት ዱላ ነገ በዬተራ በሁሉም ላይ ሊመዘዝ እንደሚችል ማሰብ ብልህነት ነው።ኢትዮጵያ የአማራው ብቻ ሳትሆን በሌሎቹም አስተዋጽኦ የተመሰረተች የጋራ አገር ናትና አጋርነቱን በይፋ ማስመስከር ይጠበቅበታል።       


የተጀመረውን አገር የማፈራረስ ሂደት ለማጠናቀቅ ጎሰኞች ከሚወስዱት እርምጃ ጎልቶ የሚታየው
እንቅፋት የሚሆንባቸውን አገር ወዳድ(የራሳቸውም ጎሳ ተወላጅ ቢሆን) በጉልበት ማሶገድ፣መግደል፣ማፈናቀል፣መሬት እየነጠቁ የራሳቸውን ጎሳ ተወላጅ ማስፈር፣የአጎራባች ጠ/ግዛቶችን ለም መሬትና ወንዞች  የእኛ ነው ወደሚሉት ክልል ቀላቅሎ የኤኮኖሚ ምንጭ ማሳደግና መቆጣጠር፣ታላላቅ ፋብሪካዎችንና የሙያ ተቋማትን በክልላቸው ውስጥ ማስፋፋት። በሌላው ኪሳራና ጉዳት መበልጸግ፣ህዝብ እርስ በርሱ የሚጋጭበትን ዘዴ ማስፋፋት ዋና ተግባራቸው ሲሆን ይህንን የማይቃወም የማንኛውም ጎሳ ተወላጅ ወይም ድርጅት ለኢትዮጵያ አንድነትና ለህዝብ ልዑላዊነት እንደቆመ ተደርጎ መቁጠር ስህተት ነው።


እውነቱን ለመናገር  ከዘመነ መሳፍንት በስተቀር  በቅድመ ወያኔ ዘመን  በኢትዮጵያ ውስጥ ጎሳና ክልልን ማእከል ያደረገ ስርዓትና መንግስት አልነበረም።  በተለይም ከአጼ ቴዎድሮስ ወዲህ የነበሩት ነገስታት ኢትዮጵያን አንድ አድርጎ የመምራት እንጂ በጎሳቸውና በተወለዱበት ክልል የተወሰኑ አልነበሩም። አብዛኛዎቹ ህይወታቸውንም አሳልፈው የሰጡት ኢትዮጵያን ሊወር የመጣውን የውጭ ጦር ለመከላከል በጦር ሜዳ ላይ ነው።የአጼ ቴዎድሮስ ህልምና ምኞት በተወለዱበት የቋራና የጎንደር መሬት ላይ ብቻ ተወስኖ የቀረ አልነበረም።አጼ ዩሃንስም ኢትዮጵያን ሊወር የመጣውን የደርቡሾች እስላማዊ ጦር  በመዋጋት መተማ ጦር ሜዳ ላይ ወደቁ  እንጂ ከተከዜ መለስ ያለውን  የትግራይ ግዛታቸውን ብቻ ለማዳን ሲከላከሉ አልተሰዉም።ያጼ ምኒሊክ በአንኮበርና በሸዋ፣ያጼ ሃይለስላሴም በኢጀርሳጓሮና በሃረር ተወስኖ የቀረ ጠባብ አመለካከት የነበራቸው መሪዎች  አልነበሩም። እነዚህ መሪዎች በትልቅነት ለትልቅነት የሚያስቡና የሰሩ  እንጂ በትንሽነት ለትንሽ መንደር የቆሙ አልነበሩም። ደርግም የተባለው የወታደሮች አምባገነን ቡድን ከሁሉም ጎሳ የተውጣጡ የወታደሮች ስብስብ እንዲሁ ምንም እንኳን በህዝቡ ላይ ታይቶ የማያውቅ እልቂት ቢፈጽምም የክልልና የጎሳ ፖለቲካ አላራመደም፤መሪዎቹም ጄነራል አማንሚካኤል አምዶም  የኤርትራ(ትግሬ) ተወላጅ፣ጀነራል ተፈሪ በንቲ የኦሮሞ ተወላጅ፣መንግስቱ ሃ/ማርያምም የኮንሶና የአማራ ተወላጅ ነበር። በቅድመ ወያኔ ዘመን  ለአገር መሪነቱ ሃይል እንጂ የጎሳ ማንነት ወሳኝ  አልነበረም፤ሃይላቸውንም የገነቡት ከተለያዩ ጎሳዎች ከተውጣጡና ተመሳሳይ አስተሳሰብ ካላቸው የከባቢ ጉልበተኞች (ባላባቶች) ጋር በመተባበር ነው።እንደ መሪዎቹ ቅልቅልነት የማንኛውም ጎሳ ባህል፣ቋንቋና እምነት የተከበረ ነበር እንጂ የተከለከለ አልነበረም።ያማ ባይሆን ኖሮ አሁን በኢትዮጵያ ውስጥ የሚነገሩት ቋንቋዎችና የተለያዩ እምነቶች አይኖሩም ነበር።ትምህርትና የስራ ዕድልም እንደዚሁ በጎሳ ማንነት የሚያጡትና የሚያገኙት አልነበረም።የአማራ መንግስታት በሚባሉት ስርዓቶች የአማራው ተወላጅ ከሌላው የበለጠ ኑሮና ዕድል ያገኘ አልነበረም፤ይባስ ብሎ በድህነት አለንጋ የሚገረፈው አማራው ነበር።እውነቱ ይነገር ከተባለ ከኤርትራውያን የበለጠ በኢትዮጵያ ውስጥ የደላው ህዝብ አልነበረም።ዓይን ያወጣ አድሎና ልዩነትን የፈጠረው፣የዘመነ መሳፍንትን ታሪክ የደገመው ላለፉት 29 ዓመታት በስልጣን ላይ የተቀመጠው ወያኔ መራሹ ኢህአዴግ  የተባለው የጎሰኞች ስብስብ ነው።


በተጨማሪም አማራው ማህበረሰብ ከሌሎቹ የተለየ የድሎት ኑሮ አልኖረም።ጊዜ ባነሳቸው ጉልበተኞች መከራ ደርሶበታል፤ዘሩን ለማጥፋት ብልቱን ተሰልቡዋል።በየጦር ሜዳው ተማርኮና  ከየመስኩ ታፍኖ የቤት ውስጥ አገልጋይ ከመሆን አልፎ በአገር ውስጥ የባሪያ ንግድ ማእከሎችና እንደ ግንደበረት ባሉት ገበያዎች ተለጉሞ ተሸጧል ፤ታስሮ በወደብ በሮች ተጭኖ ካገሩ ወጥቷል።መሬት አልባም ሆኖ በጭሰኝነት ሲማስን ኖሩዋል። ይህንን እጣ ፈንታ የቀመሰ ማህበረሰብ ሌላውን ማህበረሰብ የጎዳ አድርጎ መቁጠር ፍጹም ስህተት ከመሆኑም ሌላ ሃጢያት ነው።የሌላው ማህበረሰብ ተወላጅ በራሱ ጎሳ ተወላጆች ሲሸጥ ሲለወጥ ኖሯል።አባ ጅፋር፣ የጋሞውን፣ የከፋውን፣ የኦሮሞውን፣ንጉስ ጦና ወላይታውን፣የአፋር፣የሐረርና የሶማሌ  ሱልጣናትም የሌላውን ጎሳ ተወላጅ ብቻ ሳይሆን የራሳቸውን ጎሳ ተወላጅ፣ደካማና ደሃ ፍጡር እያፈኑ በአዶሊስ፣በርበራና አትባራ ወደብ ለአረቦች እየሸጡ ሃብት የሚያግበሰብሱ ነበሩ።በከባቢ ጉልበተኞች መካከል በሚደረግ ጦርነት ላይ የተማረከው የሁሉም ጎሳ ተወላጅ ከዚህ ኢሰብአዊ አያያዝ አላመለጠም። ለመጀመሪያ ጊዜ አድራጎቱን ያወገዙትና በሕግ የከለከሉት የአማራው ተወላጅ የኢትዮጵያ  ንጉስ አጼ ምንሊክ ናቸው።የዘመናችን ተገንጣይ ጎሰኞች ግን ይህንን ደሃውን ወገናቸውን ነጻ ያወጡ ትልቅ መሪ እንደወንጀለኛ አድርገው በመሳል ታሪካቸውን ብሎም የአማራውን ታሪክ ሊያጎድፉት ይሞክራሉ።ምናልባትም የሚቆጫቸው ነገር ቢኖር የራሳችን ጎሳ ተወላጅ በሆነ ጉልበተኛ ለምን ስንረገጥ፣ስንሸጥና ስንለወጥ አልኖርንም፣ለምን እንደሌላው አፍሪካዊ በነጮች አልተገዛንም በሚል የምርጫ ጎደሎ በመነሳት ሊሆን ይችላል። የአጼ ምንሊክ ታሪክና ውለታ ግን ድንበር ተሻግሮ በሌሎች የቅኝ ግዛት አገሮች በተለይም ለጥቁር ሕዝብ  ሕዝብ ኩራትን ያጎናጸፈ፣ ከፍተኛ ዝናና ቦታ የያዘ የታሪክ ሃቅ ነው።

የአንድ አገር ህዝብ ሊግባባ የሚችልበት አንድ ቋንቋ መኖር በኢትዮጵያ አልተጀመረም፤በአማርኛ ቋንቋ ደግሞ ሁሉም ተጠቀመበት እንጂ አልተጎዳበትም። አማራውም ቋንቋው ስለሚነገር ከሌሎቹ የተሻለ ኑሮ አልኖረም።ሌላው ቀርቶ ጠግቦ አላደረም። በታሪክ አጋጣሚ ብሄራዊ ቋንቋ የሆነው አማርኛ ህዝቡን ከቦታ ወደ ቦታ ተንቀሳቅሶና ተግባብቶ ለማደር ጠቀመው እንጂ አልጎዳውም። ሁሉም ከቋንቋው ሌላ አይናገር ቢባል  ሰማንያ የሚሆነው ማህበረሰብ በምን ተአምር ሊግባባ ይችላል?የባቢሎን ታሪክ መፈጠሩ አይደለምን?እንግሊዝኛ ወይም ፈረንሳይኛ ወይም ስፓኒሽ ቋንቋዎች አብዛኛው  የዓለም ህዝብ እንዲግባባ እረዱት እንጂ መቼ ጎዱት?እኛስ ከሌላው አገር ህዝብ ጋር ለመግባባት እነዚህን ወይም የያገሩን ቋንቋ እየተማርን እንናገር የለምን?የእኛንስ አገር በቀል የሆነውን አማርኛ ቋንቋ በአገራችን ውስጥ  መናገራችን ከመግባባት ባሻገር ምን ጉዳት አመጣብን?ከንግግር ያለፈ የራሳችን ፊደላት መኖሩም የምንኮራበት የጋራ እሴታችን እንጂ እንደቀረው አፍሪካዊ በባእዳን ቋንቋ እየጻፍን እንድናፍርና ጥገኛ እንድንሆን መች አደረገን?አላደረገንም።


እውነቱን ለመናገር በቅድመ ወያኔ ስርዓቶች በትምህርትና በስራም  እንዲሁ በህግ ተደንግጎ ጎሳው ተለይቶ አድልኦ የተደረገበት ኢትዮጵያዊ  አልነበረም።የአገሪቱ አቅም በፈቀደው  በሁሉም ቦታ ለማዳረስ ተሞክሯል።የስልጣን ክፍፍሉም ሁሉንም ማህበረሰቦች ተወላጆች ያካተተ ነበር። ከሃምሳ ዓመት ወዲህ የጎሳ ድርጅት  ፈጥረው የሚያተራምሱት የዚያ ዕድል ተጠቃሚዎች የነበሩት ናቸው።ኤርትራን ገንጥሎ መሪ የሆነው ኢሳያስ አፈወርቂ የወሎ ጠ/ግዛት አገረ ገዥ ከነበሩት አጎቱ ከአቶ ሰለሞን  አብርሃም  ቤት እየኖረ ትምህርቱን የተማረው በደሴ ከተማ በወይዘሮ ስሂን ት/ቤት ከዚያም ምንም እንኳን ባይጨርስበትም በቀድሞው የቀዳማዊ  ሃይለስላሴ ዩኒቨርሲቲ  ነበር። የጅቡቲ መሪ የሆነውም እንዲሁ በድሬዳዋ ከተማ እየኖረ የተማረ ነበር፤የወያኔና የኦነግ ባለስልጣኖች እንደዚሁ በተከፈተው ዕድል በኢትዮጵያ ዋና ከተማዎች በሚገኙ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ውስጥ የተማሩ፣ አብዛኛዎቹም በየስራ መስኩ በአላፊነት ቦታ ላይ ተቀምጠው የተጠቀሙ፣ ለነበረውም ስርዓት ያገለገሉ  ናቸው።ያ እውነት ተክዶ የበሉበትን ወጭት ሰባሪዎች ሆነው አገር ለመሰባበር ግብ ግብ ይዘዋል።

የየካቲት 1966 ዓም የለውጥ ንፋስ
ሁሉም ነገር እንደነበር አይቀርምና፣ህብረተሰብም እንዲሁ በለውጥ ሂደት ስለሚጓዝ በኢትዮጵያ ውስጥ ሰፍኖ የነበረው ስርዓት የህዝቡን ፍላጎት ለማሟላት አቅም እያጣ ሲሄድ፣እርሃብ ሰፍኖ የብዙ ሕዝብ ህይወት ሲቀጥፍ፣በተለይም ተማሪው የለውጥ ፍላጎቱ ከፍተኛ በመሆኑ ስርዓቱን ወጥሮ ያዘው።በዓለም አቀፍ ደረጃ የደረሰው የፖለቲካና የኤኮኖሚ ቀውስ ሁኔታውን አባብሶት የለውጥ ማእበል  ኢትዮጵያንም ቀስፎ ያዛት።በዚህ ወቅት ነበር በተማሪው ትግል ውስጥ እራሳቸውን እንደ እባብ ቀብረው የነበሩ ጎሰኞች ቀና ቀና ያሉትና ድርጅት ፈጥረው ጫካ እስከ መግባት የደረሱት።      


አገር ወዳዱ ለውጥ ፈላጊ የተማሪው ትግል በአገር ውስጥና በውጭ አገር ባቋቋማቸው ማህበራት ትግሉን ሲያራምድ ሳያውቀውና ሳይገነዘበው  የጎሰኞች ካሮሳ በመሆን በቅጡ ያልተረዳውን መፈክር አንግቦ በአደባባይ ወጣ፤«የብሄር መብት እስከመገንጠል ድረስ» የሚለውን  ትርጉሙን የሳተ መፈክር የመታገያ አቋሙ አደረገው። በአጥንትና በደም የተዋቀረና የተገነባ የአገር አንድነትና የሕዝብ ትስስርን እንደ ተራ ጋብቻ ውል "የመፋታትና የመለያየት መብት" ማወቅ ተደርጎ በመቁጠር ትልቅ አገር አጥፊ ስህተት ተሰራ።በዚህ ነጠላና ግልብ አመለካከት የለግላጋው ወጣት ተማሪ አዕምሮ እንዲበከል ተደርጎ የአገር አጥፊነት ሂደትን በተራማጅነት ጭንብል( ማስክ )እንዲቀበለው ሆኖ ለአሁኑና ለወደፊቱ ለሚፈራው የአገር መበታተን አደጋ የራሱን ድርሻ አበርክቷል።በአንቀጽ 39 ስር የሰፈረው  ህግ በዚሁ አስተሳሰብ ማህጸን ውስጥ የተጸነሰ ነው።ጥፋቱን አምኖና ተቀብሎ ያንን ማረምና ማስተካከል የደፋሮችና የእውነተኞች ግዴታ ነው።በጥቂቶቹ ጥፋት ብዙሃኑ የዛ ትውልድ አባል ሲወገዝ መኖሩ ትክክል አይደለም።የዛ ትውልድ አባል ለዴሞክራሲ ስርዓት፣ ለአገር እድገትና መሻሻል፣ለእኩልነት የታገለና መስዋእትነት የከፈለ ጀግና ትውልድ ነው። ለራሱ ጥቅም ያደረ፣ብሔራዊ ስሜት የጎደለው፣ምግባረቢስ አልነበረም።


ለመሆኑ የብሔር መብት እስከመገንጠል ድረስ የሚለው መመሪያ ከዬት፣መቼና  እንዴት መጣ? 
ይህ የብሄር  የራስን ዕድል እስከመገንጠል ድረስ  የመወሰን መብት በሶሻሊዝም ጥላ ስር  የግራው ርዕዩተዓለምና ፖለቲካ ሲስፋፋ  አንዱ መሰባሰቢያ የትግል መመሪያ በመሆን ያገለገለ  መፈክር ነበር።የተነደፈውም  በቅኝ ግዛት ስር ይማቅቁ የነበሩትን አገሮች ነጻነት ለማረጋገጥ ለነጻነት ግንባሮች እውቅና የሰጠ መፈክር ነበር።በአውሮፓ በኦቶማን ቱርክ፣በአስትሮ- ሃንጋሪና ጀርመኒ መዳፍ ስር የወደቁትን አገሮች እንዲሁም በአፍሪካ፣በደቡብ አሜሪካና በኢስያ የሚካሄዱትን  የነጻነት ትግል በመደገፍ መፈክሩ ለሶሻሊስቱ ትግል አጋር መሰብሰቢያ ሆኗል፤  በተጨማሪም የዃላዃላ  በሶቪየት ህብረት ስር የተጠቃለሉት የአውሮፓ ሶሻሊስት አገሮች  ካልጣማቸው ከህብረቱ ሊወጡ እንደሚችሉ  የተሰጠ ዋስትና  ነበር። በዚያን ጊዜ ብሄር(ኔሽን) የሚለው ቃል አገር እንጂ ጎሳ የሚል ትርጉምና ግንዛቤ አልነበረውም።የብሄር ነጻነት የሚለውን አቋም ብዙዎቹ የሶሻሊስት መሪዎች በሶቪዬት ሥር የተጠቃለሉትን አገሮች የሰራተኛውን መደብ እንደሚከፋፍለውና  መፈክሩ  የንዑስ ከበርቴው ጥያቄ ነው በማለት ይቃወሙት ነበር። ለምሳሌም የኮሚኒስት ርዕዩተዓለምን በመቀበልና በማሳደግ ብሎም የመጀመሪያውን የሰራተኞች ፓርቲ መስርተው ከነበሩት መካከል የኤኮኖሚና፣የማህበረሰብአዊ ፈላስፋ የፖለቲካ ሊቅ የነበሩት የፖላንድ ተወላጇ ጀርመናዊቷ ዶር. ሮዛ  ሉክሰንበርግ አንዷ ነበሩ። ይህ ብሄረተኝነት(የጎሰኝነት)ዝንባሌ የጸረ አብዮተኝነት ንፋስ ያመጣው ጭንቀትና ሽብር የወለደው ብቻ ሳይሆን  በትግሉና በጋራ ትግሉ ተስፋ መቁረጥ ጭምር የመጣ መሆኑን ብሎም አደገኛነቱን ገልጸዋል። በሶሳሊስቶቹ እምነትና አመለካከት ህዝቦችን ያስተሳሰራቸው ጠንካራ ገመድ በመደብ ላይ ያረፈ የጋራ ብሩህ ዓላማ  መኖሩ ነበር። ያ የጋራ ዓላማ ከያቅጣጫው እየተቦረቦረ ሲመጣ ጥርጣሬና ችንፈት በሰዎች ልብ ውስጥ ሲገባ ከጋራ መድረክ እያፈነገጡ ወደ ብሔሩ ድንኳን ውስጥ መግባትና እያንዳንዱ ለራሱ ብቻ ቆመ፤የብሔር ጥያቄ ቀዳሚውና ዋናው እየሆነ መጣ።  ሲሉ ምስክርነታቸውን ሰጥተዋል።የዃላ ዃላም የዚሁ የጎሰኝነትን ዓላማ የሚደግፉና የሶሳሊስቶችን እምነት የሚቃወሙ በሰራተኛው መደብ ትግል ስም ሰርገው የገቡ ቡድኖች ስልጣኑን ሲይዙ እነ ዶር ሮዛ ሉክሰምበርግንና መሰሎቻቸውን በመግደል አሶገዷቸው።የጎሰኞች ባህሪ አንዱ ይህ አይነቱ ጭካኔ ነው።


የሶሻሊስቱ ርዕዩተዓለም ወይም ፍልስፍና ቅኝ አገዛዝን፣የመደብ ልዩነትን፣ጨቋኝና ተጨቋኝ፣በዝባዥና ተበዝባዥ፣ ዘረኝነት እንዳይኖር፣የሰው ልጆች መብትና እኩልነትን የሚያስተምርና የሚከራከር ሆኖ ሳለ "የላብ አደሩ አምባገነንነት  "የሚለው መንፈስ በሶሻሊስቶቹ ጎራ ለአምባገነንነት ማቆጥቆጥና መነሳት በር መክፈቱ አይካድም።በዚህ ድክመትና ክስተት ላይ በከበርቴው ስርዓት ጎራ ስለሶሻሊስቱ ጭራቅነት በስፋት መወራቱ የብዙሃኑን አእምሮ ለመለወጥና በጠላትነት እንዲሰለፍ አድርጎታል።አምባገነንነት የግለሰቦች ፍላጎትና ምርጫ እንዲሁም ክፍተት የሚፈጥረው እንጂ የህብረተሰብ ምርጫ አይደለም።እዚህ ላይ የከበርቴው ስርዓት ከአምባገነንነት የራቀና የጸዳ ነው ማለት አይደለም።በሁለቱም ርእዩት /ፍልስፍና በሚመሩ የአምባገነን ስርዓቶች ለአገር ብዙ የሰሩና ሊሰሩ የሚችሉ፣ለዴሞክራሲ የቆሙ ዜጎች ለእልቂት ተዳርገዋል።የዜግነት መብታቸው ተጥሶ  ኢሰብአዊ በሆነ መልክ የመከራ ሰለባ ሆነዋል።


በሶሻሊዝም ስም (National socialism)ካባ የሂትለር ናዚና የሞሶሊኒ መነሳት፣ በአገራችንም በሶሻሊዝም (ህብረተሰባዊነት) ስም  መንግስቱ ሃ/ማርያምን የመሰለ ጨካኝና ገዳይ አምባገነን ለስልጣን መብቃት ለዚያ ምስክር ነው።  እነዚህና እነዚህን የመሰሉ በያገሩ የተነሱ የስልጣን እብዶች ባደረሱት ጥፋትና በፈጸሙት ወንጀል የተነሳ መልካም የነበረው ሳይንሳዊ  የስርዓት መመሪያ የተጠላና የተፈራ ሆነ።አንድ አውቶብስ ወይም ባቡር በሰካራም ወይም እብድ ሾፌር ገደል ቢገባ ጥፋቱ የአውቶብሱ ወይም የባቡሩ ሳይሆን የሾፌሩ ነው።ሆኖም ግን በአውቶብሱ ወይም በባቡሩ  ላይ የተዛባ ፍርድ ሲሰጠው መስማቱ የተለመደ እንደሆነው ሁሉ በሶሻሊስቱም ርዩተዓለም ላይ እንዲሁ የተዛባ ትርጉምና አመለካከት ሰፍኑዋል።ተሳፋሪውም እብድ ወይም ሰካራም ሾፌር መሪውን በጨበጠበት አውቶብስ ወይም ባቡር ላይ አልሳፈርም ፤ይውረድና በሌላ ጤነኛ ሾፌር ይተካ ብሎ አለመጠየቁና ፣ ገደል እስኪገባ ድረስ ድምጹን አጥፍቶ መጓዙ የጥፋቱ ተካፋይ ያደርገዋል።አምባ ገነን ስርዓቶችንም እንዲሁ ደግፎ ማጨብጨቡ አጨብጫቢውን ከወንጀሉ ነጻ አያደርገውም።


በሌላ በኩልም ሶሻሊዝም የጎሰኞች መጠቀሚያ መሆኑ ነው።በሶሻሊዝም ስም ስልጣን ላይ ወጥተው በመብትና እኩልነት ስም አገር የማፈራረስ ዓላማ ማስፈጸሚያ መሆኑ አሁን በአገራችን ላይ የሰፈነውን ስርዓት የሚመራውን የወያኔ ቡድን እያዩ መረዳት ይቻላል።ጎሰኝነት ሶሺያሊዝም ሳይሆን የሶሻሊዝም ጸር ነው።ውስጠ ጸባዩ ፋሽዝም ነው።የመደብ አምባገነንነትን በጎሳና በዘር አምባገነንነት ተክቶ የሚንቀሳቀስ ጸረ ሕዝብ፣ጸረ አንድነት፣ጸረ ሰላም፣ጸረ አገር የሆነ የአጥፊዎች መሸሸጊያ ዋሻና ማሳሳቻ ጭንብል(ማስክ) ነው።ይህ አይነቱ መወገዝና መወገድ ያለበት እንጂ በእርቅና በድርድር የሚሞዳሞዱት አይደለም፤ሊሆንም አይገባም። ጎሰኞች ሲያሻቸው ሶሻሊስት አለያም ካፒታሊስት በመሆኑ ጅዋጅዌ ውስጥ እየገቡ ሊያምታቱ ይሞክራሉ።የሶሻሊስቱን አመለካከት በማጣመም ለራሳቸው እንዲያገለግል አድርገውታል። ስለጎሰኝነት ወይም ስለብሔር ጥያቄ ከተገለጹትና ከተጻፉት መካከል የሩስያው መሪ ጆሴፍ ስታሊን እንዲህ ሲሉ አቅርበውታል።
Stalin on national question  በሚለው መጽሃፍ ውስጥ ስለ ብሔር ይህንን ሰፍሮ እናገኘዋለን።


በማርክሲዝም እይታም ብሔር (ኔሽን/አገር) እንዲህ ይገለጻል "what is a nation?" "a nation is primarily a community ,a definit community of people.This community is not racial,nor is it tribal.The modern Italian nation was formed from Romans,Teutons,Etruscans,Greeks,Arabs and so forth.The French nation was formed from Gauls,Romans,Britons,Teutons and so on.The same should be said of the British,the Germans and others,who were formed into nations from peoples of diverse races and tribes.Thus a nation is not a racial or tribal,but a historically constituted community of people.


በሌላውም ቦታ የዚህ  ዃላ ቀር የጠባብ ብሔር  አስተሳሰብ የሚወልደው ቅራኔና ግጭት በእድገትና በተባበረ የህዝብ ትግል እየከሰመ እንደሚሄድ እንዲህ ሲሉ ይገልጹታል። "national differences and antagonisms between peoples are daily more and more vanishing"and that "the supermacy of the prolitariat will cause them to vanish still faster."the subsequent development of mankind,accompanied as it was by the clossal growth of capitalist production,the shuffing of nationalities and the almagation of people within ever larger territories."


የሶሻሊስት ርዩተዓለም የሰራተኛውን መደብ የመብት ትግል በአጠቃላይ የሚያንጸባርቅና ድንበር ዘለል( አለፍ) አመለካከት በመሆኑ በብሔር ስም የሚካሄደው ትግል ብሎም የራስን ዕድል የመወሰን መብት የሚለውን መርሆ ለትግሉ እንቅፋትና ከፋፋይ እንደሚሆን በመገንዘብ ይቃወሙት ነበር።በዓለም አቀፍ ደረጃም ብቻ  ሳይሆን የአንድን አገር የሰራተኛው መደብ ወይም  ህዝብ ትግል ሊያዳክመውና ሊጎዳው እንደሚችል፣ሕዝቡንም ለአገር በቀል በዝባዦችና ጨቋኞች አሳልፎ እንደሚሰጠው በመረዳት ያወገዙት ነበር።  እንደሚከተለውም ይገልጹታል። 


"the national autonomy or national self determination prepares the ground not only for the segregation of nations,but also for breaking up the united labour movement.the idea of national autonomy creats the psychological conditions that make for the division of the united workers party into separate parties built on national lines.The break up of the party is followed by the break up of the trade unions,and complete segregation is the result.In this way the united class movement is broken up into separate national rivulets." "If nationalism implanted among the workars,it poisons the atmosphere and spreads noxious ideas of mutual distrust and segregation among the workers of the different nationalities.It only serves to aggravate and confuse the problem by creating a soil which favours the destruction of the unity of the labour movement,fosters the segregation of the workers according to nationality intensifies friction among them.That is the harvest of national atonomy or national determination."


ይህ ትንታኔ በአጭሩ ሲተረጎም


ጎሰኝነት ወይም የብሔር  አስተሳሰብ በህብረተሰቡ ወይም በሰራተኛው መደብ ውስጥ ሰርጎ ከገባና  ካቆጠቆጠ ሁሉንም የሚበክል መርዝ ይሆናል።አለመተማመን፣ልዩነት፣ብሎም የመከፋፈልን አደጋ ያፋጥናል።እነዚህ ሁሉ የብሔር ነጻነት ወይም የራስን እድል በራስ የመወሰን የሚለው አስተሳሰብ  ውጤቶች ናቸው።


በዚህ ትንታኔ አኳያ አገራችን ኢትዮጵያን ብንመረምራት ከጀርመኑ፣ከጣልያኑና ከቀሩትም ሃገራት ምን የተለየ አገራዊ አመሰራረት አላት?እሷም እንደተቀሩት አገሮች በተለያዬ ጎሳና ነገዶች የሰላም ወይም የግጭት ሂደት በወለደው ውህደት የተፈጠረች አገር ናት።አገር የአንድ ነጠላ ጎሳ ውጤት ሳይሆን የብዙ ጎሳዎች ቅንጅት የሚፈጥረው የህብረት ውጤት ነው።አንዱ ጎሳ ተነጥሎ ለብቻው አገር አይሆንም።አንድ አይነት ቋንቋ መናገር ብቻውን የአንድ አገር ህዝብ አያሰኝም። የካናዳ፣የአውስትራሊያ፣የእንግሊዝ፣የአሜሪካ ህዝቦች  እንግሊዝኛ በመናገራቸው  የአንድ አገር የእንግሊዝ ዜጎች አላደረጋቸውም።ተራርቀው ይኖራሉ፣ኩታ ገጠም መሬት የላቸውም፣ባህላዊ ትስስራቸው የመነመነ ነው፣የኤኮኖሚ ትስስራቸው ይበልጥ ከሚቀርባቸው ጋር የተሳሰረ ነው።ከእንገሊዝ አገር ጋር በዓለም  አቀፉ የንግድ ሰንሰለት የተሳሰሩ እንጂ በእንግሊዝኛ ተናጋሪነታቸው  ብቻ  በአንድ መንግስት የሚሽከረከር ግንኙነት የላቸውም።የእነሱ እንግሊዝነት ያከተመው የሚኖሩበትን ቦታ እንግሊዝን ለቀው ሲሄዱ ጀምሮ ነው።በሄዱበት ለምደው ከነዋሪው ጋር መስለው፣አንድ የጋራ ባህልና ማንነት ፈጥረዋል።የአንድ አገር ሰንደቅ ዓላማ አውለብላቢዎች ሆነዋል።


ይህንን በአገራችን ማህበረሰቦች ተርጉመን ብናዬው ኦሮሞው ፣አማራውና ሌላውም ከአንድ ቦታ ተንቀሳቅሶ በሌላው የኢትዮጵያ መሬት ከሌሎች ማህበረሰቦች ጋር ተቀላቅሎ የኖረ ነው። ከፈለሰበት ቦታ ከሚኖረው ህዝብ ጋር አንድ አይነት ቋንቋ ቢናገርም ከጊዜ ብዛትና ከመቀላቀል የተነሳ በቋንቋ ስላጼ(ዲያሌክትስ)ይለያያል፣የራሱ የሆነ አንድ ወጥ መሬት የለውም፤ለምሳሌ የወለጋው ኦሮሞ ከአሩሲው ወይም ከባሌው ኦሮሞ ሳይሆን   በባህል፣በኤኮኖሚ፣በስነልቦና ይበልጥ ግንኙነት ያለው ወለጋ ውስጥ ከሚኖሩት ኦሮሞ ካልሆኑት ማህበረሰቦችና ከአጎርባቹ ክፍለ ሃገር ህዝብ  ጋር ነው።አብሮ በመኖር ባህል፣ቋንቋ፣እምነት ተወራርሷል።የሌላውም እንዲሁ።የወለጋው ኦሮሞ ከደቡብ ወሎው ኦሮምኛ ተናጋሪ  ከቋንቋው በስተቀር የሚተሳሰርበት ሰንሰለት የለውም ፤የነበረው የጎሳ ግንኙነቱ በፍስለት መቀስ  ተበጥሷል።ኦሮሞ ነኝ ከማለት ወሎዬ፣ሸዌ፣ጎጃሜ፣ሓረሬ ወዘተ በሚለው ተለውጧል።የአንድ ኢትዮጵያዊ መንፈስና ማንነት አስተሳስሮታል።በባህልም የተለያዬ ነው።የሸዋ ኦሮሞ የሚያከብረው የኢረቻ  የአምልኮ በዓል ለወሎ፣ለሃረር፣ለባሌው ወይም ለወለጋው ኦሮሞ እንግዳው ነው። የየከባቢው ኦሮሞ ከሌሎቹ ጋር የተወራረሰው የራሱ የሆነ የከባቢ ባህልና ልማድ አለው።የጋራ ቋንቋ የሆነውንም አማርኛ ተናጋሪ ሆኗል።


የጎሳ ገላጭ ባህሪ በየጊዜው እየተለዋወጠ የሚሄድ እንጂ  ዘላለማዊ  አይደለም። በሰለጠነው ዓለም የሚኖር ማህበረሰብ ከሌላው ተነጥሎ ሊኖር አይችልም፣የግዴታ ከሌሎች ጋር ተሳስሮ እንዲኖር የሚያደርጉት ሁኔታዎች ተፈጥረዋል።የንግድ ማደግ፣የመጓጓዣ መስፋፋት፣የትምህርትና የስራ ዕድል አንዱ ከኖረበት ቦታ ወደ ሌላው ሄዶ እንዲኖር በዛውም ተጋብቶና ተዋልዶ እንዲቀላቀል፣የሱን ባህል ለሌላው በመስጠት እሱም የሌላውን ባህል በመልመድ ከሰፈር እይታ አገራዊና ዓለም አቀፋዊ እይታ እንዲያጎለብት አድርጎታል።የሚወልዳቸው ልጆችም የአንድ ጎሳ ማንነት ሳይሆን የህብረብሔር ማንነት መታወቂያቸው ሆኗል።አስተሳሰብና እይታው ከጫጨ ጠባብ የክልል አመለካከት የላቀ ዐገር ወይም ዓለም አቀፋዊ ሆኗል።ከእድገቱ ጋር የተቆረቆሩ ከተማዎች የአንድ ጎሳ ወይም ማህበረሰብ ይዞታዎች ሳይሆኑ በውስጣቸው የሚኖረው ህዝብ የጋራ እሴቶቹ ናቸው።የመንግስት መቀመጫ ወይም የአገር ዋና ከተማ(መዲና) የሆነ ከተማ የየትኛውም ጎሳና ክልል ንብረት ሳይሆን ሁሉም በጋራ የመሰረተው የጋራ ከተማው ነው።አንዱ ብቻውን የይገባኛል ጥያቄ ሊያቀርብበትና የእኔ ብቻ ነው ብሎ ሊበይንበት አይችልም።የሁሉንም አገር ዋና ከተማ ስናይ አንድ ጎሳ የኔብቻ ነው ብሎ የማይቦርቅባቸው፣የሁሉም ያገሩ ሕዝብ በተለይም የኑዋሪው ሕዝብ የጋራ ይዞታና  ንብረት ናቸው።

   
ወደ ዓለም ታሪክ ዘወር ብለን ብናይ የከበርቴው ስርዓት የሰፈነባቸው አገሮች ገበያ ፍለጋና ለምርት የሚሆኑ የተፈጥሮ ሃብቶችን ለመቆጣጠርና ለመዝረፍ በማደግና ገና በባላባታዊ ስርዓት ስር የሚማቅቁ አገራትን በመዳፋቸው ስር ለማስገባት ሲመቻቸው በዲፕሎማሲ፣በእርዳታና በሃይማኖት ስም፣አለያም በሃይልና በተንኮል ጥቅማቸውን ለማስከበር የሚያስችል መንታ ስልት መጠቀማቸው በታሪክ የታዬ ሃቅ ነው።እንደ ኢትዮጵያ ያሉ እርስ በርስ የሚናቆሩ ባላባቶችና የከባቢ አምባገነኖች ባሉበት አገር አንዱን ባላባት ወዳጅ መስሎ በመቅረብ በምክርና መሳሪያ በመርዳት ሌላውን ለማሶገድና ጠላትን ለመቀነስ የከፋፍለህ ግዛው ፖሊሲያቸውን ዘረጉ።በዚህ ስልት ቋንቋና ሃይማኖት ቀላሉ የማላያያ መሳሪያቸው ሆነ።ሌላ ሌላም የማለያያ ጥቃቅን ምክንያቶች ጎልተው እንዲወጡ አደረጉ።ለዚህ ዓላማቸው በስልጣን የሚሻኮቱትን ተጠቀሙባቸው።የዃላ ዃላ ግን መሰሪ ደባቸው ተጋለጠና  አገር ወዳዶች የከበርቴውን የባዕድ አገር ወረራ ዓላማ በመረዳት ከወጥመዱ ላለመግባት አምቢ ብለው በአንድነት ቆመው  በመመጣበት ሁሉ  ለመቋቋም ቆርጠው ተነሱ፤ጦርነትም ገጥመው ነጻነታቸውን ለማስከበር በቁ።በዚህ ወረራን በማክሸፍ የመጀመሪያ አገር የሆነችው ኢትዮጵያ ነበረች።ለሌሎቹም በተለይም በቅኝ አገዛዝ ስር ወድቀው ለነበሩ የአፍሪካ አገራት በአጠቃላይ ለጥቁር ሕዝብ የነጻነት ምልክት ሆነች።በዚህ የተነሳም ወራሪ የከበርቴ አገሮች በኢትዮጵያ ላይ ጥርሳቸውን ነከሱ፤ በበቀል እርምጃ የምትወድምበትን ዘዴ ማብሰልሰል ጀመሩ።
አሁንም እንደቀድሞው ዋና ስልት ያደረጉት በከባቢ ስሜት፣በደካማ ጎን በመግባት ነው።የልዩ ልዩ ቋንቋዎችና የተለያዩ እምነቶች አገር የሆነችው አትዮጵያ ለዚህ አይነቱ የጥፋት ተልእኮ የተመቸች ሆና በማግኘታቸው በወጥመዳቸው ሊገባ የሚችለውን አጥምዶ ለመያዝ ብዙም ችግር አልገጠማቸውም።ለአፍራሽ ዓላማቸው የሚረዱና የሚተባበሯቸውን በልዩ ልዩ ጥቅም ፣የውሸት ታሪክ አስታጥቀው  የተስፋ ዳቦ  እየመገቡ በመደለል የራሳቸውን አገር ለማፍረስና የበታች ሆኖ ለመኖር የመረጡትን ከብብታቸው ስር አስገቡ፤ከነዚህም ውስጥ  ከማህበረሰቡ ውስጥ በትምህርትና በኑሮ ላቅ ያለ ቦታና ተሰሚነት ያላቸው የበለጠ ስልጣንና ሀብት ለመያዝ የሚቋምጡትን የከባቢ ተወላጆችን ነው። በቀድሞ ጊዜም በዘመነ መሳፍንት ወቅት አንዱን ባላባት በመደገፍ ሌላውን እንዲወጋ መሳሪያ በማቀበል የተለያዬ ሙከራ አድርገዋል።ሆኖም ግን አልተሳካላቸውም፤አገር ወዳዱ ተባብሮ ዓላማቸውን አክሽፉዋል።በዚህ መልክ በየአገሩ በተለይም በአፍሪካ ብሎም በኢትዮጵያ ውስጥ  በተለይም ላለፉት ሃምሳ ዓመታት ጎልቶ የመጣው ችግርና ቀውስ አነሳሱና ምክንያቱ ይኸው ዘረፋን ዓላማ ያደረገው የካፒታሊዝም ስርዓት ሲሆን የጎሳን ማንነትና ጥቅም እንደ ፖለቲካ መነሻና ግብ አድርገው የተነሱ የነጻነት አውጭ ግንባሮችን እንዲቋቋሙ በማድረግ የተጫወቱት ሚና ነው።ያም ጥረት በአለፉት 27 ዓመት ፍሬ አፍርቶ ለማየት በቅተዋል።ሆኖም ግን ኢትዮጵያ ጭራሽ እስክትደቅ ድረስ ለማየት ያላቸውን ምኞት ምንም እንኳን አንዱን በሌላው እዬቀያዬሩ ቢሞክሩም ፍላጎታቸውን  አላረጋገጠላቸውም፤አሁንም የተሻለ መሳሪያ ያስሳሉ፣ይፈልጋሉ።ከነዚህ ውስጥ በአገራችን ስልጣን ላይ የወጡትና በስልጣን ሽኩቻ የተለያዩት አምባገነን የጎሳ ድርጅቶች ጃብሃ፣ ሻእብያ፣  ወያኔና፣ኦነግ እንዲሁም ሌሎች  በኢሕአዴግ በሚል ስም የተሰባሰቡት አጫፋሪዎች ናቸው። የከበርቴ አገራት መሳሪያ የሆኑት ያገር ውስጥ ጎሰኞች ብቻ ሳይሆኑ የጎረቤት አገሮችም ሱዳንና ሶማሊያ የዚህ አድማ ተባባሪዎች ነበሩ አሁንም ናቸው።ጅቡቲም የራሷን  ድርሻ ተጫውታለች አሁንም እየተጫወተች ነው።ለተገንጣይ ሃይሎች የገንዘብ፣የመሳሪያና መጠለያ እንዲሁም የመረጃና ሎጅስቲክስ እርዳታ በመስጠት ለስልጣን አብቅተዋቸዋል።ለወዲፊቱም ለታቀደው ኢትዮጵያን የማፈራረስ የጋራ አድማ የሚቻላቸውን ከማድረግ አይመለሱም።


 የምዕራቡ ከበርቴ ዓለም በተለያዩ ጊዜዎች ስምና መልኩን እየቀያየረ መጥቷል፤የዘረፋ ዓላማውን ግን አልቀየረም።አሁን ግሎባላይዜሽን ብሎ የፈጠረው ፈሊጥ በዚያው የዘረፋ ማህጸን ውስጥ የተወለደ የዘመኑ ወረራ ነው።እንደስሙ የዓለምን ሕዝብ በአንድ እድገታዊ ደረጃና ነጻነት ረድፍ ውስጥ የሚያስገባ ሳይሆን ለማይጠግቡት የከበርቴ ስርዓት ተጠቃሚዎች የዘረፋ መብትና ዕድል በስፋት የሚከፍት ዘዴ መሆኑ መታወቅ አለበት።በዚህ ዓለም አቀፍ የዘረፋ ውድድር ውስጥ በአንድ ወቅት በሶሻሊዝም ስም ዘረፋን ይታገሉና ይቃወሙ የነበሩ አገሮች በተለይም ቻይና ከነበራት የፖለቲካ መስመር እርቃ የከበርቴው የዘረፋ ተወዳዳሪ ሆናለች።እሷም ለጥቅሟ የሚቆሙትን በመርዳት ትልቅ ደባ በመስራት ላይ ነች። ለዚህ ደግሞ ሊያገለግሉ የሚችሉ ቡድኖችን አዘጋጅቶ ስልጣን ላይ እንዲወጡ ማድረጉ ቀላሉ ዘዴ ነው።በዚያም አንጻር በኢትዮጵያና በሌሎቹም ያፍሪካ አገሮች የተሳካ ስልት ሆኗል።የኸው የግሎባላይዜሽን መርሆ ዘረፋውን ለማስጠበቅ በጦር ሃይልም እንደሚጠቀም በተለያዩ አገሮች ውስጥ የተካሄደውንና በመካሄድም ላይ ያለውን ጦርነት እያዩ መረዳት ይቻላል።በሰላምና ፣በዲሞክራሲ ስም ሰርጎ በመግባት አገራት ሰላምና አንድነት እንዳይኖራቸው ተሰባብረው ጥገኛ ሆነው እንዲቀሩ የማድረጉ ስልት የዛው የዘረፋው አካል እንደሆነ መታወቅ አለበት።አገራት እራሳቸውን ችለው ለማደግ በቅድሚያ ነጻነታቸውን ማስከበር ይኖርባቸዋል።ተለጣፊ በመሆን የማደጋቸው ዕድል የመነመነ ነው።አገር ወዳድ  መሪዎች ለአገር እድገትና ነጻነት ካሰቡና ከቆሙ  የህዝባቸውን መብት ማክበር፣በአገራቸው የተፈጥሮ ሃብት ላይ የመወሰንና የመጠቀም የባለቤትነት መብታቸውን አሳልፈው አለመስጠት፣ ከቀጨጨ የክልል ጥቅም፣ ስሜትና እይታ ተላቆ አገራዊ (ብሔራዊ)በራስ የመተማመን ስሜቱ እንዲጎለብት ማደረግ ለእድገቱና ለነጻነቱ ዋስትና ነው።በውጭ ካፒታል ብድርና እርዳታ መተማመን የነጠፈ እለት ባዶ እጅ መቅረት ይሆናል።ከዛም በላይ ከፍለው የማይጨርሱት ዕዳ ውስጥ መዘፈቅ ነው።ለክፍያ ሲባል የአገርን አንጡራ ሃብት አሳልፎ እስከመስጠት ይደርሳል። የውጭ ዘራፊ ሃይሎች አንዱ አገልጋይ ተዳክሞ ጥቅማቸውን ማስገበር ካልቻለ እሱን ጥለው ሌላ ለመተካት ዓይናቸውን አያሹም።ጦርነት ቀስቅሰው አገር ከማፈራረስ አይመለሱም።ይህ በያገሩ የታዬ የመገለባበጥ ስልት ነው።በአገራችንም የማይሆንበት የለም።ይህ ከመሆኑ በፊት አገር ወዳዱ አደጋውን ለመቋቋም ነቅቶና ተደራጅቶ መጠበቅ አለበት።ሕዝብ የስልጣኑ ባለቤት ለሚሆንበት የጋራ ትግል መሰለፍ የያንዳንዱ አገር ወዳድ አላፊነትና ግዴታ ነው። የዘረፋና የባርነት መሳሪያ ለመሆን በሕዝብ መብትና በነጻ አውጭነት ስም የተለያዬ ባንዲራ ሰፍተው ተደራጅተው ጊዜ የሚጠብቁ መኖራቸውን አውቆ እንዳይሳካላቸው ማድረግ ይኖርበታል።  
           

የግራው፣ የሶሻሊስት(ኮሚኒስት)ፍልስፍና« የዓለም ስራተኞች ተባበሩ!፣ ዓለም የሰራተኞች ትሆናለች!»  በሚለው ንድፈ ሃሳብ ዓለም አቀፋዊነትን እንጂ ጎሰኝነትን የሚያራምድ ጠባብ እይታ አልነበረውም።የአፍሪካን፣የደቡብ አሜሪካን፣የኤሽያን አገሮች  ህዝብ ከነጮች የቅኝ ግዛት ምዝበራና ጭቆና ለማላቀቅ እንጂ አገራትን በመሰባበር የመንደር መንግስታት ተቋቁመው ህዝብ እርስ በራሱ እንዲተላለቅ የሚቀሰቅስ ተልእኮ አልነበረውም።የሁሉም ሰራተኛ መብት እንዲጠበቅና እንዲከበር እንጂ በጎሳ አንጻር እያዬ ችግሩን የሚያባብስ አልነበረም።ትግሉ የዓለም ሰራተኞችን ከዓለም አቀፍ ብዝበዛ ለማላቀቅ የሚደረግ ትግል ነበር እንጂ የሰራተኛው መደብ በጎሳና በሃይማኖት ተከፋፍሎ እርስ በርሱ እንዲተላለቅ የሚያስተምር አልነበረም።የጎሳና የሃይማኖትን ልዩነት ተጠቅሞ የሰራተኛውን መደብ የሚያፋጀው የከበርቴው መደብ ስርዓት  ነው።ሆኖም ግን  በሶሻሊስቱ ርዕዩት ስም ስልጣን ላይ የወጡ አምባገነኖች በፈጸሙት ግፍና በደል እንዲሁም በጸረ ሶሻሊስቶቹ ጎራ በከበርቴው ስርዓት አፍቃርያን  ያላሰለሰ ፕሮፓጋንዳና ጦርነት  የተነሳ ህዝብ እንዲጠላውና እንዲፈራው ሆኖ   በመጨረሻውም ተንኮታኮተ።በሶሻሊስቶች ትግል ተከብሮለት የነበረው መብቱ ቀስ በቀስ እይተሸረፈ የአሰሪው መደብ እንደፈለገው የሚያሽከረክረው ዕቃ ሆነ፣ ቦታውን  በግለሰብ ነጻነት ስም ዘረፋ የሚያራምደው የኔዎሊበራል የፖለቲካና የኤኮኖሚ ርዩተዓለም  ሙሉ ለሙሉ ተቆጣጠረውና አሁን ዓለም ወደ ምትገኝበት ምስቅልቅል ሁኔታ ገባች።ጥቂቶች የሚንደላቀቁባት፣ ገደብ የለሽ ሃብት የሚያግበሰብሱባት፣ብዙሃን ለልዩ ልዩ ችግር የተጋለጡባት ሆነች። ህዝቡ በተለያዩ ችግሮች ውስጥ ተማግዶ ወደራሱ ብቻ እንዲመለከት፣ አዲሱ ትውልድም ተስፋው  ጨልሞ ፣ በመኖርና ያለመኖር መካከል አጣብቂኝ ውስጥ ገብቶ  ከጥቂት አገር ወዳዶች በስተቀር  በእራስ ወዳድነት በሽታ ተለከፈና  አገራዊና ህዝባዊ ስሜቱ ተፍረከረከ። እንኳንስ ለአገር ለቤተሰቡ የማያስብ ሆነ።ሰብአዊ ስሜቱ ወደአውሬ ጸባይ ተለወጠ። ትልቁም ትንሹም በእራስህን አድን እሩጫ ተጠመደ።በዓለም አቀፍ ደረጃ የዘረኝነት ስሜት አቆጠቆጠ።አቅጣጫው ካልተለወጠ ዓለማችን ከባሰ ምስቅልቅል ሁኔታ ውስጥ መገባቷ አይቀርም።ያንን አደጋ ለመከላከል የሚረዳው መሳሪያ በየአገሩ ዘረኝነትን፣ጎሰኝነትን፣ግለኝነትን መታገልና ማሸነፍ ነው። ከተለያዩት ስርዓቶች ውስጥ መልካሙን በመውሰድና መጥፎውን በመጣል አሁን ላለነበት ምስቅልቅል የዓለም ችግር መፍትሄ ሊሆን ይችላል። በአገራችንም ሰፍኖ ያለው ችግር ከዚህ አኳያ መታዬት ይኖርበታል።          

በአገራችን ውስጥ የጎሳ  ድርጅት ፈጥረው ህዝቡን የሚያተራምሱት ምሁራን ነን ባዮች «የብሄር መብት እስከመገንጠል» የሚለውን መፈክር በማጣመም የልዩነት ግንብ ገንብተው ህዝብ እርስበርሱ እንዲተላለቅ የተገለገሉበትና ወደፊትም ሊገለገሉበት እላይ እታች በማለት ላይ ይገኛሉ። በኢትዮጵያ ውስጥ እነሱ ያገኙትን ዕድል ሌላው እንዳይደርሰው ፤ወንዝ ተሻግሮ ከሌላው ወገኑ ጋር እንዳይግባባ፣በፈለገበት ቦታ ኑሮ እንዳይመሰርት፣እውነተኛ ታሪኩን እንዳያውቅ ታውሮና በጠባብ መሬት ላይ ተከንችሮ በነሱ መዳፍ ስር ወድቆ በድህነት እንዲማቅቅ፣ከሌላው ወገኑ ጋር እየተጫረሰ ዕድሜ ልኩን ከቀውስ እንዳይወጣ የሚያደርገውን በተቆርቋሪ አንደበት የሚረጩትን መርዝ መቋቋምና መታገል፣ የነሱ ሰለባ ሊሆን የሚችለውን ኢትዮጵያዊ ማዳን፣ የሁሉም ኢትዮጵያዊ ግዴታ  ነው።እነዚህ በጠባብ ፍልስፍና የታወሩ ጎሰኞች አብዛኛዎቹ አንድነቱ በተጠበቀ፣ሰፊና ሃብታም አገር  በድሎት እየኖሩ የአንድነትን ጥቅም በማስተማር  የተወለዱበትን ደሃ አገርና ህብረተሰብ  ከመጥቀም ይልቅ የኢትዮጵያ ጠላቶች ለሚወረውሩላቸው ፍርፋሪ ተገዥ በመሆን ልዩነትን እያራገቡ ከባሰ ቀውስ ውስጥ እንዲገባ ሲጥሩ ማየት ከማሳዘን አልፎ ያሳፍራል።ኢሰብአዊነትም ነው። ስለሆነም ነው በተባበሩት መንግስታትና በአፍሪካ ህብረት ደንብና ህግ አገራትን በጎሳ መከፋፈልና መገንጠል ወንጀል ሆኖ በሚከተሉት አንቀጾች  የሚወገዘው።
የተባበሩት መንግስታት በሴፕቴምበር 14 ቀን 1960 በቻርተሩ አንቀጽ ቁጥር 1514 ባሰፈረው የራስን ዕድል የመወሰን መብት ሲቀበልና ሲያጸድቅ  የወሰደው ግንዛቤ ከቅኝ ግዛት ማላቀቅ(decolonization )ሂደትና ዓላማ ጋር የተሳሰረ እንደሆነ ያመለክታል።ይህንኑም ሲያብራራው የውጭ ተጽእኖ ሳይኖር፣የሕዝቡ ፍላጎት ሙሉ ለሙሉ በነጻ የሚከበርበት ጎሳ(race)እምነት (creed) ቀለም(colour) መሰረት ያላደረገ ፣ሁሉም በጋራ የሚረካበት የጋራ የሆነ የሕዝብ ውሳኔ እንደሆነ ያረጋግጣል።ለጋራ ሰብአዊ መብት መከበር እንጂ ለአንዱ ዘር ወይም ጎሳ ቅድሚያና እውቅና አይሰጥም፤አንዱን ከሌላው ነጥሎ ለመጉዳት ወይም ለመጥቀም አይሞክርም።በዓለም አቀፉ ህግ መሰረት አገራት ከቅኝ አገዛዝ መዳፍ ስር ተላቀው የራሳቸውን መንግስት የማቋቋም መብታቸውን ማወቅ ማለት በአንድ አገር ውስጥ የሚኖሩ የተለያዩ ጎሳና ነገዶች ከአንድ አገር ተገንጥለው የራሳቸውን ድንበር አስምረውና ሸንሽነው የራሳቸው የሆነ መንግስት እንዲያቋቁሙ የሚፈቅድላቸው አይደለም።  

ይህንንም በሚከተለው ሃረግ ያስቀምጠዋል። "To concede to minorities,either of language or religion,or to any fractions of population the right of withdrawing from the community to which they belong,because it is their wish or their good pleasure,would be to destroy order and stability within states and to inagurate anarchy in international life,it would be to uphold a theory incompatible with the very of the state as a territorial and political unity." 


በአማርኛ በአጭሩ ሲተረጎም "ለጥቂቶች ደስታና እርካታ እንዲሁም  ጥቅምና ፍላጎት በማጎብደድ በቋንቋና በሃይማኖትም ሆነ በሌላ ሰበብ ካሉበትና ከኖሩበት አገርና ማህበረሰብ ተገንጥለው ለመኖር የሚጠይቀውን ሃሳብ መቀበል ሕገደንብ ተጥሶ አለመረጋጋት እንዲከሰትና ስርዓተ አልበኝነት እንዲነግስ ያደርጋል።ዓለም አቀፋዊ ህይወትንም ይጻረራል።ከሃገር የግዛትና የፖለቲካ አንድነት ጋር የማይሄድና የማይጣጣም ጎጂ አቅጣጫ ነው"ይለዋል።


ቀጠል አድርጎም በዚሁ አንቀጽ ስር በቁጥር 6 ላይ  የሚከተለው ስፍሯል።"Any attempt aimed at the partial or total disruption of the national and territorial integrity of a country is incompatible with the purposes and principles of the charter of the united nations"


ባጭሩ ሲተረጎምም "የአገራትን ብሔራዊ አንድነትና ዳር ድንበር የሚያፋልስ ሙከራ ከተባበሩት መንግስታት ዓላማዎችና ህጎች ጋር ተጻራሪ ነው።"ይላል።


ድርጅቱ በ1970 ዓ,ም ባወጣው ተጨማሪ ህግ የሚከተለውን አስቀምጧል "A state will not be considered to be representative if it formally excludes a particular group from participation in the political process,based on that group"s race,creed or colour"


ሲተረጎም"አንድ መንግስት ሌላውን በጎሳ ማንነቱ፣በዕምነቱም ሆነ በቆዳው ቀለም ምክንያት በፖለቲካው ህይወት  ውስጥ በእኩልነት ደረጃ የማያሳትፍ ከሆነ የጋራና ሁሉንም የሚወክል መንግስት ነው ተብሎ አይቆጠርም።"


የአፍሪካ ህብረትም በዚህ የብሔር የራስን መብት እስከመገንጠል የሚለውን የጎሰኞች መፈክር በሚከተለው የድርጅቱ መመሪያና አቋም ይኮንነዋል።


"Rejecting any right to secession from existing states as reflecting the right of a state to be free from outside interference rather than as an ethenicaly specific right for a group to choos its own political status"


"አገራት ከውጭ አገር ተጽእኖና ቅኝ አገዛዝ ስር ተላቀው የራሳቸውን ዕድል ለመወሰን ያላቸው መብት ማወቅ ማለት በአንድ አገር ውስጥ የሚኖር ማህበረሰብ በጎሳና በሌላውም ምክንያት ተገንጥዬ የራሴን መንግስት ላቋቁም ለሚለው  ተመሳሳይ እውቅና ይሰጠዋል ማለት አይደለም።"ብሎ ያስቀምጠዋል።


የተባበሩት መንግስታት ድርጅትም የሚቀጥለውን ተጨማሪ ደንብ አጽድቋል።



 "Self determination remains a rhetorical tool utilized by groups within states seeking independence,autonomy,or simply a grreater degree of controle over issues that directly affect them.Many of these groups share ethenic,lingusistic,or other characterstics,but the international law of self determination as opposed to a few-non binding declarations and recommendations has never accorded to such groups any special right of self governance."


"According to article 46 ,in which the oft-repeated phrase regarding territorial integrity is repeated."nothing in this declaration may be interpreted as implying for any state,people,group or person any right to engage in any activity or to perform any act contrary to the chapter of the united  nations as authorizing or encouraging any action which would dismember or impair,totally or inpart,the territorial integirity or political unity of sovereign and independent states."


በ2007 ዓ,ም ስብሰባም ላይ የሚከተለውን ውሳኔ በቁጥር 61/295 አንቀጽ 4  "Indigenous people in exercising their right to self-determination have the right to autonomy or self government in matters relating to their internal and local affairs as well as ways and means for financing their autonomous functions"



በነዚህ ከዚህ በላይ በሶስት ክፍሎች የተጠቀሰው ውሳኔ በአጭሩ ሲተረጎም


"የራስን ዕድል መወሰን የሚለው ቅላጼ ብዙውን ጊዜ የሚስተጋባው በአንድ አገር ውስጥ የሚኖሩ የበላይነትን ለመያዝ በሚፈልጉ ቡድኖች ነው።የዚህ ቡድን አባላት የጎሳ ማንነትን፣ቋንቋንና ሌላም መለያዎችን የሚጋሩ ቢሆኑም የዓለም አቀፉ ሕግ የራሳቸውን መንግስት እንዲያቋቁሙ አይፈቅድላቸውም።በአንቀጽ 46 የተጠቀሰውም የአገርን አንድነትና ዳር ድንበር መከበርን በማጉላት ማንኛውም አገር፣ሕዝብ፣ቡድንም ሆነ ግለሰብ የአገርን አንድነትና ዳርድንበር በሚያፈርስና የፖለቲካን ውህደት በሚያናጋ መልኩ የራስን ዕድል መወሰን መብት በሚል ሽፋን የሚደረግን ሙከራና ጥረት እንደማይቀበለው በግልጽ አስቀምጧል።ሆኖም ግን በ2007 ዓም በአንቀጽ 61/295 በቁጥር 4 ላይ  ባሳለፈው ውሳኔ ነዋሪው ሕዝብ የራሱን አስተዳደር የመመስረትና በከባቢው ጉዳዮችና የገነዘብ ነክ ጥያቄዎች ላይ የመወሰን መብት እንዳለው አረጋግጧል።


በተባበሩት መንግስታት ድርጅትም ሆነ በአፍሪካ ህብረት ቻርተሮች በተደጋጋሚ በወጡት ህጎችና ደንቦች ለማየት የምንችለው የጎሳ ማንነት የአገርን አንድነትና ብሔራዊ ማንነትን ሊስተካከልና ሊወዳደር ብሎም ሊቀናቀን እንደማይገባው ነው።ኢትዮጵያውያንም ያለብንን የጋራ ችግር በጋራ እንድንወጣው የሚመክርና የሚያሳስብ መመሪያ ነው።የከባቢም ሆነ የጎሳ  ባህል፣ እምነታችንና ጥቅማችን  ተከብሮልን በአገር አቀፉ መንግስታዊ መዋቅር ውስጥ አንድንሳተፍ መብታችንን የሚያረጋግጥልን ነው።በጫጨ ኤኮኖሚና በጠባብ ክልል ውስጥ መታሰርን አሶግዶ የትልቅ አገር ባለቤቶች የሚያደርገን ሕግ ነው።


በተግባር የሚታየው ግን ይህን ሕግ ተስማምተው የፈረሙ አገሮች ሕጉን እየጣሱ በአገራት የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ እየገቡ ፣ጥቅማቸውን ለማስከበር ድንበር ጥሰው ወረራ በማካሄድ ወይም  የእርስ በርስ ግጭትና ቀውስ በመፍጠር ፣ከፋፍሎ በማጫረስ ተንኮል ላይ ተሰማርተው ይገኛሉ።በዚህ እኩይ ተግባር አገራት ተሰባብረዋል።ሕዝቦች ተጨፍጭፈዋል፤ተፈናቅለዋል፤ተሰደዋል።የእኛም እጣ ፈንታ ይኸው ሆኗል።የወደፊቱ ትውልድ አገረ ቢስ እንዳይሆን ከፈለግን የአንድነታችንና የሰላማችን ጸር የሆነውን የጎሳ ፖለቲካና ጎሰኞችን ከሚከተሉት የአጥፍተህ ጥፋ ጎዳና ስናስወግዳቸው ነው።ያ ደግሞ የአንድነት ሃይሉ አላፊነት ነው።


በአለፉት ሃምሳ ዓመታት የታዩት የትውልዱ ስህተቶችና ጥፋቶች በብሔር፣ብሔረሰብና በብሔር የራስን ዕድል በራስ የመወሰን ዙሪያ የተከሰተው የትርጉምና የግንዛቤ ስህተት ነው።
ከላይ በተቀመጠው የሶሻሊስቶቹም ሆነ የተባበሩት መንግስታትና የአፍሪካ ህብረት ትንታኔ፣ብሎም በዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ግንዛቤና ተለምዶኔሽን(Nation) ማለት አገር፣ናሽናሊቴ(nationality) ማለት ዜግነት፣(ethnics,tribe or clan)ጎሳ ወይም ነገድ (community) ማህበረሰብ(society) ህብረተሰብ እንደሆነ መቀበልና እነዚህን ስያሜዎችም በአግባቡ መጠቀም አለብን። ኔሽን የሚለው ቃል አገራዊ  አጠራር መሆኑን  የሚያሳዩት ተጨማሪ ስያሜዎች ደግሞ የሚከተሉት ናቸው።  


ዩናይትድ ኔሽንስ =የተባበሩት መንግስታት ወይም የተባበሩት አገሮች፣ናሽናል አንተም=ብሔራዊ (የሕዝብ) መዝሙር፣ናሽናል አርሚ=ያገር መከላከያ ሰራዊት ፣ናሽናል ቲም=ብሔራዊ/አገራዊ ቡድን----እያለ ይቀጥላል።እነዚህ አጠራሮች ከጎሳ ጋር  በምንም መልኩ የተያያዘ ትርጉምና አጠቃቀም የላቸውም። ጎሰኞች ግን የሚኖሩበትን አካባቢ አገር አድርገው ሊጠቀሙባቸው ይፈልጋሉ።ያ ከሆነ ደግሞ አትዮጵያ  በሰማንያ ጎሳ ትቆራረሳለች ማለት ነው።የተባበሩት መንግስታትም የተባበሩት ጎሳዎች በሚል ይለወጣል ማለት ነው ።በመካከሉ የውቅያኖስ ባህር ለያይቶት በ12000 ደሴቶች  የሚኖር፣ ከሁለት መቶበላይ  ቋንቋዎች የሚናገር፣ ከሁለት መቶ ሚሊዮን በላይ ሕዝብ ያላት ኢንዶኔዚያ በአንድ ሰንደቅ ዓላማና ማእከላዊ መንግስት በምትተዳደርበት ዓለም ውስጥ እየኖሩ ለዘመናት በአንድ የተያያዘና ኩታገጠም መሬት ላይ አብሮ የኖረና በትውልድ ሃረግ የተሳሰረ ህዝብ የሚኖርባትን ኢትዮጵያን ለማፈራረስ መቅበጥበጥ ከእብደትም በላይ እብደት ነው።  

  
 በተለይም በተማሪው እንቅስቃሴና በፖለቲካው ትግል አለም ውስጥ የተሰማራነው  በተራማጅ ጭንብል የጎሰኞች ዓላማ አራማጅ በመሆን የፈጸምነውን ስህተት ማረምና ማስተካከል ይኖርብናል።መንደራቸውን አሳብጠው የአገር መልክ በመስጠት በአገር ደረጃ ታውቆ ነጻነት አውጆ ለመኖር የሚደረግ ደባቸውን ማውገዝ ብቻ ሳይሆን መከላከል ይኖርብናል። በአገርነት የምትታወቀውና የረጅም ታሪክ ያላት አገር ኢትዮጵያ ነች።በውስጧ ያሉት ማህበረሰቦች፣ጎሳዎችና ነገዶች የዚች አገር አካል እንጂ እራሳቸውን ችለው ያልኖሩ፣ሊኖሩም የማይችሉ  በሃገርነት እውቅና የሌላቸው ክፍለሃገሮች ናቸው።ጎሰኞች በሚናገሩት ቋንቋ ብቻ የራሳችን ነው የሚሉትን ክልል እንደ ሃገር መቁጠርና የራሳቸውን ዕድል እስከመገንጠል ድረስ መብት እንዳላቸው ማወቅ ኢትዮጵያውያንን  እንደ ባህር ተሻግሮ የመጣ  ወራሪ ሃይል መቁጠር ይሆናል።በታሪክ ኦሮሞ፣ አማራ፣ ትግሬ፣ ወላይታ፣ሃረሬ ሲዳማ...የሚል አገርና ዜግነት አልነበረም አሁንም የለም።ወደፊትም ሊኖር አይገባውም።የነበረው፣ያለውና የሚኖረው ኢትዮጵያ የምትባል አገርና ኢትዮጵያዊ የሚል ዜግነት ብቻ ነው። ለዚያ መቆም ማለት ለህልውናና ለማንነት መቆም ማለት ነው።ያንን ማንጸባረቅና ለዚያ ሃቅ መቆም ኳላ ቀርነትና ያለፈ ስርዓት ናፋቂነት መሆን አይደለም። በሃሰት የጎሰኞች  መጋዝ እየተገዘገዘ ሊወድቅ የሚንገዳገድን ማንነት ማዳን ማለት ነው።አገርና ትውልድን ከጥፋት መታደግ ማለት ነው።በትልቅነት ማመን የስልጣኔ ምልክት ነው እንጂ ዃላ ቀርነትና ያለፈ ስርዓት ናፋቂነት አይደለም።ዃላቀርነት በትንሽነትና በዘመነ መሳፍንት አስተሳሰብ መዳከር ነው።


በሌላውም በኩል የሚታየው የስያሜና  የቃላት ግድፈት መታረም የሚኖርበት ሕዝብና ሕዝቦች የሚሉት ቃላት ናቸው።የአንድ አገር ዜጋ ወይም ነዋሪ ሕዝብ እንጂ ሕዝቦች ተብሎ አይጠራም።ሕዝቦች የሁለት የተለያዩ አገሮች ተወላጅና ነዋሪ የሆኑትን ለመለየትና ለማሳየት የሚገለገሉበት አጠራር ነው።በአንድ አጠቃላይ ግዙፍ አገር ወይም ዓለም ወይም ክፍለ ዓለም የሚኖር ሕዝብ ይባላል ወደ አገራት ዝርዝር ሲገባ ደግሞ ሕዝቦች ይባላል።የኢትዮጵያ ሕዝብ፣የሱዳን ሕዝብ ይልና የሁለቱን አገር ሕዝብ በጥምር ሲጠራ የኢትዮጵያና የሱዳን ሕዝቦች ሊል ይችላል ማለት ነው።የዓለምን ፣የአፍሪካን የአውሮፓን ሕዝቦች በተናጠል ሲጠሩ ግን የአፍሪካ ሕዝብ።የዓለም ሕዝብ፣የአውሮፓ ሕዝብ እያለ ይጠራል ማለት ነው።ይህንን  አሰያየም  በማወላገድ እራሳቸውን የአንድ አገር ሕዝብ አስመስሎ ለማቅረብ ሲሉ ተገንጣይ የጎሰኞች ቡድኖች ያካባቢያቸውን  ነዋሪ ከሌላው በሚለየው መልኩ  ሕዝብ በማለት ሲያቀርቡ የተሳሰረበትን የአንድ ሕዝብነት ሰንሰለት ለመበጠስ ሲሉ ሕዝቦች የሚለውን አጠራር ይጠቀማሉ።ስለሆነም በኢትዮጵያ ና በህዝቧ አንድነት የምናምን ዜጎች ሕዝብ የሚለውን ስያሜ ማስተጋባት ይኖርብናል።በመካከላችን የዜግነት ልዩነትም ስለሌለ ሕዝቦች እያልን እራሳችንን ማለያየት አይኖርብንም።ሕዝቦች የሚለው አጠራር የሚበታትነንና የሚለያየን የተገንጣዮችና የጎሰኞች የስነልቦና ሰለባ ስልት ነው።
  

ያጣነውን ለማግኘትና የያዝነውን ለማስከበር የግድ ጠንካራ እምነትና ሃይል መገንባት ያስፈልገናል።ቻይና በአቋሟ ጥናትና በገነባችው ብሔረተኝነትና  የኤኮኖሚና ወታደራዊ ሃይል ከመቶ አርባ ስድስት ዓመት በፊት በእንግሊዞች ተቀምታ የነበረውን የሆንግ ኮንግ ግዛቷን አስመልሳለች።ከሰባ ዓመት በፊትም እንደ ሻእብያ ባለ የራሷ ተገንጣይ በጀነራል ሻንጋይሸክ  የተገነጠለችውን ታይዋንን መልሶ ለማቀላቀል ጥረትዋን አላቆመችም። ከእናት አገር ቻይና  ለመቀላቀል የሕዝቡም አዝማሚያ እያጋደለ መጥቷል፤የጊዜ ጉዳይ ነው በተግባር መታየቱ አይቀርም።እኛም ኢትዮጵያውያን የዓላማ ጥናት ካለን ለተመሳሳይ እድል ባለቤቶች ለመሆን የሚያግደን የለም። የድህነትንና የጎሰኝነትን ግንብ ካፈረስን እንኳንስ የውስጡ የውጩም ኢትዮጵያዊነትን ይሻል።
   
      
የአንድነት ሃይሎች መመዘኛው ምንድን ነው?

1-የኢትዮጵያን አገራዊ አንድነት መቀበልና ከማንኛውም አይነት አደጋ መከላከል፣ብሄራዊ መግለጫ የሆነውን አረንጓዴ ቢጫ ቀይ ሰንደቅ ዓላማ ብቸኛ አድርጎ ማውለብለብ

2-  በኢትዮጵያዊነት ማመን፣በአደረጃጀትም ሆነ በስያሜ ኢትዮጵያዊነትን  አጉልቶ ማሳየት፣

3-ከቅድመ ወያኔ በዓለም አቀፍ ደረጃ(በተባበሩት መንግስታትና በአፍሪካ አንድነት)እውቅና የነበረውን የኢትዮጵያን ዳር ድንበር  ለማስከበር ቁርጠኛ መሆንና በተግባር ማሳዬት።በህገወጥ መንገድ በጉልበትና በውጭ ሃይሎች አሻጥር የተገነጠለውን የኤርትራ ጠ/ግዛት ሌላው ቢቀር እንደ ነጻ አገር እውቅና አለመስጠት።የህዝቡን መልሶ መዋሃድ በሚረዳ መልኩ ሰላማዊ ትግል ማካሄድ።የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነቱን ማዳበር። 

4-ኢትዮጵያንና ህዝቡን  ማእከል ያደረገ  ማህበራዊ፣ፖለቲካዊ፣ምጣኔሃብታዊ፣ወታደራዊ-- ወዘተ ተቋማትን ለማነጽ  ለእድገትና ለሰላም የሚያበቃ መርሃ ግብር መንደፍና  በተግባር ለመተርጎም መንቀሳቀስ።

5-በጎሳና በሃይማኖት ስምና እረድፍ አለመደራጀትና አገሪቱን በዚያ መልክ የማካለሉ ሂደት ያደረሰውንና ወደፊትም ሊያደርስ የሚችለውን መዘዝ ተረድቶ ለመከላከል ቁርጠኛ መሆንና በተግባር ማሳየት።

6-ላለፉት ሃምሳ ዓመታት በትውልዱ አዕምሮ ውስጥ የተተከለውን በዲሞክራሲና በብሄር መብት ስም የዳግማዊ ዘመነ መሳፍንትን ጸረ አንድነትና ጎሰኝነት አስተሳሰብ  ነቅሎ ለመጣልና ለማምከን የጎሰኝነት ዝንባሌና አቋም ይዘው የተደራጁትን መታገል።

7-በስልጣን ላይ ያለው ወያኔ መራሹ የኢሕአዴግ  ቡድን ስልጣኑን የያዘው በህዝቡ ነጻና ዴሞክራቲክ ምርጫና ውሳኔ ሳይሆን  በጉልበት ስለሆነ የሚያወጣው ህግ፣ የሚወስደው ውሳኔና የሚያደርገው ውል  ሁሉ ህጋዊነት እንደሌለው ማመንና ስርዓቱን ለማሶገድ ጠንካራ የአንድነት ሃይል ግንባር መመስረት፤ በጎሳና በክልል ተዋረድ ሳይሆን አገር አቀፍነትና ሰብአዊነት ያለው፣ብሔራዊ ነጻነትንና ጥቅምን በሚያስከብር በፖለቲካ ርዩተዓለም ላይ መሰረት ያደረገ ስርዓትና የፖለቲካ ባህል ማስፈን።የጎሳን የተረኝነትን ስሜትና የሥልጣን እርክክቦሽ ለአንዴና ለሁሌውም መስበር፤


8-እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ በጎሳ ማንነቱ  ሳይሆን በሰውነቱና በኢትዮጵያዊነቱ እኩልነቱ ተከብሮለት በፈለገበት ያገሪቱ መሬት የመኖር፣የመስራት፣ንብረት የማፍራት፣ባገሩ ጉዳይ ላይ የመወሰን፣የመምረጥና የመመረጥ  መብቱን ማወቅ፤የአገሪቱን የተፈጥሮ ሃብትና ግብአት ያለአድልኦ ለዜጎች ሁሉ  በሚጠቅመው መልክ የማዳረስና የማዋል ተልእኮን በተግባር ማረጋገጥ፤በልማት ስም የአገር ሃብት በባእዳን እንዳይዘረፍ፣በርካሽ ዋጋ እንዳይሸጥ እንዳይለወጥ መከላከል።


እነዚህ ከሞላ ጎደል ለአንድነት ሃይሎች የመመዘኛና የመሰባሰቢያ ነጥቦች ናቸው ብዬ አምናለሁ።
እነዚህንም የጋራ ዓላማዎች በተግባር ለመግለጽ የሚችል የሽግግር ጊዜያዊ መንግሥት ማቋቋም የግድ ይላል።ባለው የጎሰኞች ስርዓት በጎ ፈቃድና ፍላጎት የሚፈጸሙ አይደሉም። የሽግግር መንግሥቱም የህብረተሰቡን ስብጥርነት ያንጸባረቀ መሆን ይገባዋል።የወጣቱ፣የሲቪክ ማህበራት እንቅስቃሴዎችን፣አገር አቀፍ የተቃዋሚ የፖለቲካ ድርጅቶችን፣የሙያ ድርጅቶችን፣ የአዛውንትን፣ የሃይማኖት ተቋማትን፣ምሁራንን፣ሴቶችን ተወካዮች ያቀፈና ያሳተፈ መሆን አለበት።         


ከቅድመ ወያኔ በፊት የነበሩትን ስርዓቶች የመሩትና  የተጠቀሙበት ከሁሉም ጎሳ የተውጣጡ ጥቂቶቹ  እንደመሆናቸው መጠን የተጎዳባቸውም እንደዚሁ የሁሉም ጎሳ ተወላጅ የሆነው ብዙሃኑ ህዝብ  ነው።


አሁን በየጎሳው ስም ድርጅት ፈጥረው የአገሪቱን አንድነት የሚፈታተኑትን ተሸክሞ መሄድ ወይም የሚጠይቁትን ሁሉ መቀበል  እንደ ዲሞክራሲ መብትና ባህል ሊታይና ሊቆጠር  አይገባውም።ጸረ አንድነት ማለት ጸረ ህዝብ ማለት ነው።ጸረ ህዝብ መሆን ደግሞ ጸረ ዴሞክራሲ መሆን ማለት ነው።


ጎሰኝነት ወይም ዘረኝነት ሌላው ባህሪው ደግሞ ፋሽስትነት ነው።ሂትለር የዓለምን ህዝብ የጨፈጨፈውና እስከ አሁንም ድረስ ጠባሳው ያልጠፋው «የአርያን ምርጥ ዘር» የሚል ንድፈሃሳብ በመከተሉ ነበር።አሁንም የእሱ ተከታዮችና አድናቂዎች ያንን የዘረኛ መፈክር መመሪያቸው አድርገውታል።


በዕድሜያችን ካየናቸው የናይጀሪያ( ቢያፍራ)የሩዋንዳና ሶማሊያ አሁን በመካሄድ ላይ ያለው የደቡብ ሱዳን የርስ በርስ ጦርነት መነሻው ጎሳን መክንያት ባደረጉ ቡድኖች መሆኑን የሚክድና የሚዘነጋ የለም።  ታዲያ የጎሳ ፖለቲካ በየትኛው በጎ ገጹ ይመረጣል?   


ጎሰኞች የሚጠቀሙበት አንዱ መንገድ ህብረተሰብ ውስጥ የሚኖረውን  አንዳንድ መተራረብ፣ መናናቅና መተቻቸት  ነው። ይህ ደግሞ እንኳንስ በኢትዮጵያ በሰለጠኑትና ባደጉት የአውሮፓና የአሜሪካ ህዝቦች መካከል የተለመደ ነው።በየአገራቱ የሚኖረው ህዝብ የሰሜኑ በደቡቡ፣የምስራቁ በምእራቡ የአነጋገር ዘይቤ(ዲያሌክት)፣አለባበስና ባህል ይስቃል ፣ይቀልዳል።በሃይማኖትም ቢሆን ካቶሊኩ በፕሮቴስታንቱ፣ፕሮቴስታንቱ በካቶሊኩ ላይ ከመቀለድና ከመናቅ አልፎ ደም ተቃብተዋል፤ያም ሆኖ ግን አገራቸውን አላፈራረሱም።አብሮ መኖሩና መቀላቀሉ፣የአስተሳሰብ ለውጥ መምጣቱም የነበሩ ድክመቶችን ለማሶገድ ስለረዳቸው መናናቁ እየቀነሰና ከነጭራሹም እየጠፋ መጥቷል።የሁሉም ማንነት መግለጫ ሰውነታቸውና የአንድ አገር ዜግነታቸው ሆኗል። እኛም ከዚህ ተምረን ያለብንን ድክመት አሶግደን ከድህነት፣ ከስደትና ከግጭት ወጥተን የተሻለች ኢትዮጵያ ባለቤቶች ብንሆን ይመረጣል።የትልቅ አገርና የብዙ ህዝብ ጌታ መሆን ለተፋጠነ እድገት መስረት ነው። 


በጎሳ ድርጅት ውስጥ የተሰገሰጉት ወገኖቻችን ቆም ብለው ሊያስቡት የሚገባው ነገር ለጭቆናና ለድህነት የዳረጋቸው ኢትዮጵያዊነታቸው ሳይሆን በየጊዜው የሰፈኑት ስርዓቶች መሆናቸውን ነው።የስርዓቶቹ ባለቤቶች ከሁሉም ጎሳ የተውጣጡ እንደመሆናቸው በነዚያም ስርዓቶች የተጎዳው ሁሉም ያገሪቱ ዜጋ እንጂ አንድ ወይም የተወሰኑ ጎሳዎች ብቻ አልነበሩም።ለዚያም ነው «የአማራ  ስርዓት»ተብሎ የተፈረጀውን ስርዓት የአማራ ማህበረሰብ ተወላጆች ግንባር ቀደም ሆነው የታገሉት። ስለሆነም የሌላው ማህበረሰብ ተወላጆች የተጎዱት እነሱ ብቻ እንዳልሆኑና፣ ብቻቸውንም ከዚያ ችግር ሊወጡ እንደማይችሉ አውቀው ትግላቸውን  ከሌላው ወገናቸው ትግል ጋር ማስተሳሰር ይኖርባቸዋል። ትግሉ የሰባዊ(የዜግነት) መብትን ማስከበር ስለሆነ ክልል፣ሃይማኖት፣ቋንቋ፣ጾታና ዕድሜ አይለይም።ስለሆነም  የየጎሳው ተወላጅም  በስሙ  የሚነግዱትን የጎሳ ድርጅት መሪዎችና ዓላማቸውን አንቅሮ ሊተፉውና ሊታገለው ይገባል።የሌሎቹን ውጤት እያዬ ከዚያ ሊማር ይገባዋል፤ ከነተረቱ «ነደደችን ያዬ በሳት አይጫወትም» ይባላል።
  

ለህዝብ ኑሮ መሻሻልና ለህዝባዊ ስርዓት ባለቤትነት ዕድል ለመብቃት ከሁሉም ቅድሚያ መሰጠት ያለበት በወያኔና ግብረአበሮቹ የተዘረጋውን አጥፍቶ መጥፋት ጉዞ መከላከልና  ኢትዮጵያ  አገራችንን ማዳን ስለሆነ በኢትዮጵያዊነቱ የሚያምነው ዜጋ ለአገር አድን ትግሉ« የአገር ወዳዶች የጋራ ግንባር»በመፍጠር  ትግሉን ማቀናጀት ይጠበቅበታል።አሁን በየቦታው የተቀጣጠሉትን ህዝባዊ አመጾች ሰብስቦ ወደ አንድ ሃይል መለወጥ አማራጭ የሌለው ምርጫ ነው።በየቦታው ተበታትኖ ከመባከን በአንድ ዓላማ ላይ ያተኮረ ግንባር ፈጥሮ መታገሉ ውጤት ይኖረዋል።ለዚያም በመጀመሪያ የትግሉን ቅደም ተከተል ማወቅ ተገቢ ነው። አገር ሳይኖር የስርዓት ለውጥ ሊታሰብ አይችልም።ሌላው ሁሉ አገር ሲኖር ነው።ለአገር አንድነት ቅድሚያ ሊሰጠው ይገባል።ከዚህ የተሻለ ሌላ ምርጫ አይኖርም።ተገንጣዮች" ለነጻነት" ብለው ሃይል ሲሰበስቡና አንዳንዶቹም ሲሳካላቸው አገር ወዳዶች "ለአንድነት" በሚለው መፈክር ዙሪያ ሊሰበሰቡ ይገባል።ከተገንጣዮች የበለጠ ደጋፊ ያለው የአንድነቱ ጎራ መሆኑን ሊያውቁት ይገባል።የዲሞክራሲው ጥያቄም በሂደቱ ውስጥ ሊጎለብት ይችላል።በየጊዜውና በየቦታው ለተመሳሳይ ዓላማ የተለያዬ ስብሰባ ማካሄዱና ድርጅት መፍጠሩ መፍትሄ አይሆንም። ከፍ ብሎ ከ1-8 የአንድነት ሃይሎች መመዘኛ ሆኖ የቀረበው ዝርዝር ለግንባሩ ተሳታፊዎች የመሰባሰቢያ ዓላማ ሊሆን  ይችላል።


እድገትና ልማት ማለት ከቀጨጨ የጎሳ አስተሳሰብ መውጣት፣ እርሃብና ድህነትን አሸንፎ የህዝቡን  የኑሮ ደረጃ የሚሻሻልበት፣ጤናው የሚጠበቅበት፣የትምህርት ዕድል የሚስፋፋበት፣የሁሉም ዜጋ መብቱ፣ደህንነቱና ሰላሙ የተረጋገጠበት፣የከተማና የገጠር ልዩነት የጠበበበት ስርዓት ሲሰፍን ብቻ ነው።በውጭ አገር ብድርና እርዳታ ተገኝቶ ተዘርፎ በውጭ አገር ባንክ ከሚከማቸው  በተረፈው ገንዘብ  የከተማ እንብርቶች በሚሰሩ፣ ንብረትነታቸው የዚያው የስልጣኑ ባለቤቶች በሆኑ ህንጻዎች ብዛት፣ በሙስናና በአቀባባይነት በተሰማሩግለሰቦች የሚሽከረከሩ የሚያማምሩ መኪናዎች መኖር የጥቂቶችን የተሞላቀቀ ኑሮ እንጂ የብዙሃኑን ኑሮና  አገር አቀፍ እድገትን አያሳይም።የውጭ አገር ባለሃብቶችም የአገሪቱን ተቋማት በርካሽ እየገዙ ባለቤት መሆናቸው ና ኢኮኖሚውን መቆጣጠራቸው የጥገኝነት እንጂ  የልማትና የእድገት ምልክት አይደለም።


እዚህ ላይ ግን መገንዘብ ያለብን አንድ አገር ከሌላው አገር ተነጥሎ በራሱ ሊራመድ እንደማይችል ነው። ለሳይንስ እድገት፣ለተመክሮ ልውውጥ፣ለእድገትና ለሰላም በመከባበርና በጋራ ጥቅም ላይ የተመሰረተ ግንኙነት መኖር ተገቢና አስፈላጊ ነው።መከላከልና መቃወም የሚገባው አንዱ የበላይ ሌላው የበታች፣የዘራፊና የተዘራፊ፣የባሪያና የጌታ ግንኙነት እንዳይኖር ከማድረጉ ላይ ነው።  


 በአገራችን በተለይም በአዲስ አበባና በቀሩት ከተማዎች የህዝቡ ኑሮ ሲታይ ብዙሃኑ የበይ ተመልካች ሆኖ በኑሮ ውድነት የሚለበለብበትና ኑሮን ለማሸነፍ ሲል ባልባሌ ተግባርና ወንጀል የተሰማራበት፣ቤት አልባ ሆኖ በላስቲክ የተጠለለበት፣ ሁኔታ ጎልቶ ይታያል።ነጋዴው ሊከፍለው በማይችለው ግብርና የቤት ኪራይ ከንግድ ሥራው እንዲወገድ የማድረጉ ሴራ በገሃድ ሥራ ላይ ውሉዋል።ኪራይ ወይም  ግብር ለመክፈል ሲሄድ ኔትወርክ የለም በሚል ውሸት በማግስቱ እንዲመጣ ሲደረግ በማግስቱ ሲሄድ አንድ ቀን አሳልፈሃል ተብሎ በብዙ ሽህ የሚገመት ቅጣት እንዲከፈል  ይገደዳል።ከአስር ዓመት በፊት በሊዝ የገዛ የከተማ ቦታ ክፍያ ውል በተፈጸመበት የገንዘብ መጠን ሳይሆን አሁን ባለው የገንዘብ ግሽበት ሂሳብ እንዲከፈል አለበለዚያ የኖሩበትን ቦታና ቤት የሚያሳጣ አሰራር በመዘርጋቱ ኑዋሪውን ከባድ ችግርና ስጋት ላይ ጥሉዋል።ችግሩ እጥፍ ድርብ የሚሆነው ደግሞ በጎሳ ማንነታቸው ለጥቃት በተጋለጡት በተለይም በአማራው ማህበረሰብ  ተወላጆች ላይ ነው።


  ከታች እስከ ላይ የተስፋፋው ሙስና፣እራስንና ገንዘብ ወዳድነት፣ሴት አዳሪነት፣ስራ አጥነት፣ውሸት፣ስርቆትና ዘረፋ፣ ምግባረ ቢስነት፣ባህር ማዶ ተሻግሮ በየአረብ አገሩ ለባርነት ኑሮ መጋለጡ፣ስደቱ የዚያው የጎሰኝነት ስርዓት ውጤት ነው። የዚህ ሁሉ ተጠያቂው ጎሰኞች የፈጠሩት ወያኔ መራሹ የኢሕአዴግ  ስርዓት ነው።መፍትሔውም የጎሰኞችን ስርዓት መደምሰስና ዳግመኛ በኢትዮጵያ መሬት በውጭ ሃይሎች የሚረዳና ባንዳ   ቡድን ለስልጣን እንዳይበቃ ክፍተቱን በአንድነት አጥር መዝጋት ነው።  ያ ደግሞ ይቻላል!
አገሬ አዲስ