Friday, October 17, 2008

በትግራይ ሕዝብ ላይ ስትጮህ የሰማሗት የከረንት አፈይርስዋ አራዊት





 በትግራይ ሕዝብ ላይ ስትጮህ የሰማሗት የከረንት አፈይርስዋ አራዊት
ጌታቸዉ ረዳ የጎሳ ድርጅቶች የሆኑ ኦነግ እና ህወሓት በ1991 ዓ.ም በአሜሪካኖችና በእንግሊዞች እርዳታ በጋራ ወደ ሥልጣን ከወጡ ወዲህ የጎሳ ግጭቱ ከጥላቻ አልፎ ወደ መገዳደል እና ወደ ዘር ማጽዳት ዘመቻ የተሸጋገረበት የዓይን ምስክሮች፤የዘመቻዉ ሰለባዎች፤ታሪክ ዘጋቢዎች የሰብአዊ መብት ጠበቃዎች እና የዜና ወኪሎች የዘገቧቸዉ ሰነዶች በተለያዩ ወቅቶች ለሕዝብ እንዲነበቡ ተደርገዋል።
የጎሳ ፖለቲካ አራማጆች ጎሳቸዉን ለይተዉ ጥብቅና ለምን እንደቆሙ የማሕበረሰብ-የስነልቦና ሊቃዉንት ሲገልጹት፡ባጭሩ የጎሳ ፖለቲከኞች ዓላማ የአንድን ቋንቋ ተናጋሪ ክፍለ ህዝብ በቀረዉ ሕዝብ ላይ የበላይ ለማድርግ መፈለግና መብት በማስከበር ሥም ወደ ሥልጣን ቁንጮ መረማመድ ነዉ ይላሉ።ይህ እንዳለ ሆኖ፤ያብዛኛዎቻችን ችግር ጎሰኘቹ ወዳዘጋጁልን ወደ ዝብርቅርቁ ጨዋታቸዉ ገብተን በማወቅ የገዛ ራሳችንን ለማጥፋት ታይተናል።
 
አለፍ አለፍ ብየ ለትዝብት በጊዜ ሰሌዳ የምጎበኛቸዉ የፓል-ቶክ መድረኮች አሉኝ። ሰሞኑን ተራ ደርሶት የጎበኘሁት “Ethiopian Current Affairs Discussion” የሚባለዉን የፓል ቶክ መድረክ ነበር። መድረኩን ሦስቴ ያክል የጎበኘሁት ይመስለኛል። ከሦስቱ ሁለቱ ጊዜ ከተሳታፊዉ ይልቅ አዘጋጆቹ ለምን እንደሚጮሁ ባይገባኝም ሃይለ ቃል እየተጠቀሙ ፤የቀይ መብራት ቁልፍ በመጫን ጎብኚዎችን የማባረር ሥልጣን እንዳላቸዉ አስኪ ሰለች ደጋግመዉ ሲዝቱ ዛቻዉ ቡረቃዉ ከመጠን በላይ ነዉ። በአመለካከት የተቃወማቸዉ በተለይም ከረር ያለ እንደሆነ ቅጽበታዊ-ቁልፉን ተጭነዉ ከመድረኩ ያስወግዱታል።ባጭሩ “ይገድሉታል!” በነገራችን ላይ ይህ ነገር በሳላ በተባሉ መድረኮችም ይህ ጸባይ ሲያደርጉ ታዝቤአለሁ። ከዚህ ፍርሃት የተነሳ ሌሎች የሚወያዩትን ሃሳብ እንዳያመልጣቸዉ በመስጋት ከመድረኩ ላለመባረር በተለይም አዘገጆቹን ወይንም የአዘጋጆቹ ቅርብ ተዋዳጆች(ጉሩፖች) ላለመተናኮል/ላለመነካካት በመጠንቀቅ ሃሳብ ከመስጠት ተቆጥበዉ ሃሳብ ከመሰንዘር ይልቅ አድማጭ መሆንን ይመርጣሉ። አዘጋጆቹ በተለይም (ሴቲቷ) በመንግሥት ሥልጣን ተቀጣሪ ቢሆኑ ኖሮ የደርግን ካድሬዎች ዓይነት ጋጠወጥ ማን አህሎኝነት ባሕሪ ቅጂ ከመሆን አያልፉም ነበር የሚል ግምት አለኝ።
 
ይህ ዘመኑ የለገሰን ጥበብ ልቅ-መብት ተሰጥቶ ያለተቆጣጣሪ ማንም ለፍዳዳ መድረኩን እየከፈተ “የመሸታ ቤት ዲሞክራሲ” ፈልስፎ ሕዝብን ሲዘለፍ ስናደምጥም የጥቡበ መጥፎ ገጽታዉ ተጠያቂነት ያለመኖሩ በእወነቱ ይህነን የሚያስቆም መንገድ መፈጠር አለበት እላለሁ። ሰሞኑን በእኛ በትግሬዎች ላይ ስትጮህ የሰማሗት የካረንት አፈይርስዋ አራዊት ምን ስትል እንደሰማሗት አንዳፍታ ላዉጋችሁ።
 
በመድረኩ ላይ የመነጋገርያዉ ርዕስ በሸራተን ሆቴል ዉስጥ ትግራይን ለመገንባት በተደረገዉ ዓለም አቀፍ የትግሬዎች ማሕበር የገንዘብ መዋጮ ላይ ነዉ።ልጅቷ ከአዘጋጆቹ አንዷ ነች። ትጮሃለች፤ትሰብካለች፤ስሜቷ ሰማይ ደርሷል። አዋጊም አዛዢም ትልም አዉጪም ሆናለች።ስለ ሸራተኑ እና ስለ ትግራይ ሕዝብ የምታዉቀዉም የማታቀዉም የተቻላትን ሁሉ እየዘበራረቀች ታወራለች። የሕዝብ ቆጠራዉ ከየት እንደለቀመቺዉ ባለዉቅም የትግራይ ሕዝብ 5ሚሊዮን መሆኑን ታስረዳለች። “እኛ የኢትዮጵያ ሕዝቦች በቁጥር ሲነጻጸር እጅግ ስለምንበልጣቸዉ ተባብረን 5ሚሊዮኖቹን ትግሬዎች ማሸነፍ አለብን!” እያለች ትእዛዝ እና ቅስቀሳ ታካሂዳለች። አብዛኛዎቹ የድጋፍ ጽሁፍ፤ አንዳንዶቹም በሕዝብ ላይ የብልግና ትችት ሲጽፉ አንዱም በሁኔታዉ ተገርሞ “ይህች ሴት አደገኛ ነች! ሲበዛ ማይምነት አይሏታል! የሩዋንዳን ዓይነት ግጭት በእኛም ዘንድ እንዲነሳ እየሰበከች ነች!..ወዘተ በማለት 5ሚሊዮን የትግራይ ሕዝብ “እናሸንፈዋለን” ማለት ብልግና እና ወንጀል ነዉ፤ ነዉር ነዉ” በማለት ሕዝብን እናንበርክከዉ ስትል በጮኸችዉ በዛችዉ አራዊት ላይ ቅዋሜዉን የገለጸዉ ሰዉ ቅጽበታዊ የማስወገጃ ቁልፉን ተጠቅመዉ ከመድረኩ አስወገዱት። ሌላዉም እንደዚሁ አስወገዱት፤ሁኔታዉ አላማራቸዉ የተቀሩት ቀስ እያሉ ከመድረኩ ራሳቸዉን አስወገዱ። በዚህ ጊዜ እኔም ቅሬታየን ልተነፍስ ብል ምን ዕጣ እንሚደርሰኝ ስላወቅኩ ነጻነትን በሚቃወም ሽብር በሚለቀዉ ቁልፋቸዉ “ሳልገደል” ራሴን አስወገድኩ።
 
ይህ መድረክ ካሁን በፊት ተመሳሳይ ጸረ ትግራይ ሕዘብ ቅስቀሳ ተደርጎ የመድረኩ አዘጋጆች ሰበካዉን ባለማስቆም በነጻነት እንዲተላለፍ በማድረጋቸዉ ያንድነትና የሰላም ወገኖች ያንኑ ቀድተዉ ለሕዝብ እንዲደመጥና ጥላቻ እና ጎሰኛነት ወንድም በወንድም ላይ እህት በእህት ላይ ምን የት ያህሉ እየተሰፋፋ መሄዱን ለማስገንዘብ ይፋ ሆኖ በየህዋ ሰሌዳዉ ተለጥፎ አንደ ነበር ይታወሳል። ይህ መድረክ የብርሃኑ ነጋ፤የብርቱካን መዲቅሳ፤ብርሃኑ መዋ እና የአንዳረጋቸዉ ጽጌ የፕሮፓጋንዳ መፈንጫ እንደነበረ እና ዛሬም ካልተሳሳትኩ ፖለቲከኞቹ ከሚጠቀሙበት ሚዲያቸዉ አንዱ ይህ ጎሰኞችና በስሜት የሚነዱ እንሰሳዎች የሚበዙበት “ኢትዮጵያን ካረንት አፌይርስ ዲሰካሽን” ይመስለኛል። በዚህ ሚዲያ ሕዝቡ አትኩሮቱ እንዲጥልበት ሳሳስብ ቀጥሎ ወደ ፖለቲካዉ ሂሱ በመግባት ትንሽ ልበል እና ልሰናበት።
 
ብዙ ፖለቲካ ድርጅት መሪዎች እና መግለጫቸዉ ምንም እንኳ ወያኔ ጎሳዉን ለመጥቀም ቢሯሯጥም በሰባዊ እና በዲሞክራሲአዊ ምብቶች ሕዝቡ እንደኛዉ በወያኔ መሪዎች እና ፖሎሲ የተረገጠ በመሆኑ ሕዘቡን ጠላት አናደርገዉም ቢሉም ዛሬም በርካታ “የሰዉ-አራዊቶች” በዙርያችን ስላልታጡ የትግራይ ሕዝብ እንደጠላት እያዩ “እናሸንፈዉ! እናንበርክከዉ! እናጥፋዉ! እንማርከዉ..” የሚሉ አልጠፉም።ልጅቷ ከሆዷ ዉስጥ አስራ አፉን ከፍቶ የተራበዉን አራዊቷን እኛኑን 5 ሚሊዮናችን ለመዋጥ እፈታዋለሁ እያለች የምታስፈራራን ዛቻዋን ለምን እሰከዚህ ድረስ በድፍረት መድረክ ላይ ወጥታ የሕዝብ ፍጅት ለማየት እንደናፈቃት ራሴን ስጠይቅ በወቅቱ ቅስቀሳዋ አስቆጥቶ-ቢያሳዝነኝም፡ ልጅቱን ቀጥተኛ ተጠያቂ አላደረግኳትም።ምክንአቱም ከፋፋይ ሃይል ብለን የምንጠራዉ ብቻ አይደለም ተዋናያንና መሪ ወንጀለኞች። ለምሳሌ “በኦኖጎች እና በመሰሎቻቸዉ እንዲሁም የእስልማና አካራሪ ሃይላት በአማራዉ እና በኢትዮጵያ ተዋህዶ ቤተክርስትያን ላይ ያላቸዉን ጥላቻ እንዴት እና ወዴት እንዳመራ ማንስ አንደመራዉ ጸሐፊዉ አቶ ጸጋየ ገ/መድህን አርአያ ሲገልጹ እንደሚከተለዉ አቅርበዉታል
 
“ወንጀላቸዉ አማራ ገድለዉ አርደዉና ከገደል ጫፍ ወደ ታች በመጣል በጭካኔ ብቻም አይደለም። በሰዎቹ መርዝ አብደዉና ያበደ ፍልስፍና እንግበዉ ያልሆኑትን ሆነዉ፤ያልሆነዉን ረግጠዉ ከዚህ መሬት ማህጸን ዕኩል የተወለደዉን የእናትም የአባትም ልጅ ጠላት አድርገዉ በማየታቸዉ ሌሎችም እንዲያዩ በማድረጋቸዉ አዝናለሁ።ታሪክ አያዉቁም አልልም።ያዉቃሉ። በእነዚህ ተለማማጅ የፓሎቲካ ሰዎች ላይ የምናየዉ ጉድፍ ግንባሩን ግን በክፋ ክፉ የታሪክ ገጽ ላይ ለማተኮርና በክፉ ክፉ መፍትሔ ላይ ዓይናቸዉን በመጣላቸዉ ነዉ። ይህ ሕዝብ ስለሚቀጥለዉ ትዉልድ ሕልዉና ሲጨነቅ እነሱ ዛሬ ሊያገኙ ስለሚጓጉት ሥልጣን እንቅልፍ አልባ የሚሠሩት ተንኮል አልተገጣጠመም እንጂ ሰንደቅ ዓላማችን ብቻ ሳይሆን የሁላችንም ሕልዉና ዋስትና ሊኖረዉ አይችልም ነበር። በደኖ ይሉናል። አርሲ ይሉን ይሆናል። ቀጥሎ ግምቢ ይሉን ይሆናል። አሶሳስ?...”
 
በእርግጥም እሳቸዉ እንዳሉት ማንነታቸዉን ሲጸየፉና ያልሆኑትን ካልሆኑበት ሥፍራ ሲፈልጉ ማን አለመሆናቸዉን ለማወቅ ሳይችሉ በጨለማ ሲዳክሩ እያነጣጠሩበት ያለዉን ወዳጅ ይሁን ጠላት መለየት ሳይችሉ ቀርተዉ እንዲሁ በደፈናዉ ራሳቸዉን እና የራሳቸዉንም የሆነዉን የዒላማቸዉ ተጠቂ ያደርጉታል። ስለሆነም በከረንት አፌይርስ ፓልቶክ መድረክ ላይ ወጥታ በ5ሚሊዮን የትግራይ ሕዝብ ላይ የዘመቻ ጥቃት ጥሪዋን ስታስተላልፍ የሰማሗት አራዊት የአንድ አገር ሕዝብ ክፍል በሌላኛዉ ክፍለ ሕዘብ ላይ ተሸናፊ እና አሸናፊ አንበርካኪ እና ተምበርካኪ የሚታይበት መድረክ መቀስቀሷ፤ በወየኔ እና በሻዕቢያ መሪዎች ፉክክር ምክንያት የመረብ ምላሽ ህዝብ እና የትግራይ ሕዝብ ተላልቆ አንዱ በሌላኛዉ የአሸናፊነት ስሜት እንዲኖረዉ የተጫረዉ “የሞኞች- ጦርነት” ከዚህ የማሸነፍ እና የተሸናፊነት ስነ ልቦና አስተሳሰብ የመነጨ አደገኛ አስተሳሰብ መሆኑን ይህች ልጅ የብዙዎቹ ደንቆሮች ናሙና መሆኗን አልተጠራተርኩም። በተለይም ልጅቷ የጠራ አማርኛ ስትናገር በመስማቴ አመራ ትሆን? የሚል ጥያቄ ስላደረብኝ፤ ከሆነችም ተባብረን እናሸንፈዉ ምትለዉን የትግራይን ሕዘብ ለአመራዉም ሆነ ለተቀረዉ የኢትዮጵያ ክፍለ ሕዝብ ምኑ መሆኑን ላስረዳ።
 
አታዉቀዉ ሆና “እኔ አማራ እንጂ እኔ ጉራጌ፤ እኔ ኦሮሞ እንጂ፤ እኔ አደሬ እንጂ እኔ ዓፋር እንጂ.. ሶማል አንጂ…ትግሬ አይደለሁም ብትለንም” ወያኔም “በጎሰኛ መጽሃፉ ትግሬነት ለዕገሌ… እንጂ .. ለዕገሌና ..ለእገሊት … ምኑም አይደለም ቢለንም” እሱም እነሱም አናንተም አንቺም አሷም እኔም ሁላችንም ትግሬዎች ነን።ከትግራይ እና ከአማራዉ ደም እና አጥንት ባህሪና ባህል ያልተቀላቀለ ጎሳ ከቶ ማንም የለም። ትግራይ እና አማራዉ ያገሪቷ መሰረታዊ መስራቾች ሆነዉ በግንባር የተሰለፉ የኢትዮጵያ ህብረተሰብ መሆናቸዉ ኢትዮጵያዊ ሁሉ መገንዘብ የታሪክ አዋቂነት ይመስለኛል። -መሬቷን-ድምበሯን ሰማይዋንና ወለሏን ማለትም የአገሪቱን ግምብ ሲገነቡ በተዛማጁ የእነኚህ ማሕበረሰብ ደም እና አጥንት ከሌላዉ መሕበረሰብ ቋንቋ፤ባሕል፤ደም እና አጥንት ጋር እየተዛመዱ እየተጋቡ እየኖሩ እና እየተገበያዩ በሰላሙና በጦርነቱ “የተዋሃደ-ማህበረስብ” ዘርተዉ አብቅለዉ አሰሳድገዉ ይሄዉ እስላሙም ክርስትያኑም ተዋህደዉ ኦሮሞዉ ጋምቤላዉ ቤንሻንጉሉ ጉራገዉ አማራዉ ትገሬዉ… ወደ 75 ሚሊዮን የሕዝብ ብዛት ደርሰናል። እኛ ያለፉት የነሱ ዉጤቶች አብረን እነጋገራለን።ባስደናቂ ጥበባቸዉ በ አንድ መሬት ባንድ አገር ወለልና ጣራ አኑረዉን ሄዱ።ሂደቱ ሻዕቢያዎች፤ኦኖጎች ወያኔዎች ላማስቆም ቢሞክሩም ተፈጥሮን ማስቆም አልተቻላቸዉምና ዛሬም ከማንኛቸዉም ቁጥጥር በላይ ወጥቶ ዕድል በተገኘ ቁጥር ዉህደቱ በመቀጠል ላይ ነዉ። ቋንቋዉን መናገር የደም ትስስሩ ማንነቱ መለያ ሊሆን አይችልምና ሁላችንም የአንድ ፈጣሪ የፈጠረን ፍጡር ወንድም እና እህትማማቾች ነን።በዚህ ላይ አንድ ልበል እና ልሰናበት።
 
“አማራ በነገድ በዘር በቋንቋ በባሕልና በዕምነት ከአክሱማዊያን/ትግሬዎች ጋር ተቀራራቢ እና ተመሳሳይ ከሆኑት ወገኖቹ የአማራ -ብሔረሰብ አንዱ ነዉ። የአክሱምን/የትግሬዎችን መንግሥት በቀጣይ ያዋቀሩት አማራዎች ናቸዉ። ስለሆነም ነዉ “የአማራ/ትግራይን (ኢትዮጵአዊነት) ከባድ የዘር ሚዘን ተሸክመን ከምፅዋ አስከ ቦሮና ከጋምቤላ አስከ በርበራ ከሚያደክም እና ከሚፈትን ጉዞ ቤጃዎች አገዎች ኦሮሞዎች ገላግለዉን ቁጭ!! የአማራም ሆነ የትግራይ ዘረ-ድንግልነት እና ዘረ-ንጹህነት ከብዙ ዘመናት በፊት መፈራረሱን አረጋግጠናል” {ዋሕድ (የሕብረት ልሳን) ቅጽ -ቁጥር 4 ገጽ 9}። //-// አምላክ ኢትዮጵያን ይጠብቅ http://www.ethiopiansemay.blogspot.com/