Saturday, August 26, 2017

ዝምታ ሁሉ እንደማስማማት አለመቆጠሩን ለመግለጽ ስል ብቻ?…

Note- from the Editor:
As Ethio Semay repeatedly challenged and exposed the Oromo movement inside or outside Ethiopia, you can see from the so called 'Kero' (Oromo youth) movement an organization made to destroy the speedy revolt of the Ethiopian people. It is premature, mercenary orchestrated by TPLF itself and some extremist Islamist Oromo leaders in the Diaspora(USA and Europe) in order to drag the speed of the revolution and create confusions among Ethiopian society. This organization is nothing but nihilist movement. Therefor, such organization is a branch for the nihilist and fascist OLF, therefore, Ethiopians need to isolate such organization and labeled it as OLF. These group are simply outdated and fascistic in nature.


ዝምታ ሁሉ እንደማስማማት አለመቆጠሩን ለመግለጽ ስል ብቻ?

                                                          ነፃነት ዘለቀ (netsanetz28@gmail.com)



ይህን አጭር ማስታወሻ የምጽፈው በርዕሴ ለመጠቆም እንደሞከርኩት አንድን የተነገረ ወይ የተጻፈ ነገር በዝምታ ብቻ ታዝቦ ማለፍ ስምምነትን እንደመግለጽ የሚቆጠር እንዳልሆነ ለማስገንዘብ ስል ብቻ ነው፡፡እንጂ ሰዎች ባበዱና በሰከሩ ቁጥር ብዕር እናንሳ ብንል በቀን ውስጥ ያለው 24ቱ ሰዓትም  በጭራሽ አይበቃንም፡፡ ይሄ የተለከፈ ዘመን ደግሞ በየቀኑ የማያሰማንና የማያሳየን ነገር ባለመኖሩ ብዙው ነገር አስገራሚና አስደንጋጭም እየሆነ መጥቷል፤ በሁሉም ረገድ - በሃይማኖቱም በፖለቲካውም፣ በማኅበራዊ ሕይወቱም… በእያንዳንዱ የሕይወት መስመር የምንሰማውና የምንታዘበው ነገር ሁሉ በአብዛኛው አስፈሪ ነው፤ የምንጽናናበት ነገር እየቀነሰ የምንደነግጥበት ነገር ደግሞ እየበዛ የመሄዱ ምሥጢር አልገለጥ ብሎናል፡፡ ስለዚህም በያለንበት ባማርኛው ትርጉሙ “ጉድ!” እያልን መጨረሻውን መጠበቅን የመረጥን በርካታ ዜጎች አለን - ባገር ቤትም በውጪው ዓለምም፡፡ ጊዜ ያመጣውን ጊዜ እስኪሽረው አንድ ተገን ይዞ ፈጣሪንና የታሪክ ፍርድን በተስፋ መጠባበቅ ደግሞ የነበረና ያለ ምናልባትም ወደፊትም የሚኖር ነው፡፡ እናም ያበዳችሁና በዘመን ድፍርስ የእንክርዳድ ጠላ የሰከራችሁ ወንድም እህቶቻችን አቅል አጥታችሁ የምትናገሩትንና የምታደርጉትን ሁሉ የሚታዘብና ለነገው ትውልድ የሚያደርስ ጤናማ ሰው እንደማይኖር አስባችሁ ከሆነ ተሳስታችኋል፡፡ ጥንታውያን ዕብዶች አሁን የቡና መጣጫ እንደሆኑት ሁሉ የዛሬዎቹ ዘረኞችና ልበ ሥውራን ጎጠኞችም በነገው ታሪካችን እንደጭራቅ የልጅ ማስፈራሪያ እንደምትሆኑ አሁኑኑ መረዳት አለባችሁ፡፡ የሰከረ የሚበርድበት፣ ያበደም የሚጨምትበት (ካልሞተ በቀር) ዘመን መምጣቱና የተንጨባረረ ማንነቱን በዘመን መስታወት ማየቱ አይቀርምና ጊዜ ሰጠን ብላችሁ የምትሆኑትን ያጣችሁ ወገኖች ጥጋባችሁንና ዕብሪታችሁን ልክ እንድታስይዙት የወንድምነቴን እመክራለሁ፡፡ እውነቱን ለመናገር እንደ እናንተ ለማበድ ብንፈልግ ኖሮ ከእናንተ በላይ እያበድንና እየሰከርን የፈለግነውን መሆን የሚያስችለን ዕድሉ የነበረን ብዙ ነገን ዐዋቂ ዜጎች አለን - በዘርም፣ በቋንቋም የተሟላ ወቅታዊ የመርገምት መሣሪያ እያለን በወፍ ዘራሽ አስተሳሰብ አንበከልም ብለን ግን ዳር የቆምን፣ ከዚያም ባለፈ ለነፃነት ትግሉ የበኩላችንን አስተዋፅዖ የምናደርግ ትግሬዎች፣ ኦሮሞዎች፣ ጉራጌዎችና ሌሎችም ብርቅዬ ኢትዮጵያውያን ሞልተናል - በዚህስ ወላድ በድባብ ትሂድ፡፡ ዝም ያልነው ባለታክሲዎች በመኪኖቻው ውስጥ “ከላይ ነው ትዛዙ” እንደሚሉት የማይቀር ታሪካዊ ፍርድን ከታች ብቻ ሣይሆን በዋናነት ከላይም ጭምር እየጠበቅን ስለሆነ ነው፡፡ ለመግቢያ ያህል ይህን ካልኩ ወደ ዋና ነጥቤ ላምራ፡፡


“ቄሮ በኦሮሚያ ክልል የጠራውን የአምስት ቀን አድማ ግቡን ስለመታ በሦስተኛው ቀን አቋርጫለሁ አለ/ከቄሮ የተላለፈው አስቸኳይ መግለጫ (ምንጭ  http://www.zehabesha.com/amharic/?p=79730

ከዚህ በላይ በተመለከተው ርዕስ ዘሃበሻ ላይ የተለጠፈውን ዜና ዛሬ ጧት አነበብኩ፡፡ ማለፊያ ዜና ነው፡፡ ሕዝባዊ ዐመፅ አስፈላጊ እስከሆነ ድረስ ማንም ይዘዘው፣ ከየትም ይታዘዝ ዋናው ዓላማው ነውና ሁሉም ዜጋ ሊያከብረው ሊታዘዘውም ይገባል፡፡ እናም ላለፉት ጥቂት ቀናት በአንዳንድ የሀገራችን አካባቢዎች የተካሄዱ ሕዝባዊ ዐመፆች የወያኔውን የወሮበሎች መንግሥት ማስደንገጡን ስናነብ ቆይተናልና በርግጥም የታሰበው ድል ተገኝቶ ከሆነ አድማው መቆሙ በጎ ነው፡፡ ተገኘ የተባለው ድል በርግጥም ተገኝቶ ከሆነ ደስታው የአንድ ወገን ብቻ ሳይሆን የሁሉም ነው፡፡ ይሁንና መከራን ተካፍለን እንደምንኖር ደስታንም ለመካፈል የሚያስችል የአንድነት መንፈስን ብናዳብር ጥሩ ነው፡፡

በዚህ የቄሮዎች ትዕዛዝ በተባለለት ሕዝባዊ እንቅስቃሴ ውስጥ ያልገቡኝ አንዳንድ ነገሮች መኖራቸውን መደበቅ ግን አልፈልግም፡፡ ስሜቴን ሳልገልጽ ይህን ዜና በሽፍኑ ወድዶ መቀበልም ኅሊናየ አልፈቀደልኝም፡፡ የዐመፁ ዓላማ ይህን ሀገራችንን ምድራዊ ሲዖል ያደረገውን ግፈኛ፣ ዘረኛና አጋንንታዊ የማፊያ ጉጅሌ(ቡድን)  ለማስወገድ እስከሆነ ድረስ የቄሮዎች ትዕዛዝና የትዕዛዙ አፈጻጸም ሂደት የተጎጂ ወገኖችን አካታችነት በቅጡ የዳሰሰ አልመሰለኝም፡፡ በዚህ ጉዞ የትም መድረስ እንደማይቻልም መጠቆም እፈልጋለሁ፡፡ በማያዛልቅ መንገድ - ጫፉ ድፍን በሆነ ዋሻ - የመጓዝን አደገኝነት ከጅምሩ ካልተረዱ ደግሞ ውጤቱ ዜሮን በዜሮ እንደማባዛት ነው - በዜሮ ፍቅር የመለከፍ አባዜ፡፡ አንዳንድ ኹነቶች ደግሞ በዱባ ጥጋብ በሚመሰል ጊዜያዊ የድል እርካታ ዐይንን ይጋርዳሉ፤ ያኔ መጠንቀቅ ነው፡፡ በዱባ ጥጋብ የቱንም ዓይነት ዘመቻ ድል ማድረግ ቀርቶ በአጭር ርቀት ውስጥ የሚገኝን ኮረብታ መውጣት አይቻልም፡፡ አንዲት ክር አንበሣን አታስርም፤ አንዲት ጠጠርም ጋንን አትደግፍም፡፡ ዘላቂ ድል እንጂ ጊዜያዊ ድል ካንጀት አያስጨፍርም፡፡ ሦስተኛ ዐይናችንን ካልገለጥን ዞረን ዞረን ወደ ድጡ እንመለሳለን፡፡….

በነገራችን ላይ ቄሮ ሲባል ብዙዎቻችን በግልጽ በምንረዳው አገላለጽ “የጎበዝ አለቃ” ለማለት መሰለኝ፡፡ የጎበዝ አለቃ እና ቄሮ መገናኘት ካቃታቸው ወይም እንዳይገናኙ አንዳች ደንቃራ ከተፈጠረ በመሃላቸው የሆነ ወያኔዊ ንፋስ ገብቷል ማለት ነው፡፡ የወያኔን ንፋስ ሳያስወጡ ደግሞ በቄሮና በጎበዝ አለቃ ያልተጣጣመ የተናጠል የትግል ጉዞ የወያኔን ዕድሜ ማርዘም እንጂ የሕዝብን ሰቆቃ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ማስቆም አይቻልም፡፡ ህልም ነው፡፡ ዛሬ የኦሮሞ ቄሮ ይነሳና አንድ ነገር ያዛል፤ ነገ ደግሞ የአማራ የጎበዝ አለቃ ይነሳና ሌላ ነገር ያዛል፡፡ በዚህ መሀል ወያኔ ሠርግና ምላሽ ይሆንለታል፡፡ ከዚህ አንጻር እነዚህ የአማራና የኦሮሞ እንቅስቃሴዎች - እንደ ድፍረት አይቆጠርብኝና - በሕወሓት የበላይነት የሚታዘዙ አለመሆናቸውን መረዳት እስከሚያቅተኝ ድረስ እየተቸገርኩ ነኝ፡፡ ምን ላድርግ - “እባብን ያዬ በልጥ በረዬ” እንደምንለው እኮ ሆኖብኝ ነው፡፡ ቄሮዎችን የሚያሰማሩት ኃይላት ማዘዣ ጣቢያቸው አንጨቆረር መሆኑ እንዳለ ሆኖ ሕዝብን እየከፋፈሉ ድራሽዋ የጠፋችን የጋራ ነፃነት ለማስገኘት በተፈናጅራ የትግል ሥልት ማታገል ህልም እንኳን መሆን የሚያቅተው ጭልጥ ያለ ቅዠትና ቅብዥር ነው፡፡ ለነገሩ ወያኔ በሕዝባዊ ዐመፅና በሰላማዊ ትግል (ሲቪል ዲስኦቢዲየንስ) የሚወድቅ ቀላል ቡድን አይደለም፡፡ ዓለም አቀፉ የፀረ ኢትዮጵያ ኃይል ከጎኑ የተሰለፉለት ከባድ የኢትዮጵያ ጠላት በመሆኑ በሰላማዊና በተበታተነ ሕዝባዊ ተቃውሞ ሕወሓት ይወድቃል ብሎ ማሰብ በትንሹ ቂልነት ነው፡፡ ሕወሓት ልክ እንደ እስካሁኑ ሁሉንም ተቃዋሚ ተራ በተራ እንደዘንዶ ይውጣል እንጂ በመለያየትና እርስ በርስ በመነታረክ ለውጥ አናመጣም፤ ደግሞም ከተቃዋሚዎች አለመስማማትና በቃላት ጦርነት ከመጠዛጠዝ በተጓዳኝ እንኳንስ ከ14 እና ከ15 ሺህ ማይሎች በሚታዘዝ የሳይበር ጦር እዚሁ ሆነን በአካልና በቅርበት ታግለን ከጣልነውም እሰዬው ነው፡፡ አያያዛችንን እያዩ ወያኔዎች በሺዎች የሚቆጠሩ ጭብጦዎቻችንን ቀምተውናል፤ እናም በመንጌ አማርኛ ወያኔዎች ንቀውናል - ሊንቁንም ይገባል፡፡ የተናቀ ኃይል ደግሞ ሲከፋፈል የበለጠ ይናቃል፡፡ መሣቂያ መሣለቂያም ይሆናል፡፡ ጥረታችን ሁሉ በግልጽ የሚናገረው የወያኔ መሣቂያ እንደሆንን ዕድሜ ይፍታህ ለመቆየት መወሰናችንን ነው፡፡ የብዙዎቻችን ምርጫ “በተናጠል ታግለን የግል ፍላጎታችንን በሕዝብ ጫንቃ ላይ መጣል ካልቻልን ወያኔ ዕድሜ ልኩን ይግዛ!” የሚል ይመስላል፡፡ ይህ ደግሞ ባልጠጣው ላደፍርሰው ዓይነት የጥጋበኛ አውራ ዶሮ አስተሳሰብ ነው፡፡ ከዶሮነት እንውጣ!

የምቃወማቸውን አንዳንድ ነጥቦች ቀጥዬ ላስቀምጥና በርግጥም ለኢትዮጵያና ለኢትዮጵያውን የምታስቡና የምትጨነቁ ወገኖች ይህን ትግል የምታራምዱ ከሆነ ጊዜ ሳያልፍባችሁ መንገዳችሁን አስተካክሉ፤ ከወያኔያዊ ተፅኖዕም በአፋጣኝ ውጡ፡፡ እንዲህ የምለው የትግሉን ዕድሜ አታንዘላዝሉት ለማለት ፈልጌ እንጂ ሀገራችን ከነዚህ ነቀዞችና ምሥጦች ነፃ አትወጣም የሚል ተስፋ የመቁረጥ ስሜት ኖሮኝ አይደለም፡፡ አንገቱ በሠይፍ የተቀላው፣ ደረቱ በጦር የተወጋው፣ ትውልዱ በመርዝ የተበከለው የኢትዮጵያ ሕዝብ አምላኩ በሶ አልጨበጠምና በቅርብ የራሱን “መሲሆች” ይልካል ብዬ በሙሉ ልብ አምናሁ፤ ነፃነታችን የቀን ጉዳይ እንጂ እንደተሰወረ የሚቀር አይደለም፡፡ ካነበብኩት ዜና በአንድ ወይ በሌላ መልክ የመሰጠኝን ሃሳብ መጥቀሴን ልቀጥል ፡-


እናም የቄሮው የተቀናጀ አድማ ዛሬ በ3ኛው ቀን እነዚህን ግቦች መምታቱን ገምግመን ተገንዝበናል። የአድማው ኢኮኖሚያዊ ተጽዕኖ በጎረቤት ሃገር ከተሞች ጭምር ሳይቀር መታየቱን ገምግመናል። ስለሆነም የአድማው ውጤት በሶስተኛው ቀን አጥጋቢና በ5ኘው ቀን ይጠበቅ ከነበረው ውጤትም በላይ ሆኖ በመገኘቱ፤በዚሁ በ3ኛው ቀን በተደረገው ግምገማ መርሃ ግብሩን መከለስ አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቷል። (አጽንኦት የተጨመረ)

ይህን መግለጫ የጻፈና ያጻፈ ወገን ያላገናዘበው ብዙ ነገር አለ፡፡ በመጀመሪያ እንደወያኔ የስሜት ፈረስ መጋለብ የት እንደሚያደርስ አላወቀም፡፡ የጸሐፊው ዓላማ በጣም ግልጽ ነው - ‹ግልብ‹ ነው አላልኩም፡፡  የጎረቤት ሀገር የሚባለው ኬንያንና ሱዳንን በመሰሉ ከተሞች ላይ የዚህ ዐመፅ ተፅዕኖ ጥላውን አሣርፎ ቢሆን ነው፡፡ እዚህ ላይ መባል የተፈለገው በወያኔ አከላለል በአማራውና በሌሎች የሀገራችን ከተሞች ለማለት ነው፡፡ ይህ ደግሞ የአንዲት እናት ልጆች መካከል ልዩነትን ለመፍጠር ታስቦ የተቀመረ ሽል መንጣሪ  አነጋገር ነው፡፡ ይቅርታ ይደረግልኝና ይህን መግለጫ የከተበ ሰው አባይ ፀሐዬ ወይም አባይ ወልዱ አለዚያም አርከበ ዕቁባይ መሆን አለበት፡፡ በአማራና በኦሮሞ እንዲሁም በሌሎች ኢትዮጵያውያን ላይ በወያኔ አማካይት የሚወርደውን የመከራ ዶፍ የሚያውቅ ኦሮሞ ታጋይ ይህን ከፋፋይ ጽሑፍ ወደ ሚዲያ ይልካል ብዬ ማመን በበኩሌ ይከብደኛል፤ ምን ጥቅም ሊያገኝ? እርግጥ ነው - የሕዝቡን ቁስል የማይረዳ፣ በውጭ እየኖረ ከመከራና ከስቃያችን የማይጋራ ቅንጡ ዜጋ ከዚህም በላይ ሕዝብን ለመከፋፈል ቢሞክር ሌላ ዓላማ ሰንቆ ሊሆን ይችላልና ብዙም አይፈረድበትም፡፡ ለማንኛውም  እውነቱን የምታውቁ ወገኖች በአፋጣኝ ጣልቃ ግቡና ከነዚህ መሰል ቅንጦተኞች ሤራና ደባ ገላግሉን፡፡ አንዱ ሌላውን ያገለለ የግል ሩጫ ስሜትን ከመግለጽና  በግል ጥቅምና ፍላጎት ላይ ያነጣጠረ ምኞትን ከማንጸባረቅ ባለፈ ኢትዮጵያ ውስጥ ፋይዳ ያለው ነገር አያመጣም፡፡
እኔ እውነቱን ልንገራችሁ፡፡ ይህን ጽሑፍ የምትጽፉ ወይም የጻፋችሁ ወገኖች በዕድሜ ምናልባት ልጆቼ ልትሆኑ ትችላላችሁ፡፡ እናም በዕድሜ ትንሽነታችሁ ምክንያት ሊሆን ይችላል ሕዝቡን በፍጹም አታውቁትም፡፡ ሕዝቡ አሁንም አንድ ነው፡፡ የሚቁነጠነጡትና የሚረብሹት የወያኔን አብሾ ሳይወዱ በግዳቸው የተጋቱ ጥቂት ወጣቶችና ጎልማሣዎች ናቸው፤ ከእውነቱ ብዙ በመራቃቸውና በሚጥበረብር የራሳቸው ዓለም ውስጥ የሚኖሩ በመሆናቸው እነሱም ያሳዝናሉ - ከመርገም ይልቅ ታዲያ “እግዚአብሔር ወደ አቅላቸው ይመልሳቸው” ብለን መጸለይ አለብን፡፡ ለዚህን መሰሉ ቅዠታቸው መሠረትም በርግጥ ለሕዝብ አስበውና ተጨንቀው ሳይሆን ያቺው ሥልጣንና ሥልጣን ቢይዙ የሚፋጠን የሚመስላቸው ወደ ሀብቱ የሚደረግ ጉዞ ናቸው፡፡ እንጂ መገንጠል ምን ያህል ተምኔታዊና ቅስምን ሰባሪ እንደሆነ ከቅርብ እስከ ሩቅ በሚታዩ ነባራዊ እውነታዎች ሳይገነዘቡት ቀርተው አይመስለኝም፡፡ ከዚህ ዋና የሀገራችን ራስ ምታት አንፃር በዚህ የዘር ልክፍት ያልተጠመዳችሁ  እነ ፕሮፌሰር ፍቅሬ ቶሎሣና መሰል ብርቅዬ ኢትዮጵያውያን የበኩላችሁን እንድታደርጉ ይህን አጋጣሚ በመጠቀም ማስታወስ እፈልጋለሁ፡፡


የኦሮሞ ትግል ግቡን የሚመታው ህዝቡን ራሱ በመረጣቸው መሪዎቹ አማካይነት መተዳደር ሲጀምርና ፊንፊኔን ጨምሮ ሁሉም የኦሮሚያ አካባቢዎች ከህዝቡ የወጡ በወጣ ዲሞክራሲያዊ አስተዳደር ስር ሲዋቀሩ ነው።


የኦሮሞ ትግል ግቡን የሚመታው ኢትዮጵያ በጠቅላላው ከወያኔ ናቡከደነፆራዊ አገዛዝ ነፃ ስትወጣ ነው፡፡ ከ80 በላይ የሚገመት ብሄርና ብሔረሰብ አቅፋ በያዘች ሀገር ውስጥ አማራ ወይ ኦሮሞ ነፃ ወጥቶ ሌላው ትግሉን የሚቀጥልበት ሁኔታ በፍጹም የለም፡፡ ይህን መሰሉን ወያኔያዊ አካሄድ በአፋጣኝ መለወጥ ይገባል፡፡ በምንም መንገድ እውን ስለማይሆን፡፡ እንተዋወቃለን፡፡ ኦሮሞና አማራ፣ ትግሬና ጉራጌ፣ ከምባታና ወላይታ ሁላችንም በተለይ ማታ ማታ አንድ ነን፡፡ በትዳር፣ በመሸታ ቤት፣ በሀዘንና በደስታ፣ ወዘተ. በእስካሁኑ ሁኔታ የሚነጣጥለን ያልተገኘ የእግዚአብሔር ውህዶች ነን፡፡ ከአሁን በኋላም ማንም አይነጣጥለንም - ከወያኔ ወዲያ ነጣጣይ ላሳር ነበርና በዚህ ከአሁን በኋላ ያለመነጣጠል ተፈጥሯዊ ቁርኝታችን መተማመን እንችላለን፡፡ ተስፋ መቁረጥ የሚፈልግ መብቱ ነው - እኛን መለያየት የማይቻልና ህልምም መሆኑን ተረድቶ ተስፋውን ጎማምዶ ይጣል፡፡ ቁርቁስ ደግሞ የትም አለ፤ እንኳንስ ሁለት ሰዎች የአንድ ሰው ሁለት እግሮችም እየተጣለፉ ጊዜያዊ ግርንጭት ይከሰታል፡፡ ግጭት በተፈጠረ ጊዜ ሁሉ ግን ሀገር አይገነጣጠልም፤ ሕዝብም አይበታተንም፡፡ መበታተን የሚጠቅመው ግለሰቦችን እንጂ ማኅበረሰብን እንዳልሆነ ከሩቅም ከቅርብም የዓለማችን ታሪክ ብዙ ተምረናል፡፡
ድል ለኦሮሞ  ህዝብ !
ኦሮሞ  ቄሮ
የኦሮሞ ሕዝብ ከኢትዮጵያ ሕዝብ አይነጠልም፤ ኦሮሞ ከኢትዮጵያ ፈጣሪዎች አንዱና ዋናው ግንድ ነው፡፡ ኦሮሞ ያልተቀላቀለበት የኢትዮጵያ ጎሣና ነገድ የለም፡፡ ይህን በያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ውስጥ የሰረጸ ደም ነጥሎ የተለዬ ኅልውና ለማላበስ መሞከር ደግሞ የዘፍጥረትን መጽሐፍ ለመለወጥ እንደመሞከር ያለ ጀብደኝነት ነው፡፡ በማንኛውም መሥፈርት የኦሮሞ ሕዝብ ከኢትዮጵያ ሕዝብ የተለዬ አይደለም፡፡ የዘመናዊቷ ኢትዮጵያ ዋና ገዢና አስተዳዳሪ ሆኖ እስከ ደርግ ውድቀት ድረስ የዘለቀው ኦሮሞ ከአጋሩ ሌላው የሀገራችን ሕዝብ የተለዬ ጥቅምም ሆነ ፍላጎት የለውም፡፡ ለዚህ ቅንና ሀገሩን ወዳድ ሕዝብ እውነተኛ ዴሞክራሲን እንጂ አዲስ መጥ ብሔርኝነትን በግድ ጭኖ ከወንድምና እህቶቹ ጋር ለዳግም ግጭትና ዕልቂት የሚጋብዘው መሠሪ ኃይል -  አዛኝ ቅቤ አንጓች  አያስፈልገውም፡፡ ኦሮሞው ከሌላው ወገኑ የተለዬ ድልም ሆነ ሽንፈት አጋጥሞት አያውቅም፡፡ የዘፈን ዳር ዳሩ እስክስታ ነው ይባላልና ይህን ተዋልዶና ተዋህዶ የኖረ ሕዝብ ከሌላው ጋር ቅራኔ እንዲገባ ከሚያደርግ ቅስቀሳና ስብከት እንቆጠብ፡፡ “ወጡ ሳይወጠወጥ ወስከምቢያው ቂጢጥ” እንዲሉ ሆኖ ገና ለገና የሕወሓት መንበር የተነቃነቀ ስለመሰለ ብቻ ሌላ እሳት ውስጥ የሚሞጅረንን ትልም አንከተል፡፡ ከመነሻው ወያኔ በዚህ ዓይነት የትግል ሥልት የበለጠ ሥር እየሰደደ ዘላለማዊነቱን ያጸናል እንጂ አይወድቅም፡፡ በዘር እየተደራጁ ወያኔን ለማስወገድ መሞከር ያቺን የበሬው እንትን ይወድቅልኛል ብላ እሰው በረት ደጅ ድረስ እየተጃጃለች የሄደችዋን ቀበሮ መሆን ነው፡፡ ልብ ይስጠን፡፡ ከአንታጀችን ለፈጣሪ እንጸልይ፡፡ ቀኑ ቀርቧል፤ ለቀኑ ምቹ እንሁን፡፡ ባንመች እንደ አረም ተነቅለን የምንጣለው እኛው ነን፡፡ ሳይለወጥ እንዳ የሚያረጅ ድንጋይ ብቻ ይመስለኛል፡፡ ሰው ደግሞ በሥ ተፈጥሮው ከድንጋይ በብዙ እጅ የተሸለ ነው፡፡ ጥላቻንና ቂምን ከሰውነታችን አውጥተን በፍቅር ጠበል ራሳችንን እናድስ፡፡ ክፋትን ለክፉው እንተወው፤ ለኛ ግን ደግነትንና ፍቅርን፣ መተዛዘንንና መተሳሰብን ገንዘባችን እናድርግ፡፡ ያኔ የጨለማው ኃይል ከኛ በሺዎች ኪሎ ሜትሮች ይርቃል፤ አሁንም ያኔ የፈጣሪ በረከትና ቸርነት በየደጃችን ሞልቶ ይፈሳል፡፡ በቃ፡፡
 Posted at Ethio Semay