Monday, March 21, 2022

ባሮን ፍራንከስታይንና የትግራይ ሕዝብ መመሳሰል የዘመናችን አሳዛኙ ክስተት ጌታቸው ረዳ Ethiopian Semay 6/22/22

 

ባሮን ፍራንከስታይንና የትግራይ ሕዝብ መመሳሰል የዘመናችን አሳዛኙ ክስተት

ጌታቸው ረዳ

Ethiopian Semay

6/22/22

ባንድ ነገር ተጠምጄ ስለነበር ወቅታዊ ትችቶቼን አቁሜ ነበር፡ ይቅርታ። የርዕዮት አዘጋጅ ቱድሮስ ፀጋዬን አስመልክቼ ስላለፉት ተከታታይ ጽሑፎቼ ክፍል 3 ላይ እንዳቆምኩ አይዘነጋም። ክፍል 4 ተዘጋጅቷል። ሆኖም ለዛሬ አንገብጋቢ የሆኑ ነገሮች እየመጡ ስለሆነ ያንን በይደር አቆጥቼዋለሁ።

ዛሬ የምንወያየው ሁለት ጉዳዮችን ነው። ስለ ፓትሪያሪኩ እና እንዲሁም “በብዙ መቶ” የሚቆጠሩ የትግራይ ተወላጆች ጦርነቱ ባስነሳው በርሃብ ምክንያት ወደ ጎረቤት ጠ/ግዛቶች (በአፓርታይዶቹ አጠራር “ክልሎች”) የመሰደዳቸው ጉዳይ “የወሎ አብን” የተባለው ሰደተኞቹን አስመልክቶ እና ወያኔዎች የሰጡት በስደተኞቹ ላይ ያላገጡበት “ፌዝ” ጸያፍ ክህደትን እንመለከታለን።

መጀመሪያ ስለ ፓትሪያሪኩ አቡነ ማትያስን እንመልከት።

አቡኑ በቀርቡ በእሳት ተቃጥለው ስለሞቱት የትግራይ ተወላጆችን አስመልክተው ሐዘናቸውን እና ተግባሩ “የአረመኔዎችና የጥላቻ ቡድኖች” ስራ መሆኑን አውግዘዋል። ይህንን አስመልክቶ የአብይ አሽከር የሆነው “ዳኒኤል ክብረት” የተባለው የዘመናችን ማፈሪያ ሰው በጠባብነት አውግዞአቸዋል። ስለ ዳኒኤል ክብረት አስመልክቶ “ኢትዬ 360” ያዘጋጀው ጥሩ የሆነ ውይትን አድምጡ፤ ትምህርት ታገኙበታላችሁ።

ሌላው ፓትሪያሪኩን አስመልክተው በዘረኛ ትግሬነት የከሰስዋቸው ሰዎችም አሉ። አቡኑ በበኩሌ በዘረኛነት መክሰሱ አግባብነት የለውም ባይ ነኝ። ምክንያቱም ከፓትሪያሪኩ ንግግሮች “አንዳንድ ሐረጎች” በመምዘዝ አጉልተው በመጠቀም እንደ ትግራዊ ተገንጣይ አውግዘዋቸዋል። እኔ ግን እስካሁን ድረስ (የወደፊቱን አላውቅም) ፓትሪያሪኩ የወያኔ ዘረኞች ጠባብ አመለካከት ቢኖራቸው ኖሮ “ከዋናው ኦርቶዶክስ” አፈንግጠው “የሃገረ ትግራይ ቤተክርስትያነ ሃገረ ስበከት”
ያቋቋሙት “ፋሺሰት ካህናትን” ማውገዛቸው ቃል በቃል ባላስታውስም እንዳወገዝዋቸው በጆሮዬ ሰምቻለሁ። ስለዚህ ፓትሪያሪኩ ያላቸው ድክመት ካለ እንደድክምት ማየት እንጂ እንደ ወያኔ ተደርገው የመውሰድ ውንጀላ አግባብነት የለውም የሚል አቋም አለኝ።

አሁን ወደ ትግራይ ስደተኞችን እንመልከት፤-

በርዕሱ እንደምትመለከቱት የትግራይ ሕዝብ፤ የወያኔና “የፍራንክስታይን” ተመሳሳይነትን እንመልከት።  “ፍራንክስታይን ሞንስተር” ማለት በ1818 ሜሪ ሼሊ የተባለች ልብ ወለድ ደራሲት በደረሰቺው ልብ ወለድ ድርሰት ውስጥ (1818) “ባሮን ፍራንክስታይን” የተባለ ተመራማሪ “ሙታንን” ለማስነሳት በሚል ምርምር በመነሳሳት ከሙታን ሬሳዎች አካላት በመውሰድ ባንዳች የመመራመር ጥበብ “አዲስ ሰው” እፈጥራለሁ ያለውን ምርምሩ ሳይሳካለት ድንገት የፈጠረው ነገር “አስፈሪ ጭራቅ” ሆኖ በመፈጠሩ ተመልሶ ፈጣሪውን “ባሮን ፍራንከንስታይን” ውጦ ስባብሮ ድምጥማጡን አጠፋው።ስለሆነም “ፍራንክስታይን ሞንስተር”በመባል ይታወቃል። ወያኔዎች ወይንም ብዙ የትግራይ ምሁራን “ወያኔ” የፈጠረው የትግራይ ሕዝብ እንጂ “ወያኔ” የትግራይን ሕዝብ አልፈጠረም ሲሉ ሁሉም በሚገርም መስማማት አንድ  ዓይነት ስምምነት ደርሰዋል።

 ፍራንኬንስታይን ጭራቅ በመፍጠርየሕይወትን እና የሞትንምስጢር ማወቅ  የሞከረውን ፈጠራ ፈጣሪውን ቢያጠፋም አዲስ ዝርያመፍጠር እናሕይወትን ማደስይቻላል ብሎ ያምናል። እነዚህን ነገሮች በፍላጎት ለመሞከር ይነሳሳል። ፈጠራው ትልቅ ዋጋ ቢያስከፍልም ትልቅ ነገር ማሳካት ይቻላል ቢልም ራስን እስከማጥፋት የሚኬደው ጥፋት “የትግራይ ሕዝብና የወየኔ ትግሬዎች” ታሪክ ተመሳሳይነት አለው።በዚህ ተመሳሳይነት የትግራይ ሕዝብ ወያኔ የተባለ “ጭራቅ” ፈጥሮ “ጭራቆቹ” በፈጣሪው በትግራይ ሕዝብ ላይ ያስከተሉት ጥፋት ለታሪክ ማሕደር ለማስገንዘብ ብዙ መቶ አመታት ይፈጃል።

የቅርቡን ጥፋት እንመልከት። “ጭራቆቹ” እስከ ደብረብርሃን ጫፍ እስኪደርሱ ድረስ የብዙ ሰው ንብረት፤ ኑሮ እና ህይወት አበላሽተዋል። ጭራቆቹ የፈጸሙዋቸው ዘግናኝ ወንጀሎች ስለምታውቁት በዝርዝር ከመሄድ ይልቅ ከፍተኛ ወንጀል ሲፈጽሙ በኢትዮጵያ ሕዝብም ይሁን በትግራይ ሕዝብ ህይወት ላይ ከፈተኛ ወንጀል ፈጽመዋል በሚል ልለፈው።

በሚያስደነግጥ እና በሚገርም ሁኔታ በምስኪን ወጣት የትግራይ ወጣት ተዋጊዎች ላይ የደረሰባቸው የሞት፤የመቁስልና አካል ጉዳት ኪሳራም ሆነ እንዲሁም በሌሎቹ በዓፋሮችና በአማሮች ያደረሱት ጉዳት ከመጤፍ ሳይቆጥሩ አገኘን የሚሉት ድል ስንመለከት “ፒሪክ ቪክትሪ” የሚሉት ድል ነው።

 ካሁን በፊት ከኤርትራኖች ጋር ስከራካር ስለ “ፒሪክ ቪክትሪ” ሰፊ ሃተታ አቅርቤአለሁ። “ኤርትራኖችም ሆኑ ትግሬዎች” ድል የሚሉት ይህንን “ፒሪክ ቪክትሪን” ነው። የፒሪክ ድል “ብዙ ዋጋ የሚከፍልበት ድል ነው” ፣ ምናልባትም ለማሸነፍ የሚከፈለው ዋጋ “ትርፉ” ከስሜት ውጭ ጊዜአዊ ፍንደቃ ካልሆነ ኪሳራው ከድሉ ጋር መመጣጠን ካልሆነ “ድል” ተብሎ የተጠራው “አራስን በራስ ከማጥፋት” የሚተረጎም ፍራንሰተይን ሞንተር” ዓይነት ወጤት ነው ማለት ነው።

በቅርቡ በርሃብ ምክንያት “በመቶዎች” ተብለው ይቆጠሩ እንጂ በሺዎች እንደሚከተሉ የሚገመት የትግራይ ተወላጆች ወደ አማራ “ክልል” በመምጣት ከጭራቁ ወያኔ እያመለጡ ምግብና መጠለያ  ፍለጋ መምጣታቸው በዜና ማሰራጫ ሲናገሩ ሰምተናል።

 ወደ ወገኖቻቸው በመምጣታቸው እንደመደሰት ይልቅ “የውሎ አብን” የተባለ የፖለቲካ ድርጅት “ወያኔ” የላካቸው ናቸው በሚል በሙሉ ልቦና በመተማመን ሀፃናትን የታቀፉ እናቶች እና ትንንሽ ልጆችን በወያኔነት በድርጅታዊ መግለጫው ወንጅሎአቸዋል። ይህ እጅግ የሚኮነን የአብይ አሕመድ አሽከር በመሆን መሳቂያ ሆኖ የቀረው “ዘረኛ ድርጅት” መላው ኢትዮጵያዊ ነኝ የሚል ዜጋ ሊያወግዘው ያስፈልጋል። ስደተኞች መስለው ሊላኩ የሚችሉ ሰዎች ይኖራሉ ወይ? አዎ! ወያኔ የተካነበት ታሪኩ ነው። ሆኖም መላውን ስደተኛ እና ህጻናት የታቀፉ ሁሉ በወያኔነት መወንጀል “ዘረኛነት” እንጂ ሌላ ሊሆን አይችልም።ያውም በገዛ አገራቸው!!

ስለ ወሎ አብን ስናወሳ የወሎ አብን ችግር አለበት። ካሁን በፊት “ዮሱፍ ኢብራሂም” የተባለ ዘረኛ 30000 ትግሬ አቅፈን የምንቀልብበት ምክንያት የለም በማለት ትግሬዎች ኢትዮጵያዊያን እንዳልሆኑና የወሎ ሕዝብ ዕርጥባን የሚተዳደሩ በማስመሰል የተናገረው ለብዙ ትግሬዎች የጅምላ እስራት ምክንያት እንደሆነ እናስታውሳለን። የወሎ “አብን” በትግሬዎች ላይ ጥላቻ እንዳለው ተደጋጋሚ ልሳኖቹን እድምጠናል። ይህ እናወግዘዋለን።

ሌላው ዋናው ጭራቅ የትግራይ ሕዝብ የፈጠረው “ወያኔ” የተባለ የጉግ ማንጉግ ስብስብ ነው።በርሃብ አለንጋ የተገረፉትን ህጻናት፤ እመጫት፤እርጉዞች፤ሽማግሌዎች ወጣቶች ከትግራይ ሸሽተው ወደ ወሎ ሲጠለሉ በውጭ አገርም ሆኑ በውስጥ አገር ያሉ የወያኔ ጭራቆች በርሃብ ምንክንያት የተሰደደ የትግራይ ሰው እንደሌለ እና ትግራይ ውስጥ ‘ርሃብ እንደሌለ’ ተናግረዋል።

“ካሁን በፊት የተዋለድዋቸውን ዘመዶቻቸውን ለመጎብኘት የሄዱ እንጂ “ከቤተሰብ ጋር ግንኙነት ከሚደረግ አንቅስቃሴ ውጪ በርሃብ” ምክንያት ከትግራይ ወደ አማራ አገር የተሰደደ የትግራይ ተወላጅ የለም” ሲል ካናዳ ተመችቶች ልጆቹን እያስተማረ የትግራይ ሕዝብ ሲቸገር ግን “የትግራይ ሕዝብ የተራበ የለም” በማለት በርሃብተኞች ላይ ሲያሾፉና በሕዝባችን ህይወት ሲቀልድባቸው የሰማነው

“የትግራይ ክልል የውጭ ጉዳይ ግንኙነት አስተባባሪ” ነኝ የሚል  ዮሃንስ አብርሃ የተባለ  ከጭራቆቹ ወያኔ በርሃብተኞቹ ላይ ሲቀልድ ሰምተናል።

ስደተኞቹ በርሃብ ተቸግረው ከትግራይ ወደ አማራ መምጣታቸውን ‘ለአሜሪካ ድምፅ አማርኛ ክፍል” በሰጡት ቃለ ምልልስ ተንተርሶ ጭራቁ ዮሃንስ አብርሃም “አንድም የትግራይ ተወላጅ የሆነ ምግብ ፍለጋ ወይንም በርሃብ ምክንያት ወደ አማራ የሄደ የለም። የሄዱበት ምክንያትም ከትግራይ ክልል ተፈናቅለው በሰሜን ወሎ ቆቦ ከተማ የተጠለሉ የትግራይ ስደተኞች ከዘመድ ጥየቃ ግንኙነት ጋር የተገናኘ ነው ሲል በርሃብተኛው የትግራይ ሕዝብ ህይወት ከቀለዱት አንዱ ነው።

ይህ የጭራቆቹ በርሃብተኛ ሕዝብ መቀለድ አዲስ አይደለም፡ በ1977 ዓ.ም በትግራይ ርሃብተኛ ገንዘብ የተጫወቱበት አሳፋሪ ማሕደር በገብረመድህን አርአያ እና በአረጋዊ በርሐ የተዘገበ ነው። የትግራይ ሕዝብ ወደ ወሎ ተሰድዶም ቢሆን የምግም የመጠለያ አቅርቦት እንዳላገኘ ቢሆንም ስደተኞቹ በርሃብና በነፃነት የመናገር ፤የመተንፈስ መብታቸው ኩፉኛ መሰቃየታቸው ከጭራቆቹ ከበባ ሰብረው መምጣታቸው ይናገራሉ።

ጭራቆቹ ግን የተራበውን ሕዝብ እንደመያዣ አድርገው ለፖለቲካ መጠቀሚያ ለማድረግ እንደፈለጉ “ ዮሃንስ አብርሃ፤ጌታቸው ረዳ፤ ደደቢት ሚዲያ እና ወዘተ…” የመሳሰሉ የወያኔ ጭራቆች በተራበ ሕዝብ ላይ ቁማር እየተጫወቱ መሆኑን ከሚያስተላለፉት መልእክት መረዳት ይቻላል።

የሚገርመው ባንድ በኩል ሕዝባችን ተርቧል፤ በርሃብ ምክንያት በሺዎቹ ሞተዋል፤ እያሉ ሲጨሁ፤ የተራቡ ሰዎች ምግብ ፍለጋ ወደ አቅራቢያ ሲሸሱ ደግሞ “ዘመድ ጥየቃ እንጂ ምግብ ፍለጋ አልሄዱም” እያሉ በረሃብተኛው ላይ ሲቀልዱ መስማት በቀላሉ የማይታይ በታሪክ ሊመሰገብ የሚገባ የወያኔ “ጉግ ማንጉጎች” አንጀት ምን እንደሚመስል ማሳያ ነው።

ታዲያ “ባሮን ፍራንክስታይን” የተባለ ተመራማሪ “ሙታንን” ለማስነሳት በሚል ምርምር በመነሳሳት ከሙታን ሬሳዎች አካላት በመውሰድ ባንዳች የመራመር ጥበብ “አዲስ ሰው እፈጥራለሁ” ያለውን ምርምሩ ሳይሳካለት ድንገት የፈጠረው ነገር “አስፈሪ ጭራቅ” ሆኖ በመፈጠሩ ተመልሶ ፈጣሪውን “ባሮን ፍራንከንስታይን” ውጦ ስባብሮ ድምጥማጡን እንዳጠፋው ሁሉ “ወያኔ” የተባለ “ሰዋዊ ጭራቅ” ወደ “ጉግ ማንጉግ” የተለወጠው “አዲስ ሰው” ፈጣሪውን የትግራይ ሕዝብን መልሶ በመዋጥ ከመኖር ወደ አለመኖር አሸጋግሮታል። ባሮን ፍራንከስታይንና የትግራይ ሕዝብ መመሳሰል የዘመናችን አሳዛኙ ክስተት።

ጌታቸው ረዳ

Ethiopian Semay