Sunday, May 29, 2022

ኢትዮጵያ ብላ ብላ በዚህ ሰውዬ እጅ ትውደቅ? ፈጣሪን ምን ብንበድለው ይሆን? ብሥራት ደረሰ 5/29/2022 Ethiopian Semay

 

ኢትዮጵያ ብላ ብላ በዚህ ሰውዬ እጅ ትውደቅ? ፈጣሪን ምን ብንበድለው ይሆን?

ብሥራት ደረሰ

5/29/2022

Ethiopian Semay

Ethiopian Semay

የኢትዮጵያን ወቅታዊ ሁኔታ ዐይኔን ጨፍኜ ዝም ብዬ በዐይነ ኅሊናየ ስመለከት ብዙ ነገሮች እውነት እውነት አይመስሉኝም፡፡ ከሞላ ጎደል ሁሉም ነገር ትያትር ይመስለኛል፡፡ እውነት የሚመስሉኝ ሁለት ነገሮች መምሸት መንጋቱና የሰዎች በእርጅናም ይሁን በህመም ወይንም በአደጋና በሰዎች እጅ መሞት ናቸው፡፡ ጊዜው ሰዓቱን ጠብቆ ይነጉዳል - እየመሸ እየነጋ፡፡ ሰውም ከቅርብ ዘመድ ጀምሮ እስከሩቅ ትውውቅ ይታመማል፤ ይሞታል፡፡ እነዚህ ጥንት የነበሩና አሁንም ያሉ ተፈጥሯዊ ክስተቶች ናቸው፡፡ በተረፈ ኢትዮጵያ አለች የምልበት አንድም ነገር የለም፡፡ በኔ ዕድሜ እንዲህ ያለ ዝብርቅርቅ ያለ ሁኔታ ይገጥመኛል ብዬ አስቤው አላውቅም፡፡ ዕድሜ ዘልዛላው ግን ብዙ ያሣያል፡፡

በልጅነቴ የማውቃት ኢትዮጵያ አሁን ድራሹዋ ጠፍቷል፡፡ ሰው ተንቀሳቃሽ ሮቦት ከሆነ ሰነበተ፡፡ አብዛኛው ሰው አእምሮው ተቃውሶ ብቻውን እያወራ ይሄዳል፡፡ አብዛኛው ዜጋ ከመሠረታዊ የሰው ልጆች አስፈላጊ ነገሮች ተፋትቶ በቀን አንዴም መቅመስ አቅቶትና አንዴ ትከሻው ላይ ባጣበቃት አሮጌ ጃኬት ወይ ሹራብ ቢጤ ተጨብጦ በየበረንዳውና በየታዛው ተቀምጦ መዋል ማደሩን ተያይዞታል - ሌላ ምርጫ በማጣት፡፡ የመንግሥት ሥራ ለስም እንጂ በተግባር የለም፡፡ ጉቦና ሙስናው እግር አውጥቶ እየሄደ ነው፡፡ የኦሮሙማ ሰዎች በኬኛ ፖለቲካቸው ሁሉንም ካልዋጥን ካልሰለቀጥን ብለው ከአዲስ አበባ ጎንደር በተዘረጋ ማፊያዊ ሥርዓት በተለይ አማራን መቆሚያ መቀመጫ አሳጥተውታል፡፡ ከዚህም የተነሳ የአንድ ዓመት ሕጻን ሳይቀር በማገት ከጣሊያኑ ማፊያም፣ ከአልቃኢዳም፣ ከአይሲስም፣ ከአልሻባብም፣ ከቦኮሃራምም፣ ከማዕከላዊ አፍሪቃ የቀድሞ አማፅያን ቡድን ከቱዋሬግም የበለጠ የእገታ ሪከርድ አስመዝግበዋል፡፡ እኛም በሣቅ ጦሽ እያልን በ“እያነቡ እስክስክስታ” ልናልቅ ነው፡፡ እንደጥርስ ሞኝ የለም መቼም - አንገት በጎራዴና በሠይፍ ተቆርጦ እየበረረ እኮ ጥርስ ይስቃል - ልክ እንደኛ፡፡

ኢትዮጵያ መረገሟን በትክክል የተረዳሁት የሁሉም የሥነ ልቦና ህመሞች መጋዘን የሆነው አቢይ አህመድ እንዲገዛት እግዚአብሔር ፈቃደኛ ሆኖ መገኘቱን ስገነዘብ ነው፡፡ ለነገሩ ሲያንሰን ነው! እኛም አብዝተነው ነበር፡፡ የክፋታችን ብዛትና ዓይነት፣ የኃጢኣታችን ነዶና ክምር እኮ ወደር የለውም፡፡

አቢይ አህመድ ምን ዓይነት ኢትዮጵያና በምን በምን ችግሮች እየተጠበሰና እየተወገረ ያለ ሕዝብ “እንደሚመራ” እንኳንስ እኛ የመከራው ገፈት ቀማሾች መላው ዓለም ያውቀዋል፡፡ ይህ ሰው ነው እንግዲህ፣ ራሱ በባዶ እግሩ እየሄደ መንግሥት አለኝ ብሎ ለመንግሥት በከፈለው ግብርና ቀረጥ ቫጋቦንዱ አቢይ አህመድ የ49 ቢሊዮን ብር አዲስ ቤተ መንግሥት እያሠራ የሚገኘው፡፡ አንድ ሎሚ በአምስትና አሥር ብር ቸርችራ በምታገኛት ትንሽዬ ሣንቲም ነፍሷን አውላ ከምታሳድር የጉሊት ሴት በተሰበሰበ ገንዘብ 2 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር የፈጀ የማዘጋጃ ቤት ሕንጻ የታደሰው በአቢይ ዘመንና በርሱ በቅንጡው ሰውዬ ቡራኬ ነው - የመጀመሪያ ግንባታው 3 ሚሊዮን ያልፈጀ ሕንጻ ዕድሳቱ ብቻ ምን ያህል እንደፈጀ (ከነሙስናው ነው ታዲያ) ልብ በሉ - በነዚህ ሰዎች እጅ ነው የወደቀችው ሀገራችን፤ በዚህ ብቻም በተውን በስንት ጣሙ፡፡ ሕዝበ አዳም ይልሰውና ይቀምሰው አጥቶ በመቶ ሽዎች የሚቆጠር ሕዝብ በረንዳ እያደረ ለመናፈሻ ሥፍራ ማስፋፊያ በሚል ብዙ ሽህ ካሬ ሜትሮችን ከዜጎች የሚቀማው፣ ጂቡቲን የሚያህል የመሬት ስፋት እንደአሜሪካንና ፈረንሣይን የመሰሉ ኤምባሲዎች አለገደብ ተቆጣጥረው ባሉባት ሀገርና ከተማ ዜጎች 50 ካሬ ሜትር የመኖሪያ ቤት መሥሪያ ተነፍገው ከተማዋን መናፈሻ በመናፈሻ እያደረገ የሚገኘው ድሃ ጠሉ አቢይ ነው፡፡

ሀገር በጦርነትና በዜጎች መፈናቀል፣ በኦሮሙማዊ የዘረኝነት ክርፋትና ጥምባት እየታመሰች አስመሳዩ አቢይ ግን ጉዳ ጉዱን ለመሸፈን የሕንጻ ቀለም ቀይሩ በማለት ለከተማ ውበት የሚጨነቅ መሆኑን ይደሰኩራል፡፡ ይህ ባሕርይው ዲሊውዥን የሚለውን የሥነ ልቦና ደዌ ያስታውሰናል፡፡ ይህ በሽታ ነባራዊ እውነትን ከሚያጥበረብር የህልም ዓለም መለየት ካለመቻል የሚመነጭ የአእምሮ ልክፍት ነው፡፡ መጥፎነቱ ይህ ዓይነቱ ሥነ ልቦናዊ ደዌ መድሓኒት የለውም፡፡ ለነገሩ የሥነ ልቦና በሽታዎች በአብዛኛው መድሓኒት የላቸውም፡፡ የአቢይ ህመሞች ደግሞ ከብዛታቸውም የተነሣ ለመፈወስ የሚሞከሩ አይደሉም፡፡

አቢይ አህመድ ከርሱ በስተቀር የተማረ የተመራመረ ሰው ያለ አይመስለውም፡፡ እርሱ ብቻ ሁሉን አዋቂ፣ እርሱ ብቻ ዶክተር፣ እርሱ ብቻ መሃንዲስ፣ እርሱ ብቻ ፓይለት፣ እርሱ ብቻ ሾፌር፣ እርሱ ብቻ የህክምና ጠቢብ፣ እርሱ ብቻ አትክልት አጠጪ፣ እርሱ ብቻ ትራፊክ ፖሊስ፣ እርሱ ብቻ ጥሩ ባል፣ እርሱ ብቻ ቅን፣ እርሱ ብቻ ጥሩ አባት፣ ምን አለፋህ …. ከእርሱ ውጪ ማንም ቢሆን የሰውነትን የውኃ ልክ ያላሟላ መስሎ ይታየዋል፡፡ በዚህም ሳቢያ ሌላ ሰው፣ ከነጭርሱ ሰው አይመስለውም፤ እናም ይንቀዋል፤ ይሰድበዋል፤ ያንጓጥጠዋል፤ በሌሎችም ያስቅበታል፡፡ የዚህን ሰው ባሕርይ ለመረዳት የዲክቴተርን ፊልም ዋና ገጸ ባሕርይ አድሚራል ጄኔራል አላዲንን ማየት በቂ ነው፡፡ እንዲህ ያለ ጠባይ አንድን ሰው የሚጠናወተው ሰውዬው ለራሱ ካለው የተጋነነ ግምት በመነሳት ነው፡፡ ያ ዓይነቱ ጠባይ በሥነ ልቦናው መስክ ናርሲሲዝም ይባላል፡፡ የዚህ ሳይኮፓቲክ ደዌ በሌላ አገላለጽ ሜጋሎማንያ ሊባልም ይችላል፡፡ ራስን ከሁሉም አስበልጦ የማየት በሽታ በሥነ ልቦናው ዘርፍ እንዲህ ነው የሚጠራው - ሰውዬው ደግሞ ሜጋሎማንያክ፡፡

አቢይ ካልሳቁለትና ካላንቆለጳጰሱት የጠሉት ይመስለዋል፡፡ በርሱ ተወዳጅ ለመሆን በግድ ማሞካሸትና “ካላንተ ይቺ ሀገር ዋጋ የላትም” እያሉ ዘወትር ማሟሟቅ በጤና ለመኖር ወሳኝ ነው፡፡ እንደዚያ ካልሆነ ነገር የሚጎነጉኑበት ይመስለውና ወጥመድ መዘርጋት ይጀምራል፡፡ ሳያጠፋ ደግሞ አይለቅም፡፡ እየሣቀና እያሳሳቀ ገደል ይከታል፡፡ ለዚህ ማስጃው ከባህር ዳር እስከ ሸገር የሠራው የግድያ ጀብድ ምስክር ነው፡፡ ይህ ጠባዩ የፓራኖያ ተጠቂ መሆኑን ያሳያል - ሰውዬው ደግሞ ፓራኖይድ ይባላል፡፡ ምን አለፋህ - አቢይ ያልተጠቃበት የሥነ ልቦና ደዌ የለም ቢባል ምንም አልተጋነነም፡፡

አቢይ ከርሱ በምንም መንገድ የሚበልጥን ሰው አይወድም፡፡ ይህ የሰው ልጅ ተፈጥሮ ነው ሊባል ቢችልም በርሱ ግን ይከፋል፡፡ ምክንያቱም በሥራ ስኬትም ይሁን በስምና በዝና እርሱን የሚገዳደር ከሆነ አንድም ያጠፋዋል ወይንም በሹመት አሳብቦ ከፖለቲካው መድረክ ያርቀዋል፡፡ በነአምባቸውና በነአሣምነው ሁኔታ ካየነው ደግሞ ተቃዋሚውንና ተቺውን ከነጭርሱ ሊያስገድልም ይችላል፡፡ አቢይ የሚፈራው ምድራዊም ሆነ ሰማያዊ ኃይል ስለሌለ ማንም ላይ ምንም ነገር ከማድረግ አይመለስም - ሚስቱ ላይም ጭምር - አሁንም ድረስ በሚስትነት ካለች ማለቴ ነው፡፡ ሲሾ ደግሞ በጥቅሻ የሚታዘዙለትን ደናቁርትና ገና ሮጠው ያልጠገቡ ጮርቃ ሕጻናትን ነው፡፡ በነዚህ ሴቶች በሚበዙባቸው ዘረኛ ኩታራዎች እየተዳደረች ኢትዮጵያ የት እንደምትደርስ ለማየት የሚጓጓው ዜጋ ብዙ ነው፡፡   

አቢይ በ26 ወሮች የዶክትሬት ትምህርቱን እንደጨረሰ አንብቤያለሁ፡፡ እንኳን የሱን ዓይት ጥራዝ ነጠቅ ሰው ለጎበዝም ቢሆን ይህ የትምህርት ደረጃ ከአራትና አምስት ዓመታት በታች አይታሰብም፡፡ ስለዚህ የዚህ ሰው ሕይወት በዕንቆቅልሽ ስለመሞላቱ ከዚህ በላይ ማስረጃ የለም፡፡ ይገርማል፡፡

አቢይ ሲዋሽ ለነገየ አይልም፡፡ ገና ሥልጣን እንደጨበጠ በቴሌቪዥን መስኮት ቀርቦ “ሀገራችን ነዳጅ ልታወጣ ሂደቱን ጨርሳለች፡፡ በቅርቡ ምርት ይጀምራል” አለና ወስፋታችንን አንጫጫ፤ በተስፋ ዳቦም ሆዳችንን ቀበተተ፡፡ ግን የውኃ ሽታ ሆኖ ቀረ - ውሾን ያነሳ ውሾ፡፡ ትንሽ ቆይቶ ደግሞ “ኦሮሞ ከሚገባው በላይ የተለዬ ጥቅም አግኝቶ ከሆነ በ24 ሰዓታት ውስጥ ሥልጣኔን እለቃለሁ፡፡” አለና አስጨበጨበን፡፡ እውነቱ ግን ከአየር መንገድ እስከ ጎጃም መንገድ አክራሪ ኦሮሞ ሁሉን ተቆጣጥሮት ሀገሪቱ በኬኛ ፖለቲካ ስትታመስ ማየት ሆነ፡፡ ሌላው ቀርቶ አዲስ አበባ ላይ የወያኔ/ኦህዲድ/ኦነግ የይስሙላው ህገ መንግሥት ተጥሶ የኦሮሚያ መዝሙር በግዳጅ ሲዘመርና ባንዲራውም ሲሰቀል እያየን ነው - የሌሎቹ ክልሎች መዝሙርና ባንዲራም እንዲዘመርና እንዲሰቀል ብንጠይቅም የአንበሣው ተረት ነው ምላሹ - “ ‹አንበሣ ምን ይበላል?› ቢሉ ‹ተበድሮ› ‹ምን ይከፍላል?› ቢሉ ‹ማን ጠይቆ?›” ዓይነት አካሄድ ነው እየተስተዋለ ያለው ለማለት ነው፡፡ ለአንዱ ብቻ ማዳላት ነውርም ኢ-ህገ መንግሥታዊም ድፍረትም ዕብሪትም ነው፡፡ ይህ ወልጋዳና ሸፋፋ አሠራር ደግሞ “ቢያዝ ኤንድ ፕሬጀዲስ” የሚባሉትን የአቢይን ሥነ ልቦናዊ ህመሞች በግልጽ የሚጠቁም ነው፡፡

በዚህ መልክ ከሄድኩ መቼም አልጭርስም፡፡ ስለዚህ ዋና ዋና ነገሮችን ልጠቁምና ልሰናበት፡፡

አማራ ዒላማ ውስጥ ከገባ ቆዬ፡፡ አሁን የፍጻሜው ጨዋታ ላይ ይገኛል፡፡ የተሸፈነ ነገር ዝንታለሙን እንደተሸፈነ አይቀርምና የአቢይ ዓላማ ግልጽ ከወጣና የላኪዎቹን አጀንዳ እያስፈጸመ እንደሆነ አማራውም ሌላውም ተረድቷል፡፡  ጊዜው የመኸር ወቅት ነው፡፡ ጃልመሮና ጃል አቢይ በአማራው ላይ ቆርጠው ተነስተዋል፤ ደግሞም በአራዶች ቋንቋ ለመግለጽ ያህል በቀላሉ አይፋቱትም፤  ምክንያቱም ከዐውሬው ጋራ በነፍሳቸውና በደማቸው ተፈራርመዋል፤ ይህን እኔ አሳምሬ አውቃለሁ፡፡ አማራን ለማጥፋት ሲባል በሤራ ፖለቲካ ተዘፍቀው በከንቱ ሲባዝኑ የከረሙ ሁሉ ክንዳቸውን አስተባብረው መጪዋ ክረምት ሳታልፍ ይህንን ነገድና በእርሱ ትወከላለች የምትባለዋን ኢትዮጵያ ከምድረ ገጽ ለማጥፋት ተማምለዋል፤ ቤተ መንግሥቱና ታንኩና ባንኩ ብቻ ሳይሆኑ የእያንዳንዳችንን ሕይወት በመያዣነት ስለያዙ ለነሱ ይህ ተልእኮ ቀላል መስሎ ቢታያቸው አይገርምም፤ ለዚህም ነው አሁን እንደሚስተዋለው ጻፍክና ተናገርክ በሚል የመጀመሪያውና ቀላሉ የዴሞክራሲ ግብኣት የተነሣ ሁሉንም አማራ ዘብጥያ ለማውረድ የቆረጡ የሚመስሉት፡፡ በዚህ ጎራ ውስጥ ግብጽ አሜሪካ፣ አውሮፓ፣ ሕወሓትና አብዛኛው  በወያኔ ፕሮፓጋንዳ የተጠለፈ የትግራይ ሕዝብ፣ ኦነግ/ኦህዲድ፣ በገንዘብና በሆድ የተገዛው ብአዴን … ይገኙበታል፡፡ አማራ ደግሞ ጥቂት ወገኖችና ፈጣሪው ከጎኑ ተሰልፈው መጪውን ክረምት ይጋፈጣሉ፡፡ አሸናፊው ግን ከአማራው ወገን የተሰለፈው ኃይል ነው፤ በጣም ግልጽ ነው፡፡ ስለሆነም ሌሎች ጠንቀቅ ማለት አለባችሁ ማለት ነው፡፡ ይህን የምለው ለራሳችሁ ነው - ለአማራው አይደለም፡፡ አማራውማ ሁሉንም ለምዶታል፡፡ ከዚህ በላይ አልናገርም፡፡ ግን ግን ስትጣሉ ለዕርቅ በሚያመች መልኩ እንዲሆን ከአሁኑ ብዙም ሳይዘገይ አስቡበት፡፡ አሁን የምትቃዡበት ፋኖ … ለነገሩ ምን አገባኝ በዚህ፡፡

ይሄ ሰዎችን በተለይ አማሮችን የማፈን ነገር ኦነጎች ደግማችሁ ደጋግማችሁ አስቡበት፡፡ ወደፊት ሕዝብ አንድ ሆኖ ይነሳል፡፡ ያኔ የለያዩትንና ሀገሩን የበታተኑበትን ወገኖች እያሳደደ ከነዘር ማንዘራቸው ቆረጣጥሞ ይበላቸዋል፡፡ መቅኖ ያሳጡትን ለገንዘብ ያደሩ ባንዳዎችን እገቡበት ገብቶ ያንቃቸዋል፡፡ ስለሆነም ብትችሉ ሰዎችን አታፍኑ፡፡ ለአንድ ዕብድ ሥነ ልቦናዊ እርካታ ስትሉ ታሪካችሁን አትበርዙ፤ አትከልሱ፡፡ ተገድዳችሁ የምታፍኑ ካላችሁ እንኳን የምትይዟቸውን ሰዎች በአግባቡ እንደሰው ያዟቸው፡፡ አታሰቃዩዋቸው፡፡ ወያኔ ሰውን ስታሰቃይ ከርማ አሁን ምን እንደደረሰባት አስታውሱ፡፡ የዘሩትን ማጨድ አለና እባካችሁን ሰውን ስታግቱ ጥቃቄ አድርጉ፡፡ የነገ ሰው መሆን ከፈለጋችሁ ደግሞ ከዚህ አፋኝ ሥርዓት በቶሎ ተላቀቁ፡፡ በርሀብ መሞትም ካለባችሁ ሙቱ - ሰውን በማሰቃየት ከሚገኝ ሲዖላዊ የሰይጣን ገንዘብ ይልቅ በድህነትና በርሀብ መሞት የተሻለ ዘላለማዊ ዋጋ አለውና ወገኖቼ በወራት ውስጥ ዕልባት በሚያገኝ ችግር ለመክበር አትቋምጡ፡፡ እኔ ተናግሬያለሁ፤ መስማት የናንተ ድርሻ ነው፡፡

በኑሮ ውድነት ህዝብን እያሰቃያችሁ ያላችሁ ማሰብ ጀምሩ፡፡ ለሚያልፍ ቀን የማያልፍ የኅሊና ጠባሳ አታስቀምጡ፡፡ ዛሬ ትናንትን እንዳልሆነ ሁሉ ነገም ዛሬን አይሆንምና ከእንስሳነት ወጥታችሁ ሰው ሰው ለመሽተት ሞክሩ፡፡ አንተ ውስኪ ስትደፋና ጮማና ብርንዶ ስትቆርጥ አጠገብህ ያለ ድሃ በአሥር ሽህ የወር ደሞዝ መኖር አቅቶት በረንዳ ላይ እያደረ መሆኑን ተረዳ - ከርሱ የባሰውንማ ቤቱ ማለቴ በረንዳዎች ይቁጠሩት፡፡ በቃኝ  ባክህን …..