Saturday, July 22, 2023

ከእያንዳንዱ ውሸት በስተጀርባ ለማታለል መነሳሳትን የሚገፋፋ ታላቅ የጣዖት አምልኮ ትግራይ ውስጥ አለ። ከጌታቸው ረዳ Ethiopian Semay 7/21/23


ከእያንዳንዱ ውሸት በስተጀርባ ለማታለል መነሳሳትን የሚገፋፋ ታላቅ የጣዖት አምልኮ ትግራይ ውስጥ አለ።

ከጌታቸው ረዳ

Ethiopian Semay

7/21/23

 የሠረቀ ብርሃን እና የቴድሮስ ጸጋየ (ርዕዮት ሚዲያ) ትወና !

ትናንት “ርዕዮት ሚዲያ” አባ ሠረቀ ብርሃን በሚል ስም የሚጠራው “ወያነ” የተባለን “ጣዖት” አምላኪ ስለ አማራ ማሕበረሰብ የተነጋረውን ለማስረዳት ተጋብዞ ብዙዎቻችሁ ያደመጠችሁት ይመስለኛል።

የሰውየው አታላይነት ሳይሆን የገረመኝ ቃለ መጠይቅ ያደረገለት አዲሱ የወያኔ ቱልቱላው “ቴድሮስ ጸጋየ” ሰውየውን ላላማጋፈጥ የሄደበትን የተለመደው ወያኔያዊ ባሕሪው ለሁለተኛ ጊዜ ታዝቤአለሁ።

ሁለት ጊዜ ስል አንደኛው አሉላ ሰለሞን የተባለው “የትግሬው ካቡጋ” እና ሁለተኛው “ሰረቀብርሃን” የተባለው “የማሌሊት ቄስ” ጋር ባደረገው ወገንተኛ የጥያቄ አቀራረብ ስልት ስትመለክቱ እጅግ የሚገርም የቴድሮስ ጸጋዬ ገናና ምጥቀትና አወዳደደቅ፤ የአብይ አሕመድ ገናና ምጥቀትና ቁልቁል አወዳደቅ ተመሳሳይነታቸው አንድ ሆኖ አግኝቼዋለሁ።

ሦሰቱ ሲዋሹ/ሲደብቁ/ሲጠመዝዙ/ሲያሰመስሉ ታዝበናቸዋል። ሦስቱ ትግሬዎች ናቸው። ስለ ኢትዮጵያ ያላቸው እይታ በአተላ ደረጃ የሚመዘን ነው። ኢትዮጵያን እንኳን መውደድ ቀርቶ ሠረቀ ብርሃን እንዳለው ፡ትግሬዎች ኢትዮጵያ የሚባል ቃል ከአንደበታችን እንዳይደመጥ፤ “ኢትዮጵያ” የሚል ቃል ካንደበቱ የሚደመጥ ትግሬ ካለ እሱ የተረገመ ነው” ሲል በማሌሊታዊ አንደበቱ ረግሞናል። ይህ “ወያኔዊ ቄስ “የርዕዮተ ዓለም አስተማሪዎቹ ወያኔዎች” ወያኔ ያልተከተለ ሁሉ “የሽዋ አማራ” እንጂ “ትግሬ” አይደለም እያሉ ሲያስተምሩት የነበረውን ማንነታችንን የመግፈፍ ወንጀል ሠርቀ ብርሃንም የደገመው ያንን ነው።

ቴድሮስ ፀጋየም ሰለሞን አሉላ (የወያነ ትግራይ ካቡጋ) እና ሰረቀብርሃንን ሲጠይቃቸው “የአማራ መንጋ” (መንጋው) የሚላቸውን አማሮችና “ሚሊሺያው ጳጳስ” እያለ የሚጠራቸው በነገዳቸው አማራ የሆኑ ጳጳሳትን እና ቀሳውስት ለማጋለጥ የተጠቀመባቸው “ቃለመጠይቆች ፤ የቪዲዮ  ሰነዶችና ጽሑፎች” ያሰባሰባቸው ማስረጃዎች እጅግ በጥናትና በድካም የተጠናቀሩ ጥልቅ  እና መጓች የአቀራራብ ስልቶቹ ስናወዳድር እነ  ጸረ አማራዎቹ እነ ሠረቀ ብርሃን እና እነ “ሰለሞን ካቡጋ” ጋር ሲደርስ ግን ጭራሽ “የሚሞግትባቸው የቪደዮ እና የቃል ሰነዶች ፈልጎ እንዳጣ እና ለጊዜው ፈልጎ አፈላልጎ በሚዲያ ሲሰራጩ ያገኘው አንድ ንግግር ብቻ እንደሆነ እና ያም በጣም መናኛ እና ለትርጉም እንደፈለገ ለመጠምዘዝ የሚያመቹ ተጠያቂዎቹ በቀላሉ ሊመልስዋቸው የሚችሉትን በማቅረብ መርጦ ‘በትንሽዋ ሴልፎኑ’ እንዴት እንዳስደመጠን ፕሮግራሙን ያደመጣችሁ ትዝብት ወስዳችኋል ብየ እገምታለሁ።

እነዚህ ሰዎች የተናገሩትን አጥብቆ ከመያዝ እና ለሚገጥማቸው ተቃውሞ ከመጋፈጥ ይልቅ የተናገሩትን ቃል ለምን በአሉታና በማጣመም ለመሸሽ ይመርጣሉ? የሚገፋፋቸው ነገር አለ። እርሱም ውሸትን የሚገፋፋ ባሕሪ ለራስ  ወይንም ለነገዱ *በሠረቀ ብርሃን ቃል ዘር) ያለው ፍቅር ነው። በተለይ እንደ ረቀ ብርሃን የመሳሰሉ “አገርኛ እና የእንግሊዝኛ ቋንቋ” እየደባለቁ ሃሳባቸውን ለሰፊው ሕዝብ ለማስረዳት የሚጥሩ “ማርክሳዊያን ቀሳውስት”  የሚዋሹበት ምክንያት” በክርስቶስ ያላቸውን አቋም በምትኩ ራሳቸውን ለመታበይ ወይም ኃጢአታቸውን ለመሸፋፈን ሲመርጡ የሚንጸባርቁት ባህሪ ነው።

የውሸትን ክብደት የሚመዝኑ ታዛቢዎች መለኪያ ሰዎቹ ከሚዘላብዱት ተለዋዋጭ አንደበት ነው።አንድ ቄስ በውሸት ከተያዘ፣ መዘዙ ቢያንስ በራሱ እና በሚጠብቀው ምዕመን መካከል ያለው መተማመን መሸርሸር ነው። 

በዛሬ አጠራር “ትግራይ” የሚባለው አካባቢ ምናልባትም ከ400 አመት በኋላ  (የአክሱም ነገሥታት ከመንበራቸው ተሸንፈው ከተባረሩ  በኋላ) በ12ኛው ክፍለዘመን የተነሳው አምሐራዊው ይኩኖ ኣምላክና የይኩኖ ኣምላክ ልጆችና የልጅ ልጆች …. ትግራይ ውስጥ ለ400 አመት ላሽቆ/ጠፍቶ/ተዳፍኖ የነበረው የኦርቶዶክስ ሃይማኖት እምነት በተጠቀሱት የአማራ ነገዶች ሕይወት ዘርቶ አብቦ እስከ ቀዳማዊ ሃይለስላሴ ዘመን ድረስ ተጠብቆ እንደነበር ታሪክ የማይፍቀው እውነታ ሰነድ አለ።

 ቀዳማዊ ሃይለስላሴ ከተወገዱ ወዲህ በተለይ ደግሞ ትግራይ ውስጥ ከ1968/1969 እስከ ዛሬ 2015 ዓ.ም ድረስ የተዋህዶ ወይንም እስልምና ሃይማኖት ትግራይ ውስጥ ከምንጊዜውም ዝቅተኛ ደረጃ የደረሰበት “ሃይማኖትና ፖለቲካ” ተዋህደው ፖለቲካው ሃይማኖትን የሚመራው” ሆኖ እያየን ነው። ትግራይ ውስጥ የፈጣሪ የአገልግሎት ማዕረግ በተሸከሙ ሰዎች ቃል የመታመን ዘመን አልፏል።

ኢትዮጵያ ውስጥ በተለይ ትግራይ እና ኦሮሚያ ውስጥ አብያተ ክርስቲያናት በሚዋሹ ቀሳውስት እየተመሩ ናቸው። በመዋሸት በሕዝብ ፊት በክርስቶስ ስም ላይ ጥፋት እንዲደርስ አድርጓል? ይህ በውሸት ምእመናንን እና የዜና ማሰራጫዎችን የማታለል ዘዴ የፖለቲካው ተልዕኮ አካል ነው እንዲህ ያሉት ውሸቶች በተቋማት፤ በአገር አንድነት ላይ ከባድ መዘዝ ያስከትላሉ (አስከትለዋልም)። ምዕመኑ “ነገዳውያን ቀሳውስትን” በመከተል የራሱን ሃይማኖቱን በማርከስ ላይ እንደሆነ እያየን ነው፤፡

ቴድሮስ ጸጋየ ሆን ብሎ የደበቃቸው የሠረቀ ብርሃን ሂትለራዊ ንግግሮችን እንመልከት፦

አባ ሠረቀ ብርሃን እንዲህ ይላልለ፦

<< (አማራ የጠራ ዘር) ስሌለው ከዚያም ከዚያም ተጠራቅሞ የመጣ ዘር ስለሆነ አማራ የሚባል ዘር የለም ! ቢኖርማ ያስብ ነበር። ስለዚህም ነው ፤’የአማራ ሕዝብ ኢትዮጵያ፤ ኢትዮጵያ’ የሚለው። የራሱ የሚባል ዘር የለውም። ከዚህ መጣ ስለማይባል፤ ከትግራይ ከዚያም ከዚያም የተወጣጣ (ስለሆነ) ራሱን ችሎ የመጣ ዘር ስሌለው ‘ሁልጌዜ ሊሸፈን የሚፈልገው ኢትዮጵያ በምትባለው (አገር) ነው’። ለዚህ ነው ሌላ ነገር አይናገርም። ኢትዮጵያዊ ነኝ ብቻ የሚለው።…….

………ኦረሞም ኦሮሞኖቱን ይዞ ኢትዮጵያዊ ነው፤ ትግራይም ትግራዋይነቱን ይዞ ኢትዮጵያዊነቱን ይዞ ነው የመጣ፡አማራ ግን አማራነቱን ይዞ ኢትዮጵያዊነት የሚለው ስሌለው፤አማራ የሚባል ዘር ስሌለው፤ ’የሚንጠለጠልበት ዘር ስሌለው’ ኢትዮጵያ በሚለው ተሸፍኖ እየሰራ ስለመጣ “Shame on you! በጣም አፍርባችለሁ።

………..የትግራይ ሕዝብ ሆይ! በትግራይ እየተካሄደ ያለው ጀነሳይድ እነዚህ አካላት ክደውሃል፡ አማራ ክዶሃል! እመነኝ! እመነኝ! አስረግጬ እነግርሃለሁ። ኢትዮጵያ የምትባል ብትከድህም እግዚአብሔር አልካደህም!”

ሲል ማሌሊታዊው ቄስ ሰረቀ በርሃን አማራ “ዘረ ቢስ” ነው። የጸዳ ዘር ሳይሆን ከዚያም ከዚያም የተጠራቀመ ያደፈ የቆሸሸ ደም “የበታች ዘር (ሎው ካስት)” ነው፤ ሲል በግሃድ ሳይደብቅ በዜና ማሰራጭያ “በትግናዚያዊ አዋጅ”  ሳይሸማቀቅ አስረግጦ (ሃይላይቱን አድምቆ) ነግሮናል።

ናዚዎች ዓለምን የሚገልጽዋት ልክ እንደ “አባ ሠረቀ ብርሃን” በቆሸሸ ዘር እና ወጥ በሆነ የጸዳ ዘር መካከል በሚደረግ ትግል እንደሆነ ያምኑ ነበር። የናዚ ዘረኝነት ስለ ዘር እና ስነፍጥረት ልዩነት በየትምህርት ቤቶችና ተቋማት ያንሸራሽሩና በአዋጅ ያስነግሩ ነበር። የተቀላቀሉ ዘሮችና አካለ ስንኩላን የማይፈለጉ ፍጡራን ስለሆኑ መወገዝና መጥፋት አንዳለባቸው አውጀዋል።

ስለሆነም ዘርን እንደመታገያ ወስደው የጀርመን ምሁራን እና ሃይማኖት መሪዎች ሁሉንም የዕለት ተዕለት ኑሮ እና ፖለቲካ በዘር ጥራትና በወጥነት እምነት ተቀርጸው ይሁዶችን የተለየ እና የበታች ዘር ናቸው የሚለውን አስተሳሰብ ተራውን የጀርመን ሕዝብ እንዲከተለው በማድረግ ጸረ ይሁዳነት እንዲሰፍን አድርገዋል።

ሠረቀ ብርሃን እና መሰሎቹ አማራ ወጥ ዘር ስሌለው ከየት እንደመጣ የማይታወቅ ሕዝብ ነው፤ ስለሆነም የኔ ዘር ነው የሚልበት ዘር ስሌላው የበታች ዘር (ሎው ካስት) ስለሆነ ሁሌም “አትዮጵያ በምትባለዋ አገር ተጠልሎ የሚኖር ሕዝብ ነው።” ብሏል።

“አባ ሠረቀ ብርሃን” እየነገረን ያለውን በንጽጽር ስንመለከት “ናዚዎች ይሁዶችን” ዘርቢስ የሆኑ በዓለም ውስጥ ተበታትኖ የሚኖር የራሱ “ወጥ (ኢንዲፐንዳንት) የሆነ ዘርና አገር የሌለው “ዝቅተኛ ዘር” የሆነ ጀርመን ነኝ እያለ “የጀርመን ዘር የሚበክል” ጀርመንን እንደ መከለያው አድርጎ የሚኖር ጥገኛ ዘር (ዝቅተኛ ዘር) ነው የሚሉ የናዚዎች አዋጅ  በመቅዳት ነው ‘ቄስ ሠረቀ ብርሃን’ አማራውን “ሎው ካስት” ነው ሲል ያወጀ።

 ይህንን ደፍሮ የሚከራከረኝ አማራ የለም፤ካለም ይቅረብ የሚል እምነት ስላለው (በድፍርትም ተናግሯል) በሚገርም ሁኔታም የርዕዮት ሚዲያ ቴድሮሰ ጸጋዬ “ይቅርታ መጠየቅ ካለበዎት የሚሉበት ነገር ካለ ዕድሉን እነሆ፡ በማለት አባ ሠረቀ ብርሃንን ጋብዞ ያለ ምንም “ከባድ ጥያቄና ሊቀርቡ የሚገባቸው ሰረቀ ብርሃን የተናገራቸው የቪዲዮ ሰነዶች ሆን ብሎ የሆነች ትንሽ መናኛ የንግግሩ ክፍል በሴለፎኑ ለአድማጮቹ  በማስሰማት እራሱንም አስገምቶ ሠረቀ ብርሃንን እንደልቡ እንዲጋልብ አድርጓል” 

 የሃይማኖት መጽሃፉ የሚነግረን “የጽድቅ ሰባኪ የሆነ ሁሉ በኃጢአተኞች መንገድ ሲቆም፣ ንስሐው እንደ ኃጢአቱ እስኪታወቅ ድረስ በታላቁ ጉባኤ ውስጥ እንደገና ከንፈሩን መክፈት የለበትምይላል። ይህ ውሸተኛ ቄስ  ውሸቱን በማስረዳት ወይም በማመካኘት ኃጢአቱን ያዋህዳል ወይንስ በትህትና እና በጽድቅ ንስሃ ለመግባት ድፍረት በማግኘቱ ሃላፊነቱን ይወስዳል?

ለድፍረቱ ይቅርታም ሆነ ንስሃ መግባት ቀርቶ “አሁንም ያልኩትን በድፍረት እደግመዋለሁ፡ የሚከራከረኝ ካለ ይምጣ” ሲል ዘረኛ ድንቁርናውን ድፍረቱ ታብዮበታል። ከእያንዳንዱ ውሸት በስተጀርባ ለማታለል መነሳሳትን የሚገፋፋ ታላቅ የጣዖት አምልኮ ትግራይ ውስጥ አለ የምለው ለዚህ ነው።

ጌታቸው ረዳ