Sunday, April 18, 2021

ስለ ታማኝ ክፍል 2 ጌታቸው ረዳ Ethio Semay 4/18/2021

 

ስለ ታማኝ

ክፍል 2

ጌታቸው ረዳ

Ethio Semay

4/18/2021



ባለፈው ክፍል 1 እንደ መግቢያ ስለ ታማኝ በጨረፍታ እንድትመለከቱት ያደረግሁት የዲያስፖራው እንቅስቃሴ የፖለቲካ መጥፎ ጎኑ ምን ይመስል እንደነበር አቅርቤዋለሁ። በስፋት ለማቅረብ መጽሐፍ መጻፍ በቻልኩ። ሆኖም ያ በቂ ይመስለኛል። ዛሬ አብይ ወደ ሥልጣን ከመጣ ጀምሮ የታዘብኩዋቸው ስለ ታማኝ ንግግሮቹ እና የወሰዳቸው በጎ ተግባር ስለሚታወቅና ለብዙዎቻችሁ መንገር ስለማያስፈልግ፤ ሊያደርግ የሚገባው ሆን ብሎ የለገመባቸው ተግባሮች እና ያደረጋቸው ንግግሮቹን እንመልከት።

ከዚያ በፊት ግን በቅርቡ February 2021 ኢትዮጵያ ብሮድካስት በተባለው አዲስ አባባ የመንግሥት የዜና ማዕከል ታማኝ ቃል መጠይቅ አድርጎ ነበር። “ዝነኛ ሊሆን ይችላል፤ የመንግሥት ተጠያቂ ሊሆን ይችላል ባደረገው ንግግር መጠየቅ አለበት፤ ሕዝቡ ይጠይቃል።” ብሏል። እኔም እየደረግኩ ያለሁት ይህንን ዝነኛ ሰው ያደረገውን ንግግር በሚመለከት ነው። አሁን ወደ ውይይታችን።

ባለፈው ክፍል 1 “ባሕርዳር ሄዶ ወጣቶችን ሰብስቦ ሲያነጋግር (ጠቅላይ ሚኒስትሩ) ከሥራቸው ያሉት ሰዎች አላንቀሳቅስ የሉዋቸው መሰለኝ…” በማለት ይጀምርና “ (ውጤት/ዲሞክራሲ/ለውጥ) ሂደት ነው” ስለዚህ እንታገሳቸው “ሚራክል አንጠብቅ” ሲል የተናገረውን ጠቅሼ ነበር። ይህ ንግግሩ አብይ አሕመድ በነገሠበት በ 6ኛው ወሩ ነው። “ሦስት አመት ውስጥ ጠ/ሚኒስትሩ አላሰራ ያልዋቸው ከስራቸው ያሉ ሰዎች ናቸው’፡ ስለዚህ ጊዜ እንስጣቸው እንታገስ ፤ዲሞክራሲ “ፕሮሰስ” “ሂደት” ነው፤ ስለዚህ ሚራክል አንጠብቅ” የሚለው ንግግሩ ዛሬም ያመነበት ይመስላል።

 “የሰው ልጅ ህይወት መቀጠፍ አሁኑኑ ይቁም፤ በቡራዩ በአዲስ አባባ ወጣቶች የተደረገ ግፍ አሁኑኑ ይገታ፤ ጊዜያዊ የሽግግር መንግሥት አሁኑኑ፤ የአማራ መጨፍጨፍ አሁኑኑ ይቁም፤…” ብለው ጸረ የአብይ ኦሮሙማ ሥርዓት የታቀወሙትን ማሰር ጀምሮ ነበር (በ6 ወር ዕድሜው)። ታዲያ ታማኝ ያኔ በወያኔ ጊዜ የተቃወመው “እየገደሉ የዲሞክራሲ ሂደት ነው ሲሉ የነበሩትን የተቃወመው የወያኔዎች መስመር” ዛሬ አብይ ሲመጣ ፡ሂደት፡ ነው፤ ብሎናል።

 ያውም አብይ እራሱ በንግግሩ ምን እንደተናገረ ታማኝን ላስታውስና እናንተ ፍረዱ። ይህ የተቀነባባር ተከታታይ የአብይ ንግግር በወንድሜ በቴድሮስ ፀጋየ (ርዕዮት ሚዲያ) ለውይይት የቀረበ አውዲዮ-ቪዲዮ ነው። ጠቃሚ ስለሆነ እነሆ አትኩሩበት።

አብይ እንዲህ ይላል።

 

“ሥልጣን ለመያዝ ወጣቶች ማለቅ ቤቶች መፍረስ የለባቸውም።” (አብይ)-

 

እንዲያ ብሎ የተናገረውን ንግገሩ በራሱ ወታደሮችና ባለሥልጣናት ሕዝብ ሺጨፈጭፉ ወቀሳ ሲደርስበት ደግሞ እንዲህ በማለት የላይኛውን ንግግሩ በእራሱ ንግግር ይጻረራል።

 

“በሞት መሃከል ሆነው ኢትዮጵያ ውስጥ ሞትን የሚያዳንቁት ለምንድነው? አሜሪካ ውስጥ በኮረናም በግጭትም የሞተው ሰው ብዛት “ኢትዮጵያ ውስጥ አልሞተም” ።ለምንድ ነው በኢትዮጵያ አጋንነን የምናየው?

 

 “ቻለንጅ መገንዘብ ጠቃሚ ይመስለኛል። ለምሳሌ ኢትዮጵያ ውስጥ ከሁለት አመት በፊት በነበረው ነውጥ ፤ በነበረው አመጽ ፤ በነበረው ለውጥ ፤ አጠቃላይ በኢትዮጵያ ደረጃ 2000 ሰው ገደማ እንደሞተ ይገመታል።  በዚያው አመት በአሜካ አገር ውስጥ 17,000 (አስራ ሰባት ሺሕ) ሰው ሞቷል። ግን ኢትዮጵያ ውስጥ ግጭቱ ተፋፍሞ ሁላችንም የሚያስጨንቅ ፤ ፓርላማውን የሚያስጨንቅ በዚህ መልክ የሆነበት ዋናው ምክንያት፤ ‘ግጭት’ የምንገነዘብበትና የምንፈታበት መንገድ የራሱ የሆነ ችግር ስላለው ነው። ዘንድሮ በቴክሳስ ፤ በኦሃዮ፤ አንዳንድ ጊዜ “ዎል ማርት” ተብሎ በሚጠራ ሱቅ ዕቃ ለመግዛት ሄዶ በርካታ ሰው በጅምላ የሚያልቅበት ሁኔታ አለ፤ ሞተዋል። ከአሜሪካ በላይ የደህንነት ተቋም ከአሜሪካ በላይ ወታደር፤ ከአሜሪካ በላይ ፖሊስ ያለው አገር የለም። እኛ ለወደፊት እንገነባ ይሆናል ለወደፊት ፤ አሁን ግን የለንም። ግጭት የሚባል ግድያ የሚባል መሰማት የለበትም (የምትሉ ሰዎች) ቢታሰብበት ጥሩ ነው።” 

”እኔ የኢትዮጵያ ጠቅላይሚኒሰትር ሆኜ የማገኘው ደሞዝ በወር $400.00 ምናምን ዶላር (አራት መቶ ምናምን ዶላር) ነው እምበላው። እንደምታውቁት አልሰርቅም፤ ይኼ ሁሉ የሰፈር ጣጣ ለመስማት ግዴታ የለብኝም!” (አብይ አሕመድ)

እያለ።

 

እኔ የቀበሌ፤የወረዳ፤የገበሬዎች፤የመፈናቀል የግድያ፤ የፍትሕ መጓደል ግፍ እና አቤቱታ የመስማት ግዴታ የለብኝም፤ደሞዜ ትንሽ ነው፤ ሞትን ለምንድነው የምታካብዱት፤ የዘር ጭፍጨፋ (በራሱ ቃል “ግጭት”) ሲፈጸም ለምንድ ነው የምታጋንኑት፤የምትጮኹት፡ “ግጭት የሚባል ግድያ የሚባል መሰማት የለበትም የሚለው ‘ቢታሰብበት ጥሩ’ ነው።”  እያለ በኢትዮጰያዊያን ህይወት ሲያሾፍ። ታማኝ በየነ ግን ወያኔዎች ጋር ሲደርስ “ለምን ሰው ትገድላላችሁ? ተብለው ወያኔዎች ሲጠየቁ “አድማ እንዴት እንደሚያዝ የሰለጠነ ፖሊስ የለንም፤ የዲሞክራሲ ሂደትና ጀማሪዎች ነን” ሲል መለስ ዜናዊ የተናገረውን ንግግር ታማኝ አምርሮ ሲቃወም ነበር። ዛሬ በአብይ ንግግር ግን ምንም አልተገረመም። ምክንያቱም “ሂደት ነው’ እና ‘ሚራክል’ አንጠብቅም” “ታገሱት” ብሎ ነግሮናል።

 

 ይህ እጅግ አስገራሚ ነው። “ታማኝ በየነ” እሳቸው አይደሉም ከሥር ያሉ አላሰራም ስላሉዋቸው ነው” እያለ ሲከላከል ስንሰማ ለዚህ መልስ እንዲሰጥበት እኔም ሆንኩኝ ቴድሮስ ጸጋየ (ርዕዮት ሚዲያ) ይህንን ከዛሬ የአብይ ተግባርና ንግግር ጋር በማነጻጻር እንዲያብራራ ድጋሚ እንጠይቀዋለን።

ለውጥ ከመምጣቱ ጥቂት አመታት በፊት” ኦሮሞ እና ሌሎቹ ኢትዮጵያዊያንን’ አሰባስበናል ተብሎ በተዘጋጀ በአንድ መድረክ ሲናገር ታማኝ አውዲዮና ቪዲዮ በመጠቀም አዳራሹን ሲያስረዳ ምን ሲል እንደነበር ላስደምጣችሁ።

 “የሚገርማችሁ ወያኔዎች ለምንድ ነው ሰው የመትገድሉ? ተብለው ሲጠየቁ ፤ ብዙ ጊዜ የሚሉት “እኛ እኮ ዲሞክራሲ አልደረስንም ፤ዲሞክራሲ ሂደት ነው (ዲሞክራሲ ደግሞ “ፕሮሰስ ነው” “አሜሪካ እኮ 200 አመትዋ ነው” እኛ እኮ ከጀመርነው ገና ሃያ/20/ አመታችን ነው” እያሉ የሰውን ክብርና ህይወት እየቀጠፉ ለሰው ልጅ ህይወት ከበሬታ የላቸውም።’’ በማለት ወያኔዎችን በሰፊው በመተቸት ‘የወያኔ ነብሰገዳይ ፖሊሶች እና የፍትሕ መዋቅሮች.’ ለምን ዜጎችን ያለፍረድ ሰው ይገድላሉ እያለ ሲተች ነበር። ለዚህም መለስ ዜናዊ “ሃርድ ቶክ” በሚባለው የበቢሲ ፕሮግራም ቃለ መጠይቅ ተደርጎለት “ሰላማዊ አመጸኞች (በቅንጅት ጊዜ) ሁለት መቶ የሚያክሉ ወጣቶች በፖሊስ ጥይት ሲገደሉ ለምን እንዲህ ሆነ ተብሎ ሲጠየቅ መለስ ዜናዊ “የሰለጠነ አድማ በታኝ ስለሌለን ነው፤ዲሞክራሲ ገና አልተለማመድነውም………./…ወዘተ” እያለ የሰጠውን የመለስ ዜናዊ ቃለ ምልልስ ታማኝ ለተሰብሳቢ ሲያስደምጥ ነበር። 

ያንን በተጻራሪ ለማሳየት ድግሞ ‘ታማኝ በየነ’ “ሰውን ላለመግደል መሰልጠን አያስፈልግም ሰው መሆን ባቻ ነው የሚያስፈልገው” በማለት “ባራክ ኦባማ” አሜሪካ ውስጥ ስለ ህጻናት/ወጣቶች/ (የትምህርት ቤት መገዳደል ይመስለኛል) ግዲያ/ በተመለከተ ባንድ ወቅት ‘እንባው እያቀረረ’ የተናገረውን የቪዲዮ ምስል ለአድመጮቹ ካስደመጣቸው በሗላ እንዲህ ይላል ታማኝ፤

”እኚህ ሰውየ ያስለቀሳቸው የዲሞክራሲ ዕውቀት አይደለም። ሰው የመሆናቸው ጉዳይ ነው።” ሲል ታማኝ ቪዲየውን ካብራራ በሗላ፤ አሜሪካን እና ኢትዮጵያ ወያኔ ባለሥልጣናትን ሲያነጻጽር የወያኔ የኦሮሞ ፖሊስ ቃል አቀባይ (?) በኦሮሞ ወጣቶች ላይ ኦሮሞ ፖሊስ የፈጸመው ጭፍጨፋ ሓላፊነት ላለመውሰድና ሓዘኔታ ባለማሳየት ባለሥልጣኑ የተናገረውን እንዲህ ሲል በቪዲዮ አዳራሹን እንዲያደምጡት ታማኝ ይጋብዛቸዋ፤

የወያኔ ባለሥልጣን ንግግር፤

 

“ከፍተኛ ሰብአዊና ቁሳዊ ውድመት እንዲደርስ የወጠኑት ያደራጁትን ሁውከት እጅግ በጣም በሕዝብ ፍቅር በተስተዋለበት መልኩ ፖሊሶቻችን እየተደበደቡም እየተተኮሰባቸውም የአካልና የሕይወት መስዋእት እየከፈሉ ሕዝቡን ለመታደግ ያሳዩት ርብርብ ፤ በእርግጥም የፀጥታ ሃይሎቻችን ከሕዝብ የወጡ በጽናት ለሕዝብ ሰላምና ለሕዝብ ደህንነት በጽናት የቆሙ በተጨባጭ ያስመሰከረ አፈጻጸም ነው የነበረው ብሎ ማለት ይቻላል።”

 በማለት ጨፍጫፊዎች የተሞገሱበት ዘመን እንደነበር ታማኝ አምርሮ ሲቃወም እናውቃለን።

 

ዛሬ ልክ እንደ ቅንጅቱ ጊዜ እና ልክ ኦሮሚያ በተባለው ክልል ኦሮሞዎች በገፍ ሲጨፈጨፉ በባሰ መልኩ ዛሬ አማራዎች፤ጋሞዎች እና አዲስ አበቤዎች በሺዎቹ በጭነት መኪና ተጭነው ወደ ደዴሳ እስር ተወስደው ሲሰቃዩ፤ ጋሞዎች በቡራዩ ሲጨፈጨፉ አማራዎች ኦሮሞ በሚባለው ክልል ለ3 አመት ያለ ማቋረጥ በየቀኑ ሲገደሉ፤ ይባስ ብሎ ሰው ተገድሎ  የሰው ስጋ ሲበላ “አብይ አሕመድ” ባልዴራስ ጋር ጦርነት እነገባለን ብሎ ዝቶ እስክንድር እና ጓዶቹ እንዲሁም ሌሎች ታጋዮች ሲያስር ሕክምና እንዳያገኙ ሞት ሲፈርድባቸው አብይ አሕመድ እንኳን ዜጎች ተጨፍጭፈው እንደ ኦባማ ሊያለቅስ ቀርቶ ጭራሽኑ “እኔ የኢትዮጵያ ጠቅላይሚኒሰትር ሆኜ የማገኘው ደሞዝ በወር $400.00 ምናምን ዶላር (አራት መቶ ምናምን ዶላር) ነው እምበላው።  ይኼ ሁሉ የሰፈር ጣጣ ለመስማት ግዴታ የለብኝም!” የምትከፍሉኝ ደሞዝ “ትንሽ ነች” እያለ ሲያሾፍ ታማኝ አልሰቀጠጠውም።    

ያውም ይባስ ብሎ፤ “ገና ከዚህ በባሰ ሰው ያልቃል ፤ ከዚያ በሗላ ይረግባል” እያለ የዘር ጭፍጨፋ እንሚቀጥል ሳያፍር ሳይፈራ ሲናገር ፤ “ሞትን ለምንድ ነው የምታካብዱት፤ የዘር ጭፍጨፋ (በራሱ ቃል “ግጭት”) ሲፈጸም ለምንድ ነው የምታጋንኑት፤የምትጮኹት፡ “ግጭት የሚባል ግድያ የሚባል መሰማት፤መታየት የለበትም የመትሉ ሰዎች ‘ቢታሰብበት ጥሩ’ ነው።” በማለት ግድያና ጭፍጫፋ መቀጠል አንዳለበት እንጂ መቆም እንዳለበት አትናገሩ

 ብሎ ሲል ታማኝ አብይን ለምን ብሎ አልጠየቀውም። ይባስ በሎ “ሂደት ነው፤ሚራክል አንጠብቅም እያለ ለአብይ የገባበለትን አገልግሎት ቃል ኪዳን እየፈጸመ ነው። ያውም አምና ዋሺንግተን ሰላማዊ ስልፍ ተገኝቶ ሰልፈኛውን በድምፅ ማጉያ ብግልጽ እንደተናገረው “ከዚህ ወዲያ እኔ ሰላማዊ ሰልፍ ውስጥ አታዩኝም” በማለት መስመሩን ግልጽ ማድረጉንና ሲታወቅበት ከነበረው ሰላማዊ ተቃውሞው መራቁን አትርሱ። የመራቁ ወቅት አሰቃቂ የዘር ጭፍጨፋ እየተካሄደ ባለበት በዛሬው ወቅት ነው። ሥርኣቱ አማራና ጋሞ እንዲሁም ሌሎችን ያፈናቅላል፤ ይገድላል “ታማኝ  በየነ” ደግሞ “ምግብ ለተፈናቀሉት ያቀርባል።” ይኼ መሰረታዊውን ችግር አይፈታም።

በመጨረሻም ፕሮፌሰር አል ማርያም እና ታማኝ በየነ የሚከተሉትን ጠ/ሚኒስትራቸውን አብይ አሕመድን ከነርሱ ጋር ሆነን እንድንደግፍላቸው ለሕዝብ ያስተላለፉትን የጋራ ጥሪ አስነብቤ 2ኘውን ክፍል በዚህ ልቋጭና፡- ለሚቀጥለው ክፍል 3 የምተችበትን የአብይ ደጋፊዎች ታማኝ በየነ እና ፕሮፌሰር አል ማርያም እንዲህ የሚለው የጋራ ጥሪያቸውን በቅንፍ ገልጬ ልሰናበታችሁ

 

ጥሪ

 

“ታማኝ በየነ እና እኔ ……………………………. እውነታውን ለመናገር በምናደርገው ጥረት እንድተቀላቀሉን ለሁሉም ኢትዮጵያውያን የሰብአዊ መብት ወትዋቾች/አክቲቪስቶች፣ ምሁራን እና ፕሮፌሽናል ባለሞያዎች ጥሪያችንን እናቀርባለን፡፡” በማለት የአብይ አሕመድ ደጋፊዎች እንድንሆን ያደረጉልንን ጥሪ በክፍል 3 እየበለትን እንመለከታቸዋለን። ያ ጥሪ አብይ ሥልጣን ከወጣ 6 ወር በሆነበት ወቅት ነው። በዚያ ወቅት ብዙ አዲስ አበቤ ወጣት የታሰረበት፤ መንግሥታዊና በነገድ ድርጅቶች/በነገድ ልሂቃን የተፈጸሙ ወንጀሎች የተካነወኑባቸው ወቅት ነው። ይንን ጥሪና ወቅቱን እንመለከታለን። አል እና ታማኝ ዛሬም ቃል ኪዳናቸው ለአብይ እንደቀጠሉ ነው።

ክፍል 4 መደምደሚያ ላይ ግን አማራ እና ታማኝ በሚል ርዕስ እንመለከታለን።

 እኔ ጨርሻለሁ፤ “ሼር” በማድርግ ሕዝቡ መረጃ አንዲኖሮው የማድረግ ሓላፊነት ለናንተው እሀቶቼና ወንድሞቼ ትቼዋለሁ፡ አመሰግናለሁ።

ክፍል 3 …………ይቀጥላል

ጌታቸው ረዳ

Ethio Semay