Wednesday, December 4, 2019

የዓረናው አብርሃ ደስታ አቋም እስኪ እንፈትሸው ከጌታቸው ረዳ ኢትዮ ሰማይ Ethio Semay ሕዳር 25/2012 (12/04/19)


የዓረናው አብርሃ ደስታ አቋም እስኪ እንፈትሸው
ከጌታቸው ረዳ
ኢትዮ ሰማይ Ethio Semay
ሕዳር 25/2012 (12/04/19)
ፎቶ ጌታቸው ረዳ Ethio Semay

 ትናንት ማታ በድንገት ‘ወዲ ሻምል’ ወደ ተባለው ፌስቡክ ስጎበኝ ትግሬው የዓረና ድርጅት ሊቀመንበር አብርሃ ደስታ በሚያስቅና በሚገርም ሁኔታ እንዲህ ይላል።

“ክቡራን ጓደኞቼ ሆይ! ህወሓት በዓረና ታጋዮች ላይ የማጥላላት ዘመቻ ከፍታ የፈለገችውን ያህል ስላልተሳካላት አሁን ደግሞ ሌላ ታክቲክ ለመጠቀም መገደዷ መረጃ ደርሶኛል። ይህም በተገኘ አጋጣሚ ከዶር ዐብይ፣ ከአማራ ህዝብና ከኦሮሞ አክቲቪስቶች ጋር ማጣላት! ለዚህም (1) በሚያጣሉ ጉዳዮች ላይ ቃለመጠየቅ በማካሄድ የተዛባ መልእክት ለማስተላለፍ በመሞከር (2) "አብርሃ ደስታ ፀረ እገሌ ነው" እያሉ በማስወራት! እላችኋለሁ፥ ዶር ዐብይ "አብዮታዊ ዴሞክራሲ" የተባለ የዓፈና መሳርያ በመጣሉ ክብር ይገባዋል። ከ10 ዓመት በላይ የምታገለው አብዮታዊ ዴሞክራሲን በሌላ የተሻለ ስርዓት ለመተካት ነው። እናም ለዚች ተግባሩ ብቻ አጋጣሚ ባገኝ እሸልመው ነበር፤ የኔን ነው ያቃለለልኝ! የኦሮሞና የአማራ ህዝብም (ሌሎችም) ልክ እንደ ትግራይ ህዝብ ነው ምወዳቸው! አብሮነት ይለምልም" (መምህር አብርሃ ደስታ) ይላል።

ልጅ አብርሃ ደስታ፤ ምን ለማመላከት ነው የፈለግከው?
እውነት ነው አንተ ከኦሮሞ አክቲኦቪስቶችም ሆነ ከኦሮሞ ሕዝብ ምንም ጥላቻ የለህም። እነሱም የሚጠሉህ ምክንያት የላቸውም። መለስ ዜናዊን መርጠህ አማራ ነው ብለው ኦሮሞዎች የሚኮንንዋቸው አጼ ምኒሊክን አረመኔ ነው ብለህ ስትኮንንላቸው ነው የምትታወቀው ስለዚህ ኦሮሞዎች በምንም መልኩ አይጠልሁም። አማራው ግን እራስህ በምትሰነዝራቸው ንግግርህ  ሊጠሉህ ይችላሉ ብየ እገምታለሁ። ስለምርጫህ አንተም አክብሩልኝ ስላልከን አክብረንልሃል (ከትችት ጋር)

መጀመሪያ ነገር ከወያኔ ጋር ያጣላህ የብሔረተኞች ባሕሪያዊ ሽኩቻ እኔ ልወክል እኔ ልወክል እንጂ በመሰረታዊ መርሆ በብዙ መልኩ ለመስራት በየአደራሹ አብራችሁ ስታቦኩ ነበር። ስለ ወልቃይት አቋምህም ሆነ ስለ በቋንቋ መስተዳደር ከወያኔ ጋር ምንም የሚለይህ ነገር የለም ።

ስለ ወልቃይት እንደውም የባሰውን የነሱ አጫፋሪ ሆነህ “መሬቱ በጉልበት ከተነጠቀው ወልቃይቴው ጋር ጦርነት እንገጥማለን ብለሃል” ይህንን ቆይቼ አቀርበዋለሁ። ስለዚህ “ይህም በተገኘ አጋጣሚ ከዶር ዐብይ፣ ከአማራ ህዝብና ከኦሮሞ አክቲቪስቶች ጋር ማጣላት!” ለምትለው አብይ በምንም ትአምር ሊጠላህ አይችልም። ምክንያቱም አንደምትወደውና እንደምታደንቀው እንሚያሻግርህም ስለሚያወቅ። ለዚያም ነው “አጋጣሚ ባገኝ እሸልመው ነበር” ብለህ ምኞትህን የምትነግረን። ለዚህ ነበር ያንተን ስም እያሞካሸ ባልደራሱን ጦርነት ውስጥ እንገባለን ብሎ ያወጀባቸው።

እስኪ ከ10 አመት በላይ አብዮታዊ ዲሞክራሲ ታግያለሁ የምትለውን ትግልህን እንፈትሽ፡
በሊቀመንበርነት የምትመራው ድርጅትህ ለዓረና ሦስት ጥያቄዎች እንደቀረቡና መግለጫ እንደሰጠህበት ሰነዶች ተመልከቻለሁ። ለድርጅትህ ለዓረና የቀርቡት ጥያቄዎች መልስ እንደሰጠህ እራሰህ የሰነድከው ማስረጃ አለ። ለምሳሌ ሁሉም የኢትዮጵያ መሬት ነው ስትሉ አልነበረምንዴ? አሁን ምን ተገኘ? ብለው ለጠየቁ ጠያቂዎች ስትመልስ ባጭሩ የሚከተለው ነበር።
1)    መጀመሪያ ስለ ክልል አወቃቀር ያለህን ፍቅር በእንዲህ ትገልጸዋለህ (የድርጅትህም አቋም)
ዓረና ክልሎች በጂኦግራፊ መሰረት መካለል አለባቸው ብሎ አያምንም። ከአንድነት ፓርቲ ጋር ያልተግባባንበት አንዱ ነጥብም ይሄ ነው። ባሁኑ ሰዓት በጂኦግራፊ የምንካለልበት ዕድል የለም። ዕድሉ የሞተው ድሮ ነው በአፄዎቹ ግዜ። ያኔ ጭቆና ባይኖር፣ ብሄር መሰረት ያደረገ አድልዎ ባይፈፀምና በእኩልነት የምንኖርባት ሀገር ብትኖረን ኖረ በ”ብሄር ጭቆና” ተወልደው በብሄር የተደራጁ ሓይሎች ባልኖሩ ነበር። በአድሏዊ አገዛዝ ምክንያት የትግራዋይነት እና የኦሮሞነት ስሜት ከዳበረ ቆይቷል። እንደ ውጤቱም አሁን በ”ብሄር” ተካለናል።” ብለሃል።፡ብብሔር ጭቆና ተወልደው ያደጉ ኦሮሞዎችና ትግሬዎች መሆናቸውን ገልጸሃል። ጥያቄው ግን ጨቋኝ ብሔር የተነበረው ማን ነው? የሚለው ልትመልስ ይገባል።

“2, ….መሬት ለክልል ወይ ግለሰብ መሰጠቱ ኢትዮጵያዊነቱ አይለቅም።”

 እንዲያ ከሆነ “መሬት ለክልል ወይ ለግለሰብ መስጠቱ ኢትዮጵያዊ መሬት መሆኑን አሁን ባለበት አሰራርም ሆነ አንተ በምትከተለው የወደፊት ክልል አደረጃጀት እምነትህ መሬት ለክልል ሲሰጥ ኢትዮጵያዊነቱን የሚለቅበት ሁኔታ አለ። ባለቤተነቱ ለክልሉ ቋንቋ ተናጋሪ በባለቤትነት ስለሚሰጥ ከሌላ ክልል ለሚመጣ ወይንም በዛው ያለተወለደ ግለሰብ “በክልላዊ ሕግ የዜግነት ነጠቃ ይካሄድበታል” ማለት ነው። ተካሂዶበታልም። ይህም አንተም አትስተውም። ኢትዮጵያዊ የሚሆነው ግን አንተ በምተቃወመው “ጂኦግራፊያዊ አስተዳደር”  ቢሆን ይመረጣል። ከድምበር ባሻገር ዘልሎ መሬት ልጠቀም ብሎ  ለሚቃጣ ውጫዊው/ባዕዳዊ/ አገር ከሆነ ብቻ ነው  ‘የኢትዮጵያ’ ሉኣላዊ መሬት ነውና እንዲለቅ አይፈቅድም የሚባለው።

አንተ አማራጭ የለንም የምትለው ይህ የምታወድሰው የክልል አስተዳደር (ቋንቋ መሰረት ያደረገ) አንተ ስለ ወልቃይት፤ጠገዴ፤ጠለምት እና ሑመራ መሬት ያለህን የድርጅትህና ያንተን አቋም ይወስደናል ማለት ነው። ሰለ ወልቃይት ያለህን አቋም እንዲህ ትላለህ፡-ፌስ ቡክህ ላይ የለጠፍከው መረጃ።

“በዚህ መሠረት ከአንድ ክልል ወደ ሌላ ክልል የሚወሰድ (የሚቆረስ) መሬት (አንድ ሜትርም ይሁን) ከቶ መኖር የለበትም። ወደፊትም አይኖርም። በክልል መሬት ላይ ድርድር የለም። ስለዚህ መግለጫ ማውጣታችን ተገቢ ነው።” ስትል በድርጅቱ መግለጫ ትክክለኛነት አቋምህ ገልጸሃል።

አንተ እየነገርከን የለኸው ከወያኔ ጋር በዚህ አቋም አንደማትለዩ ነው። ለዚህ ነው ከላይ ከወያኔ ጋር የሚያቃቅር መሰረታዊ እምነት የላችሁም ያልኩት።

 “በህወሓት አገዛዝ ባለፉት 28 ዓመታት ትግሬ ከልሆንህ መኖር አትችልም ተብሎ ከርስቱ ሲነቀል የኖሮው የወልቃይት ፤ጠገዴ፤ጠለምትና ሁመራ ነባር ሕዝብ የአማራ ተወላጅነት ያለው መሆኑን የሚያጠራጥር እንዳይደለ ተመራማሪው ወዳጄ አቻምየለህ ታምሩ የወልቃይት ጉዳይ’ በሚለው አዲስ መጽሐፍ በሰፊው ከነ በቂ ማስረጃ በላይ ከዘመነ አክሱም ጀምሮ ያለውን ቁርኝትና ታሪክ አብራርቶታል። አንተ በወያኔ በፈጠራ ትርክት ተሞረኩዘህ ““በዚህ መሠረት ከአንድ ክልል ወደ ሌላ ክልል የሚወሰድ (የሚቆረስ) መሬት (አንድ ሜትርም ይሁን) ከቶ መኖር የለበትም። ወደፊትም አይኖርም። በክልል መሬት ላይ ድርድር የለም።” ትላለህ። በዚህ አባበልህ አንተ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር (ምናልባትም ሪፑብሊክ ትግራይ ድንገት ስትሆን) ‘የሚወሰድ፤ የሚቆረስ (አንዲት ሜትርም ትሁን) ከቶ አይኖርም ስትል ወያኔ የቀጠለበትን የዘር ማጽዳት ዘመቻ በአማራው ወልቃይት ላይ እንደማታካሂድ እርግጠኛ መሆን አይቻልም። ማስረጃውን ባንተው አንደበት ይኸው።

በግልጽ ያወጅከውን ልጥቀስ፡

“"ከአማራ ብሄርተኞች ጋር ያልተግባባሁበት ነጥብ የወልቃይት ጉዳይ ነው። ከእስር ልፈታ አከባቢ “የወልቃይት ጥያቄ” መነሳቱ ነገሩኝ። የግዛት መስፋፋት ጥያቄ እንደማያዛልቅ ነገርኳቸው። አልተግባባንም። ወልቃይትን የጦር ሜዳ ከማድረግ የዘለለ ነገር እንደማይኖረው ነግርያቸው ተለያየን። የሀገር አንድነት ይቀድማል ከሚል እሳቤ እና ይታረሚሉ ከሚል ተስፋ በትዕግስት ለማለፍ ሞኮርኩኝ። ጠቅላይ ሚኒስተር ዶር አብይ አሕመድ ከባህርዳር ሰዎች ጋር ሲነጋገር የተነሱ ጥያቄዎች ስሰማ ተገረምኩኝ። አሁን ደግሞ ጋዘጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ጎንደር ሂዶ “ወልቃይት እንደ ካሽሚር” በሚል ርእስ የአማራ አክቲቪስቶች ትግል የነፃነት ሳይሆን የግዛት ማስፋፋት እንደሆነ በግልፅ ቋንቋ አስረድቷል። ዓላማቸው ወልቃይትን የጦር አውድማ በማድረግ ትግራይን ማዳከም ነው። እኔም እላለሁ፡ ወልቃይትን የጦር ሜዳ ማድረግ ይቻል ይሆናል፤ ወልቃይት መውሰድ ግን ከቶ አይቻልም።  የየትኛውም ህዝብ የነፃነት ጥያቄ እደግፋለሁ፤ የግዛት ማስፋፋት ጥያቄ ግን አናስተናግድም። ኢትዮጵያ Plan B ያስፈልጋታል። ትግራዋይ ሕበር ተወደብ! It is so!!! ) Abereha Dseta facebook)

በማለት ትግራዋይ ሕበር ተወደብ “ትግራዋይ ተባበር፤ተደራጅ!” በማለት ግልጽ የወደፊት ዕቅድህ  ስለወልወቃይት ምን እንደሆነ ግልጽ አድርገሃል።


በዚህ አባባልህ የደነገጠውና የተገረመው የቅርብ ወዳጄ ብርቅየው ብዕረተኛ ዳግማዊ ጉዱ ካሳ ትንሹ መለስ ዜናዊ በማለት አስተሳሰብህን አምከኖታል። ከሰፊው ጽሑፉ ትንሽ ቀንጭቤ ላስነብባችሁ፡

ልጥቀስ፡
ትንሹን መለስ ዜናዊ እንተዋወቅ (ዳግማዊ ጉዱ ካሣ)

"....ከመረጃ መራቅ ምንኛ ዓለም ነው ግን? አትሰማ አትለማ ዝም ብለህ ትኖራለህ፡፡ ያንንም ይህንንም ልክፈት ካልክ ግን ስትበግን መዋልና ማደርህ ነው – ለክ እንደኔ፡፡ የተኙ እንዴት ያስቀናሉ? ከርሳቸውን ከመሙላት ባለፈ ስለሀገር የማይሞቃቸው የማይበርዳቸው ድንዙዛን እንዴት የታደሉ ናቸው! ኬሬዳሽ! እጅግ ከመናደዴ የተነሣ ሌሊቱ ነግቶልኝ ይህችን ማስታወሻ እስክጽፍ ቸኮልሁ፡፡


ወዳጄ ጉዱ ካሳ “ጉድ ያለው ገንፎ አድሮ ይፋጃል” – አብርሃ ደስታ” የመለስ ዜናዊን ሌጌሲ አስቀጣይ ወጣቱ -አብርሃ ደስታ” አንድ ሰምንት የሚሆኔ አበርሃ ደስታን የሚተቹ ምሳሌዎችና ስንኞች ከተጠቀመ በላ ዓረናና ህወሓት እኔ ከማላውቃቸው መለስተኛ ልዩነቶች ባሻገር በዋና ዋና ዓላማዎች ይህ ነው የሚባል ልዩነት እንደሌላቸው ተገንዝቤያለሁ፡፡ ስለሆነም አረና ቁጥር ሁለት ካስፈለገም ሦስት ህወሓት ሊሆን ነው – በኔ ዕይታና ግንዛቤ፡፡ ገና የተረገዙ ችግሮች አሉ ማለት ነው፡፡ በማለት ትችቱን እያሰፋ  በመቀጠል ብዕረተኛው ጉዱ ካሰ እንዲህ ይላል፦

የትግራይ ሕዝብ በቁጥርና በጊዜ ቅደም ተከተል በሚለያዩ “ሕወሓቶች” እየተመራ ይቀጥላል ወይንስ አይቀጥልም የሚለውን የራሴን ጥያቄ ጊዜ እንደሚመልስልኝ አልጠራጠርም፡፡ ለአሁኑ ግን አብርሃ ደስታ የህወሓት የወጣት ክንፍ ወካይና ዓላማውን አስፈጻሚ መሆኑን መረዳቴን ገልጬ ከዚህ በታች ከተቀመጠው የወጣቱ ፖለቲከኛ የዳግማዊም ይባል የሣልሣዊ ሕወሓት አባል አቋም ጋር እንዲታይልኝ እፈልጋለሁ፡፡ አዎ፣ አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ነው ያለነው፡፡ በፖለቲካ የሚናቅ ነገር የለም፡፡ የዛሬ ትንሽ የነገ ትልቅ ነውና!

ተመልከቱት ይህን “ጩጬ” አምባገነን! ታዲያ መለስ ዜናዊ ሞቷል አልሞተም? በጭራሽ አልሞተም! ይህ ወጣት ትግራዋይ አንድ ትልቅ ፓርቲ እየመራ ይህን የመሰለ አቋም የሚያራምድ ከሆነ ሌላውና ከርሱ በታች ያለው ታዳጊ ክፍልማ እንዴቱን ያህል በሕወሓት ስብከት አይመረዝ? የዩንቨርስቲ ምሁሩ በተቀማ መሬትና በተዘረፈ ሀብትና ንብረት እንዲህ በስሜት ከራዠና ከተወራጨ ማይሙማ ከርሱ እንዴት አይብስ?

“ተጋሩ ተባበሩ፤ ተደራጁ፤ ነገሩ እንዲህ ነው” የሚያስብል ምንም ነገር የለም፡፡ አብርሃ ወደ ኅሊናው እንዲመለስ እመክረዋለሁ፡፡ ትግራይ ህወሓት የደገሰላት ይበቃታል፤ በመጀመሪያ እርሱን ትወጣው፡፡ “በፋሲካ የተቀጠረች የቤት ሠራተኛ ሁል ጊዜ ፋሲካ ይመስላታል” እንዲሉ አብርሃ ለወግ ለማዕረግ በደረሰበት ዕድሜው የሚያያት ትግራይ እንዳለች ትቀጥላለች ማለት እንዳልሆነ አብርሃ ብቻ ሣይሆን ሁሉም ሊረዳው ይገባል – በእግረ መንገድ የነገሮችንና የሁኔታዎችን መለዋወጥ ተፈጥሯዊ ባሕርይ ለመጠቆም እንጂ ይህ በፍጹም ማስፈራራት አይደለም፡፡ የእውነትን መንገድ ብቻ ከተከተልን ግን ኢትዮጵያ የኢትዮጵያውያን ሁሉ ናት! በቃ፡፡ በብጫቂ መሬት የክት ጠባያችንን አናሳይ፡፡ ወጣቱ ትውልድ በተለይ የኣባቶቹን ስህተት ማረም ይገባዋል እንጂ ማባባስ የለበትም፡፡ አብርሃ አይዞህ – ወያኔ ቢወድቅ ሁመራ ላይ ቤትህን ሠርተህ የጥጥ አዝመራህን እያዘመርህ በአባትህ ስም በደስታ ትኖራለህ፡፡ አትስጋ፡፡ አሁን ግን ይህን የሳይከካ ተቦካ ዛቻና መስፈራርቾህን ተወው፡፡ እሳት ላይ የተጣደ ድስት በጭስ አይደነግጥም፡፡ አማራው ለመብቱ እየታገለ ባለበት በአሁኑ ወቅት አንተም መንከራ ልትጨምርለት “አለሁ!” ማለትህ ከትዝብት ውጪ ምንም አያስገኝልህም፡፡" ሲል ትችቱን በሚገርም ብዕሩ የአብርሃ ደስታ ጩጬነትና ትንሹ መለስ ዜናዊነት አብራርቶልናል።።
አመሰግናለሁ
ጌታቸው ረዳ 
ኢትዮ ሰማይ-Ethio Semay