Saturday, May 8, 2021

ዘረኛ አምባገነን መንግሥትና እብድ ውሻ አንድም ሁለትም ናቸው አገሬ አዲስ Ethiopian Semay ሚያዝያ 28 ቀን 2013 ዓም(05-08-2021)

 

ዘረኛ አምባገነን መንግሥትና እብድ ውሻ አንድም ሁለትም ናቸው

አገሬ አዲስ

Ethiopian Semay

ሚያዝያ 28 ቀን 2013 ዓም(05-08-2021)

እብድ ውሻ በዬሄደበትና በዬደረሰበት ልሃጩን እያዝረከረከ የማይበክልው፣የማይነክሰው  እንሳም ሆነ ሰው የለም።በሽታው ባሳደረበት የአይምሮ መዛባትና ፍርሃት የተነሳ ከፊቱ የቆመውን ሁሉ ይነጅሳል፣ይለክፋል፣ በመጨረሻውም እንደተቅበዘበዘ ይሞታል።

 

በተመሳሳይ ደረጃም በአንድ አገር የሚነሳ  ዘረኛና ጸረ ሕዝብ የሆነ አምባገነናዊ መንግሥት ገና ከጅምሩ የብዙሃኑን ፍላጎት ይዞ ስለማይነሳ የተቃውሞ ጎራ አብሮት ይወለዳል።ዕድሜው እየጨመረ ሲሄድም የተቃዋሚው መጠንና ተቃውሞው ይጨምራል፤የዃላዃላም ለውድቀት ይዳረጋል።ያ ከመሆኑ በፊት ግን  ልዩልዩ ማታለያ ዘዴዎችን፣የሽብር ዛቻዎችን ተጠቅሞ የሕዝቡን ተቃውሞ ሊያለዝበው ይሞክራል።ተቃውሞው እዬበረታ ሲሄድም የአምባገነኑ መንግሥት ጭካኔና እብሪት እንዲሁ እዬጨመረ ይሄዳል።ምንም ጊዜ ቢሆን አምባገነኖች ከስህተታቸው ተምረውና ታርመው የሚሄዱ፣የሕዝቡን ፍላጎትና ጥያቄ የሚመልሱ የይሆኑም።  ትችትና ነቀፋን የሚሸከም  ተክለሰውነትና የሃሳብ ልእልና  ስለሌላቸውም ሁሉንም ችግርና የሕዝብ ጥያቄ በጉልበት ማርገብ ይመርጣሉ።የተሻለ ሃሳብ የሚያቀርቡና አቅጣጫ የጠቆሙ ሁሉ በጠላትነት ይፈረጃሉ። በጥፋት ላይ ጥፋት እዬጨመሩ የሽምጥ ይጋልባሉ፤ግልቢያው ግን ወስዶ ወስዶ ከማይወጡት ጉድጓድ ውስጥ ይጨምራቸዋል።የሚያሳዝነው ግን ብቻቸውን ሳይሆን አገርና ሕዝብ ጉድጓድ ውስጥ ይዞ ለመዝቀጥ  የማይራራ ልቦና ባለቤት መሆናቸው ነው።

 

 እውነተኛው ገጻቸው ሲታወቅ እንደ እብዱ ውሻ የማይለክፉት የህብረተሰብ ክፍል አይኖርም። ለእነሱ ከድጋፍና አምልኮ ሌላ የሚጥማቸው ነገር የለም።ሃሳብና ነቀፋ የሚያቀርቡ ወይም የተሻለ መንገድ የጠቆሙት ሁሉ ጠላቶቻቸው ናቸው።እነሱን ለማጥፋት የማይቀምሙት መርዝና የማይደረድሩት ሰበብ አይኖርም።

 

ጤነኛ  ወይም  አገር ወዳድ፣ሕዝብ አፍቃሪና አክባሪ የሆነ መንግሥት  ላይ ሕዝባዊ ተቃውሞ አይነሳበትም።ቢነሳበትም በጥበብና በእርጋታ ለጥያቄው መልስ ሰጥቶ ሕዝብን ያረጋጋል እንጂ አካኪ ዘረፍ ብሎ ለማጥፋት ወይም ለማፈን በፕሮፓጋንዳና በጸጥታ ሃይሉ ለማሸማቀቅ  አይቅበዘበዝም። በታሪክ  ተደጋግሞ እንደታዬው አምባገነን መንግሥታት ሲነሱ ሳይገባው አጨብጭቦ ወይም ፈርቶ በተቀበላቸው ሕዝብ ተቃውሞ ይወገዳሉ።መጨረሻቸው አያምርም።ከቶም ቢሆን እያጭበረበሩ በሥልጣን ላይ አይኖሩም።

 

ላለፉት ሰላሳ ዓመታት በተለይም ላለፉት ሦስት ዓመታት ስም እየቀያዬረ  በኢትዮጵያ ሥልጣኑን በጉልበት የተቆጣጠረው በተረኝነት ስሜት የተበከለው የጎሰኞች አምባገነናዊ ስብስብ (መንግሥት ብሎ ለመጥራት ይቀፈኛል ምክንያቱም የሕዝብን ይውንታ ያላገኘ ፣የመንግሥትነትን መስፈርት የማያሟላ በመሆኑ) ከመሰል አጋሮቹ ጋር አገራችንንና ሕዝቡን በጎሳ ከፋፍሎ እርስ በርስ እንዲተላለቅ፣ ከማይወጡት መከራና ችግር ውስጥ የከተተና በዓለም አቀፍ ደረጃ አገራችን ወዳጆቿ እያነሱ ፣ጠላቶቿ እዬበዙ፣አገር እንደ አገር እንዳትቆም የሚያደርግ  “ሕገመንግሥት” በሚል ሽፋን የጸደቀ የጥፋት ሰነድ መመሪያው አድርጎ ና ክልል የሚል የአስተዳደር አወቃቀር ዘርግቶ አሁን ለሚታዬው አደጋ አጋልጦናል።

 

 አደጋውን ቀድመው የተገነዘቡ ሰዎች ይጮሁበትና ይታገሉበት የነበረው ጉዳይ ውሎ አድሮ  የሕዝቡን ቀልብና ልብ እዬሳበ በመምጣቱ  ፍርሃት ያደረበት መንግሥት ነኝ ባይ ቡድን  የተለያዩ አፋኝ እርምጃዎችን በመውሰድ ማንነቱን ይፋ አድርጓል።እስከአሁን ድረስ በወሰዳቸው እርምጃዎች ያልተንበረከከውን ሕዝብ ለማንበርከክ ብዙ እቅዶችን አውጥቶ በመንቀሳቀስ ላይ ሲሆን ብዙ ዜጎች ሰለባ ሆነዋል።የዚያው ዘመቻ ቅጥያ የሆነው አንዱ በትናንትናው እለት በሚዲያ በኩል ያስተላለፈው በአገር ውስጥና በውጭ አገር በሚኖሩ ግለሰቦች ላይ ያቀረበው ክስና ውንጀላ ነው።ያንንም ተከትሎ በአገር አቀፍ በሚመስል መልኩ የአፈናና፣የማዋከብ እርምጃ ውስጥ ተሰማርቶ ብዙዎቹ የደረሱበት አልታወቀም።ይህ በተለያዩት የአፈናና የስለላ ብሎም በሚድያ የተቀነባበረ የውሸት ዘመቻ በአገር ውስጥ እዬተቀጣጠለ የመጣውን ሕዝባዊ ተቃውሞ ፣በተለይም በመንግሥት ተባባሪነት  በጨካኝ ጎሰኞች የጭፍጨፋ፣ ዘር የማጥፋት ፣የዘረፋና  የማፈናቀል ወንጀል ሰለባ የሆነው የአማራው ማህበረሰብ “በማንነቴና በእምነቴ መገደልና፣መፈናቀል በቃኝ! እምቢ አሻፈረኝ!” ብሎ በመነሳቱ፣ይህንን መንግሥት አገዝ የሆነ የሕዝብ ጭፍጨፋ በመቃወም   እንደ አማራው በእምነታቸውና በኢትዮጵያዊነት አመለካከታቸው የገዢው ጎሳ አባላት የሆኑትን ጨምሮ  በጠላትነት ፈርጆ ማጥቃቱን በመቃወማቸው ፣የሁሉም ከተማ የሆነችውን አዲስ አበባን ከታሪክ ባፈነገጠ መልኩ በነጠላ የጎሳ ይዞታ ስር ለመሰልቀጥ ታጥቀውና አልመው በተነሱት ጠባብ ጎሰኞች ላይ የከተማው ነዋሪ በተለይም ወጣቱ አሻፈረኝ በማለቱ ያንን ደግፈው በተነሱ በአገር ውስጥና ከአገር ውጭ በሚኖሩ አገር ወዳዶች ላይ የታወጀ የጥቃት ዘመቻ አዋጅ ነው።እያደገ የመጣውን ሕዝባዊ ተቃውሞ ለመቅጨት ታስቦ የተዘረጋ ወጥመድ መሆኑን መንገር ለቀባሪው ማርዳት ይሆናል።በሽብርማ ተከሳሹ የብዙሃኑን ደም በከንቱ የሚያፈሰው እራሱ መንግሥት ነው።

 

በአገር ክህደት ወይም በመንግሥት ግልበጣ ሴራ ላይ የተሰማሩ ብሎ ከከሰሳቸውና በኢንትርፖል በኩል ለሕግ አቀርባለሁ ብሎ የጅል ዛቻ ካቀረበባቸው ሰዎች መካከል አንዱ ነኝ።በመጀመሪያ የኢንተርፖልን ተግባርና ግዴታ የማያውቁ ጅሎች በኢትዮጵያ መንግሥት የሥልጣን  እርከን ላይ መቀመጣቸው እራሱን የቻለ አሳፋሪ ነው።በነዚህ ጅሎች መመራቱ ፣ተመሪውን ሕዝብ ሳይቀር ያስገምታል።ኢንተርፖል በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚሰራን ወንጀልና ሕገወጥ ተግባር የሚከታተል እንጂ በአንድ አገር የሚነሳን  የፖለቲካ ሕዝባዊ ተቃውሞን ለማፈን የተቋቋመ ድርጅት አይደለም። አባዱላ ገመዳ  የሚያዘው የቀበሌ ፖሊስ አይደለም። ስለኢንተርፖል ተቋም መረጃ ቢኖራቸው ኖሮ እንደዚህ ካለው ቅሌትና አስገማች ደረጃ ላይ ባልወደቁም ነበር።በጣም የሚያስገርመው ደግሞ በፊለፊትና በገሃድ የወጣን ፣በብዙሃን መገናኛ መስመር፣በጽሁፍና  በድምጽ የሚተላለፍን በአዲስ አበባና በሌሎቹ ከተሞች አደባባይ ላይ የወጡ  ሃሳብና ተቃውሞዎችን በሚስጢር  መንግሥትን ለመገልበጥ የተደረገ ሴራ ነው ብሎ ማቅረቡ የደህንነት ተብዬውን ተቋም ደረጃ ድክመት ይፋ ያደርገዋል።ይህንን ያልተሸሸገ ሕዝባዊ የአደባባይ ተቃውሞ ለማክሸፍ ያላሰለሰ ጥረትና ያለውን ሃይልና ጥበብ ተጠቅሜያለሁ ያለ  መንግሥት አቅሙ በዚህ ቀላልና ግልጽ በሆነ የሕዝብ ተቃውሞን ከማፈን ያላለፈ ከሆነ  ሌላ ውስብስብ የውጭ ጠላቶች የሚፈጥሩት ሴራና ችግር  በምን የተለዬ ጥበብ ሊከላከል እንደሚችል አጠያያቂ ነው።

 

ሌላው ትልቁ ነገር እኔ በኢትዮጵያ የፖለቲካ ትግል ውስጥ የገባሁት የአሁኖቹ አምባገነኖች ሳይወለዱ ነው።ከሁለተኛ ደረጃ የትምህርት ዕድሜዬ ጀምሮ በተማሪው እንቅስቃሴ፣ከዛም በዬካቲቱ ሕዝባዊ እንቅስቃሴ  የወታደሩ ክፍል አካል እንዲሆን፣ከካምፕ ጥያቄ ወጥቶ የሕዝቡን ጥያቄ እንዲያስተጋባ በማድረጉ ሂደት በወታደሩ ክፍል ግንባር ቀደም ሚና በተጫወተው በምድር ጦር አዬር ክፍል(Army Aviation)የተፈጠረውን አስተባባሪ ቡድን በግንባር ቀደም ከመሩት አንዱና የመጀመሪያው  ነኝ።ወታደራዊ ንቅናቄውንም በጸሃፊነት መርቻለሁ።በወታደር ክፍሎቹ መካከል በነበረው የመንግሥት የማከፋፈል ሥራ ክብርዘበኛና ፖሊስ በመንጝሥት በኩል አምስተኛ ክፍለጮር፣አራተኛ ክፍለ ጦርና አዬር ሃይል በሌላው በኩል ሆነው  ግጭት ሊፈጠር ሲል ንቅናቄውን በማቆም ለንጉሠነገሥቱ  በቤተመንግሥታቸው ቀርበው ጥያቄ ካቀረቡትና የጥያቄ ደብዳቤውንም የጻፍኩት እኔው ነኝ።ካቀረብናቸው ጥያቄዎችም መካከል ፣መሬት ላራሹ፣ትምህርት ለሁሉም፣ የዴሞክራሲ መብቶች ይከበሩ፣የፖለቲካ ፓርቲዎች ይመስረቱ፣ሕዝባዊ መንግሥት ይቋቋም…ወዘተ የሚሉ ነበሩ።ያቀረብነው ጥያቄ መልስ ሳያገኝ ይባስ ብሎም የንቅናቄው መሪዎችን ለማፈን ሴራ ሲጎነጎን ለተከታይ  ሁሉንም የጦር ክፍል ያጠቃለለ እንቅስቃሴ ለማድረግ ተደራጅተን ወደ ሥራ ለመግባት ስንወስን በውስጣችን    ሰርገው በገቡ መንግሥት የመደባቸው የአዬር ወለድ ክፍል አባላት ውጥኑ ሊኮላሽ ቻለ። በዚያም በልጅ እንዳልካቸው መንግሥት ከሊቢያ መንግሥት ግዳጅና ገንዘብ  የተቀበሉ፣ከሃምሳ ዓመት እድሜ በላይ ያለውን ሊፈጁ በሚል አስፈሪ ክስና ውንጀላ ተለቃቅመን እስር ቤት ገባን።የዚያ ንቅናቄ አባላት አሁንም ቁጥራችን ቢያንስም በህይወት አለን።ንቅናቄውንም በጸሃፊነት በመምራቴ በምርመራ ወቅት ከፍተኛ ትኩረት የነበረው እኔላይ ነበር።እስር ቤት በነበርንበት ጊዜ የተለያዩ መዝሙሮችን ያወጣን ሲሆን ተነሳ ተራመድ የተሰኘውም አንዱ ነው።በመዝሙሮቹ ውስጥ ከተካተቱት ግጥሞች መካከል

ተነሳ ተራመድ ክንድህን አበርታ፣

ላገር ብልጽግና ለወገን መከታ።

ስማኝ ያገሬ ሰው ባንድ ላይ ተነሳ፣

ድር ከተባበረ ይጥላል አንበሳ።

እስላም ወይ ክርስቲያን ሳይባል በሙሉ፣

የጎሳ ልዩነት ሳይኖር በመሃሉ፣

ያገርን ነቀርሳ መንግላችሁ ጣሉ።

አገር የበደለው አይልመድህ ሲባል

ላገሩ የሠራው እስር ቤት ይገባል።

የተገላቢጦሽ ሆነና ነገሩ፣

ተከሳሾች ነጻ ከሳሾች ታሰሩ።

ባስተዳደር ምክንያት እዬተማረረ፣

ስንቱ ኢትዮጵያዊ እንደወጣ ቀረ።

የሚሉ ስንኞች ይገኙባቸዋል።በዃላ ላይ ግን በደርግ ትእዛዝ በሙዚቃ ሲቀነባበር ግጥሞቹ ተከላልሰው ቀርበዋል።

 

  የጦር ሜዳ ፍርድ ሊበዬንብን ሲል በስከጀርባ ያሉ ጓደኞቼ ግርማ ፍስሐ፣ዩሃንስ ፍትዊ፣ብዙአዬሁ አምሳሉ፣ከሻለቃ አጥናፉ አባተና ከሻለቃ ተፈራ ተክለአብ ጋር ሆነው የጦር ሃይሎች የፖሊስ ሠራዊትና የብሔራዊ ጦር አስተባባሪ በዃላ ደርግ የተባለውን ኮሚቴ ፈጠሩ። እስር ቤት እያለሁ ለተቋቋመው አስተባባሪ ኮሚቴ ጸሃፊ እንደምሆን በዩሃንስ ፍትዊ በኩል ተነግሮኝ ነበር።ከሌሎቹ የእስርቤት ጓዶቼ ጋር ተነጋግረንበት ሕዝባዊ ኮሚቴ ካልሆነ ላለመቀላቀል ወስነን ጥያቄውን ሳልቀበለው ቀርቻለሁ።በያዝነው አቋም ከደርግ ጋር ግብግብ ገጥመናል።የደርግንም ወታደራዊ መንግሥት በመቃወም ሕዝባዊ መንግሥት በማለት በንዑስ ደርግ ስም የተቀሰቀሰውን ተቃውሞ በጸሃፊነት መርቻለሁ። በዚህም አቋም ከነመንግሥቱ ሃይለማርያም ጋር በጀነራል አማን አምዶም ቢሮ ውስጥ ሳይቀር ተጨቃጭቀናል። ልዩነቱ በመክረሩ ባላሰብንበት ቀንና ሰዓት የመሃንዲስና የእኛ ግቢ ተከቦ አባላቱ ታሰሩ።በህዳሩም ጭፍጨፋ የኮሚቴው አባላት የነበሩትን የአቪዬሽን አዛዥ ኮሎኔል ይገዙ ይመኑ፣ሻምበል በላይ ጸጋዬ፣በደርግ ውስጥ የነበሩትን ዩሃንስ ፍትዊንና መቶ አለቃ ተስፋዬን ታከለን፣ከመሃንዲስና ከክብር ዘበኛ ጦርም የንኡስ ደርግ አባላት የነበሩትን  ጨምሮ  ከቀድሞ ባለሥልጣናት ጋር በድምሩ ስልሳዎቹን ሲረሸኑ እኔ በቦታው ባለመኖሬና ባለመያዜ ልተርፍ ችያለሁ።ከእኔ ጋር ህይወቱ ተርፎ በዃላ ላይ በትግል ሜዳ ፣በአሲምባ ህይወቱ ያለፈው ጓደኛዬ ጌታቸው ሚደቅሳ ነው።እኔ ስልሳ አንደኛው፣ጌታቸውም ስልሳ ሁለተኛው ልንሆን እንችል እንደነበረም ጊዜ ካለፈ በዃላ ውሳኔ የወሰኑት ሰዎች በእስርቤት ላሉት ጓደኞቼ ገልጸውላቸው ሰምቻለሁ።

 

ብዙ ውጣውረዶችን፣ሞቶችንና፣በሚድያ የለፉ ውንጀላዎችንና ዛቻዎችን ያለፍኩ አገር ወዳድ ነኝ። ከአርባ ስድስት ዓመት በፊትም ያመለጥኩት ደርግ የተባለው የወታደር አምባገነን  የፍዬል ወጠጤ በሚል ፉከራ የታጀበ  ወጣቱን በማደራጀት በጦር ሜዳ የሚያሰማሩ በማለት ክስና ውንጀላ ካቀረበባቸው አራት ሰዎች መካከል አንዱ ነበርኩ፣በዛም ጊዜ ቢሆን በቅርብ እርቀት ላይ ሆኜም የማምንበትን ከማከናወን አላገደኝም።ሕይወቴንም ለመስጠት የልጅነት ዕድሜዬም ሆነ ከፊቴ የተደቀነው  ኑሮና እድገት ወይም ደረጃ አላጓጓኝም ነበር። ለኢትዮጵያ አገሬ እድገትና ሰላም እንዲሁም አንድነት፣ለሕዝብ ክብርና መብት በማምንበት መንገድና አጋጣሚ ድምጼን ሳሰማ ኖሬአለሁ፤አሁንም ወደፊትም አሰማለሁ።እምነቴና ከተሰዉት ጓዶቼ ጋር የገባሁት ቃል ኪዳን ያስገድደኛል።ለአገራዊና ሕዝባዊ ተኮር ጉዳይ እንጂ ለጎሳ ተኮር ዓላማ የማልሰለፍ ሰው ነኝ፣ይህ ማለት ግን ሰው በጎሳውና በእምነቱ  ሲበደል ዝም እላለሁ ማለት አይደለም።ከተበደሉት ጋር እቆማለሁ።ኢትዮጵያ ዳር ድንበሯ ተከብሮ፣አንድነቷ ተጠብቆ፣ሕዝቡም ከአምባገነን ሃይሎች መዳፍ ወጥቶ፣እንደሰውና ዜጋ ተከብሮ በመረጣቸውና በዴሞክራሲ ስርዓት እስኪመራ ድረስ ከትግል ሜዳ አላፈገፍግም፤ድምጼን ከማሰማት አልቆጠብም።ከቶ ፍርሃት የሚሉ ድክመት በውስጤ የለም።የማምንበትን በግልጽና በድፍረት የምገልጽ፣መሸፋፈን የማልወድ ሰው መሆኔን የሚያውቁኝ ሁሉ ይመሰክራሉ።ሥልጣንና  ገንዘብ ወዳድነት የሚሉት መርዛማና ደካማ ስብእናም የለብኝም።ጊዜና ሁኔታ በፈቀደልኝ የትግል መድረክ ለረጅም ጊዜ ሃሳቤን በጽሁፍ ሳሰራጭ ኖሬአለሁ።በልዩ ልዩ እርዕሶችናትዝብትበሚል አምድ በአካል ያዬሁትንና የሰማሁትን የአገር ጉዳይ እያነሳሁ  በጽሁፍ እስከአሁን ድረስ ፣ለሕዝብ ሳሳውቅና ስቀሰቅስ ኖሬአለሁ።

 

ለሰላሳ ዓመታት የሠራሁበትን፣ብዙ ገንዘብ የማገኝበትን ሥራ ለቅቄ በቅድመ ጡረታ በማገኘው ገንዘብ እዬኖርኩ ቀሪ ዕድሜዬን ለወጣሁበት ዓላማ ለማዋል ስል ወስኜ መኖር ከጀመርኩ ከአሥራ አንድ ዓመት በላይ ሆኖኛል። እግዚአብሔር ይመስገን በኑሮ የጎደለብኝ ነገር የለም።ከቤተሰቤ አልፎ ለሌላውም እተርፋለሁ።ከሁሉም በላይ ጤነኛ ነኝ።

 

ከአስር ዓመታት በፊት የኢትዮጵያ ሕዝብ የጋራ ትግል ሸንጎ( ሸንጎ) የተባለውን ለዴሞክራሲ ስርዓት መስፈን የተቋቋመ የጋራ ግንባር ስብስብ ከምስረታው ጀምሮ ተቀላቅዬ የማምንበትን አበርክቻለሁ።ከአራት ዓመት በፊትም የክልልን አወቃቀርና የጎሳ ፖለቲካን ተቃውሞ የተመሰረተውን  የኢትዮጵያ ክፍላተሃገር ህብረት የተባለውን ድርጅት በጸሃፊነት የበኩሌን አበርክቻለሁ፤ወክዬም ከሁለት ዓመት በፊት አዲስ አበባ በመሄድ የአንድነት ሃይል የተባሉትን በአገር አቀፍ ደረጃ የሚንቀሳቀሱትን አስራ ስምንት የፖለቲካ ድርጅቶች  በመሰብሰብ የጋራ ግንባር ፈጥረው አገር አድን ትግል እንዲያካሂዱ ጥረት አድርጌ ኮሚቴም አቋቁሜ  ብሔራዊ የትብብር መድረክ(National Solidarity Forum) በሚል ስም እንቅስቃሴው የብዙሃን ድርጅቶችንም እንዲያቅፍ መሰረት ጥዬ ተመልሻለሁ።በአገር ቤት የፖለቲካና የብዙሃን ወይም የሙያ ድርጅቶች በአንድ ላይ ሊታገሉ የሚችሉበት ሕግ ስለማይፈቅድ በውጭ አገር ዓለም አቀፍ የኢትዮጵያውያን የትብብር መድረክ(International Ethiopians Solidarity Forum) የሚል ሕጋዊ ድርጅት ከክፍላተ ሃገሩ አባላት ጋር መሥርተን በመንቀሳቀስ ላይ ነን። ጥረቱ በአገር ቤት ባሉት ድርጅቶቹ ድክመት እንደታሰበው ሊንቀሳቀስ አልቻለም።በአገር ቤቱ የድርጅቶቹ ስብሰባ መርጦ ከመደባቸው የኮሚቴ አባላት ሆኖ በቋሚነት የቆዬውና የዓለም አቀፉ መድረክ ውክልናም የተሰጠው  አሁን በተላለፈው የመንግሥት ውንጀላ የተካተተው አቶ ሳሳሁልህ ከበደ ነው።እሱ የሚመራው የፖለቲካ ድርጅትና መድረኩ በሚከተለው የጠራ አቋም ፣በአዲስ ሕገመንግሥት አስፈላጊነት፣በክልል መፍረስና በክፍላተ ሃገር አወቃቀር  መተካት በሚለው አቋሙ የተነሳ የምርጫ ቦርዱ ምክንያት ፈጥሮየሚመራውን የፖለቲካ ድርጅት አግዶት በየፍርድ ቤቱ ሲንከራተት ቆይቷል።መጨረሻው ላይም የምዝገባው ጊዜ አልፏል ተብሎ ከምርጫው ተወግዷል።

 

አገር ቤት በነበርኩበት ወቅት በምርጫ ቦርዱ ስብሰባ ላይ ህብረቱን በመወከል  በመሳተፍ ሕገመንግሥቱን ተቃውሜ ፣አንቀጽ 39 የመሰለ አገር አፍራሽ፣ ሕዝብ አጫራሽ የሆነ፣ሕዝብ ያልተካፈለበትና ያልፈቀደው ለምርጫ ቦርዱ የምርጫ  ሕገ ደንብና ቃል ኪዳን  የመሃላ ማሰሪያ መሆን የለበትም ብዬ የተናገርኩት ብቸኛው ሰው እኔ ነበርኩ።ሃሳቤንም በጽሁፍ እንዳቀርብ ወ/ሪት ብርቱካን ሚደቅሳ ጠይቃኝ ሰጥቻለሁ።ምናልባት የማስታወስ ችግር ከሌለባቸው በቦታ የነበሩት ከመቶ ያላነሱ ሰዎች ምንም እንኳን ጭጭ እርጭ ቢሉም፣እኔ ደፍሬ ላቀረብኩት ፣ላብ ቢያሰምጣቸውም፣ቢሸማቀቁም ምስክሮች ናቸው።

 

ከዚያም በዃላ በተለያዩ  በድምጽና በምስል በሚተላለፉ መድረኮች ላይ በመሳተፍ ሃሳቤን አካፍያለሁ፤ወደፊትም አካፍላለሁ።በግፍ ለሚጨፈጨፉት ወገኖቼ ቀርቶ ማንኛውም የሰው ልጅ  በየትም ቦታ ቢሆን በግፍ ሲጨፈጨፍና ሲጠቃ ዝም የምልበት ጨካኝ አንጀት የለኝም።የተወለድኩበትና ያደኩበት፣በሰውነትና በኢትዮያዊነት ቀርጾ ያሳደገኝ ማህበረሰብ፣ቤተሰብና  የኖርኩበትም አካባቢና ስርዓት የሰጠኝ ስብእና ፣በትምህርት ቤት የተኮተኮትኩበት ግብረገብና አገር ወዳድነት አይፈቅድልኝም። ለሰው ልጆች መብትና ለጋራ ጥቅም፣ለኢትዮጵያ አንድነትና ሰላም እንዲሁም ክብር፣ጎሰኝነትንና ዘረፋን ከሚጠሉና ከሚጠየፉ ብሎም ለማሶገድ ከሚቆሙት ጋር አብሬ እቆማለሁ። ጎሰኝነት፣ዘረኝነት እንኳንስ የቆመን የሞተንም  በድን አካል የሚያሶግዝና የሚበክል ወራዳ ማንነት መሆኑን አምናለሁ።ሰልፌ ከቀናና በጎ አሳቢዎች ጋር ነው።በዚህ የክስ መግለጫ ውስጥ የተካተቱት የማውቃቸው ሰዎች በትምህርትም ሆነ በኑሮ ደረጃ ይህ ቀራቸው የሚባሉ አይደሉም።የስነምግባርና የእውቀት ብሎም ያገር ፍቅር ባለቤቶች ናቸው።የዕድሜም ባለጸጎችና የተመክሮ ጌቶች ናቸው።ለወጣቱ ትውልድ እንጂ ለራሳቸው ኑሮ አይጨነቁም።በሰለጠነና በአደገ አገር እዬኖሩ እንቅልፍ የሚነሳቸው የተወለዱባት አገር ኢትዮጵያና በመሪዎች ያልታደለው ሕዝብ ጉዳይ ነው።ምኞታቸው ሁሉ የትውልድ አገራቸው ኢትዮጵያ ከሚኖሩበት አገር እኩል ከተቻለም በልጣ ማዬት ነው።ሌላው ቢቀር ወገናቸው በሰውነትና በዜግነቱ ተከብሮ የሚኖርባት አገር ማዬት ነው።

 

በዚህ የአምባ ገነኖቹ  የውንጀላ ክስ ላይ ከተጠቀሱት መካከል አብዛኛዎቹ የማያውቁኝና  የማላውቃቸው ናቸው።እኔ በቆምኩለት ዓላማ ከሆነ ግን ዓላማው አስተሳስሮናል።እንኳንስ ጸረ አምባገነኖች ሆኑ፤ሌብነትና ዘረፋን፣ ጎሰኝነትንና የዘር ማጥፋት ጭፍጨፋን ሲቃወሙ መከሰስ እራሱ ክብር ነው።ወንጀለኛ ማለት ከአምባገነኖች ጎን መሰለፍና የነሱ አሽቃባጭ (ውታፍ ነቃይ) መሆን ነው። መግለጫው የአገዛዙን መረበሽና ተስፋ መቁረጥ ያሳያል።አምባገነኖች መውደቂቸው  ሲቃረብ እብድ ውሻ ይሆናሉ።ጥላቸውንም አያምኑም።ኮሽ ሲል ይበረግጋሉ።የማይወነጅሉት አይኖርም።አሁንም በአዲስ አበባና በሌላውም ያገራችን ክፍል አፈናና ወከባው በሰፊው ቀጥሏል።ለትግሉ የሚከፈለው ዋጋና መስዋዕትነት ገና ብዙ ይጠብቅብናል።ጎሰኛው ቡድን ባመጣው ጣጣና የውስጥ አለመረጋጋት ምክንያት የውጭ ጠላቶቻችን ቋምጠው ተነስተዋል።ባንዳዎችን አስታጥቀው በአገራቸው ላይ እንዲዘምቱ አድርገዋል። የሚጎነጉኑትን ሴራ ሳንዘነጋ ፣እኩል በጣምራ ጠላቶቻችን ላይ የምናደርገውን ትግል መቀጠል እንዳለብን አምናለሁ። ኢትዮጵያዊነትን  ይዘን ከተነሳን የውስጡንም የውጩንም ጠላት ለማንበርከክ የሚሳነን አይሆንም።በአንዱ ላይ ብቻ በማነጣጠር ሌላውን ቸል ማለት አይኖርብንም።ጠላት ጠላት ነው።የሕዝቡን ሕጋዊና ተገቢ ተቃውሞና አገር ወዳድ እንቅስቃሴ ከውጭ ጠላቶች ጋር ማስተሳሰር የአምባገነኖቹ ስልት መሆኑን መረዳት ተገቢ ነው።

 

ሌላው በሕገመንግሥቱ ዙሪያ የተነሳው ውንጀላ በብዙሃኑና በተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅቶች በኩል ከሚነሳው ጥያቄ የተለዬ አይደለም።ብዙሃኑ አሁን በሥራ ላይ የዋለው  “ሕገመንግሥት”  መወገድ አለበት  ብሎ ያምናል፤እኔም ጭምር።በምን ይተካ ለሚለው ጥያቄ መልስ መስጠት ተገቢ በመሆኑ ፕሮፌሰር አበራ መሸሻ  በእንግሊዝኛ ያዘጋጁትን ፣አገር ቤት ልከው በሕጋዊ ተርጓሚ ተተርጉሞ፣ለፖለቲካ  ና ለብዙሃን ድርጅቶች፣ለሕግ ባለሙያዎች፣ምሁራንና ተቋማት ተዳርሶ ሃሳብ እንዲሰጡበትና ጎልብቶ አማራጭ ወይም ማሟያ እንዲሆን በይፋ የቀረበ የቀና ሰው አበርክቶ ነው።የመንግሥት አካላትም የሚያውቁት ጉዳይ ነው።ይህንንም የሕግ እረቂቅ ለማስተርጎም አላፊነቱ ለትብብር መድረኩ ተወካይ ለአቶ ሳሳሁልህ ከበደ ተሰጥቶት ሥራውን አከናውኗል ።ይህ የአገር ወዳድ ተግባር  እንደ ወንጀል ተቆጥሮ ለክስ ማስረጃነት ቀርቧል።ከዚህ የበለጠ እብደት ከዬት ይመጣል?ሃሳብን በሃሳብ መሞገት ወይስ ሃሳብ አቅራቢውን ለማጥፋት ጦርነት ማወጅ?  ላም ባልዋለበት ኩበት ለቀማ ከንቱ ድካም ማለት እንዲህ ነው።ይህን አይነቱን ከንቱና ውሸታም አምባገነን ጎሰኛ መንግሥት ይዞ ወዴት ጉዞ? ኢትዮጵያን ለማዳን፣የኢትዮጵያውያንን አንድነት፣ክብርና ዝና እንዲሁም የሚያኮራ ታሪክ፣ ለመመለስ  ኢትዮጵያዊ  የሆነ፣በጎሳ ህሳቤ ያልተጨማለቀ መንግሥት ማቋቋም የግድ ይላል።ለዚያም መዳረሻ የሚሆን የሽግግር መንግሥት አማራጭ  የሌለው ምርጫ ነው። 

 

በአገራችን ላይ የሚካሄደውን የጎሰኞች ሴራና የዘር ማጥፋት ወንጀል እንዲሁም መንግሥታዊ ተሳትፎና አፈና ለምኖርበት አገር የመንግሥት ተቋማትና የተለያዩ የፖለቲካ ድርጅቶች ፣ለሰብአዊ መብት ተሟጋቾች በስፋት እያስረዳሁ ሲሆን ሌሎቹም ኢትዮጵያውያን ወገኖቼ በያሉበት ሁሉ በተመሳሳይ  ድምጻቸውን እንዲያሰሙ ጥሪ አቀርባለሁ፤የጀመሩትንም በርቱ እላለሁ።

 

 በድንፋታ አንሸማቀቅም!እውነት ተደብቆ አይቀርም ጊዜውን ጠብቆ ይወጣል!!

አንድነትና ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!

ከዚህ ጋር የትብብሩን ዓላማና በአገር ቤት የፖለቲካ ድርጅቶች ስብሰባ ላይ የቀረበውን ጥሪና ውሳኔ ሰነድ ለግንዛቤ አባሪ አድርጌ ልኬዋለሁ።እውነቱን ከስር መሰረቱ ለማወቅ በትእግስት እንድትመረምሩት በአክብሮት እጠይቃለሁ።

አገሬ አዲስ