Thursday, September 19, 2019

ኢሬቻ የኦሮሞ ብሔርተኞች «መንግሥት» እና ሃይማኖት አንድ መሆናቸው ማሳያ! (አቻምየለህ ታምሩ) Posted on Ethio Semay (Important document –a must read!)



ኢሬቻ የኦሮሞ ብሔርተኞች «መንግሥት» እና ሃይማኖት አንድ መሆናቸው ማሳያ! (አቻምየለህ ታምሩ)

Posted on Ethio Semay (Important document –a must read!)

የኦሮሞ ብሔርተኞች በዐፄዎቹ ዘመን ነበር የሚሉትን  የመንግሥትና ሃይማኖት አንድነት ለማስቀረትና መንግሥትና ሃይማኖት የተለያዩበት አገር እንዲፈጠር ጫካ ወረድን ቢሉንም ስልጣን ሲይዙ  ግን መንግሥትና ሃይማኖትን አንድ አድርገው ሃይማኖታዊ በዓል ለማክበር ሽር ብትን እያሉ ናቸው! ሃይማኖት  የሰው ልጅ ከፈጣሪው ጋር  ግንኙነት የሚያደርግበት ሥርዓት ነው። ክርስትና፣ እስልምና፣ ዋቄፈታ፣ ወዘተ አማኞች እንደየቤተ እምነታቸው አማኞቹ ከፈጣሬያቸው ጋር ግንኙነት የሚያደርጉባቸው የአገራችን ሃይማኖታዊ ስርዓቶች ናቸው። ኢሬቻ የዋቄፈታ እምነት ተከታዮች ከፈጣሪያቸው ጋር የሚገናኙበት ሃይማኖታዊ በዓል ነው። እሬቻ  ሃይማኖታዊ  በዓል እንደመሆኑ መጠውን እውነተኛ  የክርስትናና  የእስልምና እምነት ተከታዮች እንዲሁም ሃይማኖት የሌላቸው ኢትዮጵያውያን የሚያከብሩት በዓል አይደለም። አንዳንዱ ኢሬቻን  ሃይማኖታዊ በዓል ሳይሆን  ባሕል ሊያደርገው ይፈልጋል። ሆኖም ግን  ይህ ፈጽሞ ስህተት ነው።

ሊቁ ሎሬት ጸጋዬ ገብረ መድኅን  ከጦብያ መጽሔት ጋር በ1990 ዓ.ም. ባደረገው ቃለ ምልልስ ስለ ኢሬቻ ሃይማኖታዊ በዓልነት የሚከተለውን ተናግሯል፤ «በኦሮሞ ዘንድ በገዳ ትዛዛት እየተመሩ የሁሉን ፈጣሪ አንድ አምላክ ዋቃን ማምለክ ዋቄፈና ይባላል። ዋቄፈና  ይማኖት ነው። እሬቻ ደግሞ የዋቄፈና እምነት  አካል ነው። ምዕመኑ  ተሰብስቦ ለምለም ቄጠማ፤ አረንጓዴ ቅጠል፤ አበባ…ይዞ ፤ዋቃን በወንዝ ወይም በሐይቅ ዳርቻ ወይም በተራራ ላይ የማመስገን፤ የማክበር ፤የማምለክ በአል ነው – ኢሬቻ፤ የፀሎት ቀን ነው እሬቻ። ኢሬቻ ብዙ አይነት ቢሆንም ዋናዎቹ ሁለት ናቸው፤ ኢሬቻ መልካ  እና እሬቻ ቱሉ። ኢሬቻ መልካ በውሃ ዳርቻ ክረምት እንደወጣ ይከበራል። ይበልጡን ምድርን በዝናብ ያጠገበውን ዋቃ በምስጋና የመዘከር በአል ነው። እሬቻ ቱሉ ደግሞ  በተራራ ጫፍ ላይ በበጋው መሀል ይከበራል። ዝናቡ እንዳምናው በወቅቱ እንዲመጣ ዋቃ ይለመናል። ይበልጡን የፀሎት በአል ነው። ቢሆንም…ቡራኬው፤ምስጋናው፤ ፀሎቱ በሁለቱም ኢሬቻ አይቀርም። ለተራራው ወይም ለወንዙ አይሰገድም። እነሱን ለፈጠረ ፤ አምላክ ነው የሚሰገደው። በእምነቱ ልምላሜ እና ውሃ የአምላክ መንፈስ ማደርያ፤ ንፁህ የአምልኮት ስፍራ ነው። ለፀሎት ምቹ እና ሰላማዊ ቦታ ነው። እናም በኢሬቻ መልካ በአል የተፈጥሮን ኡደት ሳያዛባ ያስቀጠለ ዋቃ ይመሰገናል። ዋቃ ይከበራል። ዋቅ ይመለካል።» [ምንጭ፡ ጦብያ መጽሔት፣ ቅጽ 5፣ ቁጥር 11፥ 1990 ዓ.ም.፤ ከገጽ 8-12] ይህ የሎሬት ጸጋዬ ገለጻ በግልጽ እንደሚያሳየው ኢሬቻ የዋቄፈታ ሃይማኖት በዓል ነው። 

ሰው ከፈጣሪው ጋር የሚገናኝበትና ፈጣሪውን የሚያመሰግንበት ማናቸውም  ስርዓት ሃይማኖታዊ እንጂ ባሕል ሊሆን አይችልም። ኢሬቻ  የጥምቀት በዓል በክርስትና እምነት ተከታዮች ዘንድ እንደሚከበረው ሁሉ በዋቄፈታ እምነት ተከታዮች ዘንድ የሚከበር ሃይማኖታዊ በዓል ነው። ኢሬቻ ባሕላዊ እንጂ ሃይማኖታዊ አይደለም የሚል ቢኖር አንድ የኦሮሞ ኡስታዝ ወይም ሼህ ቄጠማ ይዞ፣ ወንዝ ዳር ወሮች ኢሬቻን ሲያከብር ያሳየን!

የኢትዮጵያ ነገሥታትን ሃይማኖትና መንግሥትን አንድ አድርገዋል በማለት ሲያወግዙ የኖሩት የኦሮሞ ብሔርተኞች መንግሥትና ሃይማኖት እንዲለያዩ ታግለናል ሲሉን  እንዳልኖሩ ሁሉ  ዛሬ በመንግሥትነት ሲሰየሙ ግን  የዋቄፈታ ሃይማኖት በዓል የሆነውን ኢሬቻን በመንግሥት ደረጃ ለማክበር  ዝግጅት ማድረጋቸው የኦሮሞ ብሔርተኞች የታገሉት ኢፍትሐዊነት እንደሌላቸው ነው። የኢትዮጵያ ነገሥታትን መንግሥትና ሃይማኖትን ሳይለያዩ ቤተክርስቲያን ይተክሉ ነበር በማለት ሲያወግዟቸው እንዳልኖሩ ሁሉ ዛሬ እነሱ ግን ዛሬ በመንግሥትነት ሲሰየሙ መንግሥትና ሃይማኖትን አንድ አድርገው በመንግሥት በጀት የሃይማኖት  በዓልን በመንግሥት ደረጃ እንዲከበር የዋቄፈታ ሃይማኖት በዓል የሆነው ኢሬቻ የሚከበርበት ወንዝ ይቆፍራሉ፣ በመንግሥት ደረጃ የኢሬቻ ሩጫ ያዘጋጃሉ።

 ኦነጋውያን በየመድረኩ እየተገኙ ሕገ መንግሥት ተብዮው ካልተከበረ ሞተን እንገኛለን  እንዳላሉን ሁሉ  እነሱ ግን «መንግሥትና ሃይማኖት የተለያዩ ናቸው» የሚለውን የሕገ መንግሥታቸውን አንቀጽ ጥርሱን እያራገፉ ኦሮምያ  የሚባለው ክልል መንግሥታቸው ከመንግሥት ካዝና ብዙ ሚሊዮን ብር መድቦ በመንግሥት ደረጃ  በዓሉን የሚያስተናብር አካል  በማቋቋም ሃይማኖታዊውን በዓል ኢሬቻን  ለማክበር ሽርጉድ እያሉ ናቸው። ለዚህም ነው የኦነጋውያንን ፖለቲካ በቅርበት ያጠናን ሰዎች  ኦነጋውያን  የታገሉት ጭቆናን ጠልተው ለዲሞክራሲ ሳይሆን ኢትዮጵያን ወግተው ኦሮምያ የምትባል አገር ለመፍጠር ብቻ ነው የምንለው። ኦነጋውያን መንግሥትና ሃይማኖትን አንድ እያደረጉ ጥርሱን የሚያረግፉትን «ሕገ መንግሥት» ካላስከበርነው ሞተን እንገኛለን የሚሉን የሕግ መጣስ አሳስቧቸው ሳይሆን  «ሕገ መንግሥቱ» በኢትዮጵያ መንበረ መንግሥት ተሰይመው  የሌላውን ሀብትና መሬት እየዘረፉ ለመመስረት የሚያስቡትን የተስፋ አገር ለማበልጸግ የሚያስችላቸውን  የአፓርታይድ ስርዓት ለመዘርጋት  የሚያስችል አይነተኛ መሳሪያ እንደሆነ ስለሚያውቁ ነው። የኦሮሞ ብሔርተኞች በመንግሥትነት ከተሰየሙ በኋላ  ያስቀጠሉትን የአፓርታይድ ዓለም ሕጋዊ ለማድረግ  ሕገ መንግሥት ተብዮው የማይጠቅማቸው ቢሆን  ኖሮ ከሁሉ በፊት ሕገ መንግሥቱ ካልተቀየረ ሞተን እናድራለን ብለው  መንጋቸው ሰልፍ እንዲወጣ የሚቀሰቅሱ  እነሱ ነበሩ።
Posted on  Ethio Semay