Wednesday, May 17, 2017

ጥፋቱ የማን ነው - የትግሬዎች ወይንስ የዐማሮች? ዳግማዊ ጉዱ ካሣ



ጥፋቱ የማን ነው - የትግሬዎች ወይንስ የዐማሮች?
ዳግማዊ ጉዱ ካሣ (Posted at Ethiopian Semay)

 5/17/2017
ትግራይ ረፓፕሊክ› ውስጥ ሰሞኑን የእግር ኳስ ጨዋታ በዐማራና በትግሬ መካከል ተካሂዶ እንደነበርና ትግሬዎች ዐማሮችን ሰባብረው መጣላቸው ከተሰማ ሰነበተ፤ አጀንዳ መፍጠር የማይታክታቸው ትግሬ ወያኔዎች በዚህችም እያንጫጩን ነው፡፡ “እሰይ!” አይባል ነገር ሆኖብኝ እንጂ ትግሬዎቹ ያደረጉት ነገር የማይጠበቅ አልነበረምና ጥፋቱ ሙሉ በሙሉ የዐማሮች እንደሆነ የማተቤን መመስከር እችላለሁ፡፡ የቀበጡ ለት ሞት አይገኝም፤ ፍየል ሲሰባ(ም) ሾተል ያሸታል፡፡ ወደሽ ከተደፋሽ ቢረግጡሽ አይክፋሽ፡፡ ደግሞ ተረት ለዐማራ ሊያቅት?!  በንግሊዝ አፍም ልጨምርልህ ከፈለግህ - “When its time has arrived, the prey comes to the hunter.”

 አንዲት የአህያ ውርንጭላ “እማዬ፣ እዚያ ማዶ ታለው የአያ ጅቦ አትክልት ቦታ እንግባና ትንሽ ሣር እንጋጥ” ብላ ትጠይቃታለች አሉ፡፡ እናትም “አየ ልጄ፤ እንኳንስ ሄደንበት እንዲያውም ይፈልገናል!” አለቻት ይባላል፡፡ ስለዚህ በጅብ መንደር ሄዶ “ተበላሁ፣ ተጋጋጥኩ” ማለት አዘኔታን እንደማያስገኝ ቀድሞውን መታወቅ ነበረበት፡፡ እርግጥ ነው “መፍረድ ቀላል ነው፤ ‹አትፍረድ ይፈረድብሃል›” እንዳልባል እንጂ የጅል ሥራ ነው የተሠራው፡፡ ደጅህ መጥቶ እየጨረሰህ ወደሚገኝ ያመረረ ጠላት ጓዳው ድረስ ሄደህ ለጥቃት መዳረግ ጅል ካላስባለ ጅል የሚያስብል ሌላ ነገር ሊኖር አይችልም፡፡ ግጥሙ አሁን ጠፋኝ እንጂ “… ምን ያለማምጣል ጠላት ወዳጅ ላይሆን” ምናምን የሚል ሥነ ቃላዊ ስንኝ እንዳለ አስታውሳለሁ፡፡ ለማይረባ የወያኔ ፖለቲካ ሲባል ልጆቻችን ጭዳ መሆናቸው ያሳዝናል፡፡ ይህን ያደረጉ የወያኔ አዘጥዛጭ ዐማሮችም ቀኑ ሲደርስ ዋጋቸውን እንደሚከፈሉ ማወቅ አለባቸው፡፡ ማንም የዘራውን ያጭዳል፡፡ ሞት ሲዘገይ የቀረ መምሰሉ ግን ብዙዎችን እያሞኘ ያጃጅላቸዋል፡፡ ሌሊቱ የማይነጋ እየመሰላቸው የታሪክ ቋታቸውን የሚያበለሻሹ ዜጎች እጅግ እየበዙ ነው፡፡


ብዙ ትግሬ ጠግቦ በዐማሮች ሬሣ ላይ በሚያናፋበት በዚህ የጅቦች ዘመን ሊያውም ትግሬዎች ዘንድ መቀሌ ድረስ ሄዶ ኳስ መግጠም ትርጉሙ “ሩቅ ስለሆንባችሁ እናንተን ለማስደሰት ብለን እዚሁ እግርግማችሁ መጥተንላችኋልና እንደፈለጋችሁ አድርጉን” እንደማለት ነው - ለገዳይ በማዘንና በመራራት ዐማራዊ ትህትናንና ጨዋነትን የማሣየት ጥረት መሰለኝ፡፡ አእምሮውን በተነጠቀ በርካታ ሕዝብና ወሮበላ ሽፍታ መሀል ተገኝተው ሲያበቁ የሚደርስበትን አደጋ ሁሉ በፀጋ መቀበል እንጂ ተጎዳሁ ማለቱ አስራሚም ለአዘኔታ የማያመችም ነው፡፡ ወያኔ እንኳንስ ዐማራን የራሱን ወገኖች ሣይቀር በተኙበት ያረደ የለዬለት የጭራቆች መንጋ አይደል እንዴ! እነሱን እንዴት ማመን ይቻላል? ለተራ የጠበንጃ ስጦታ ሲሉ የእንግሊዝን ጦር መርተው ሀገርን የሚበትኑ፣ ለጣሊያን አድረው ኢትዮጵያን ባገኙት ዋጋ የሸጡና ወደፊትም የሚሸጡ፣ በ18ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በጦራቸው የዐማራን ግዛት ተቆጣጥረው ሲያበቁ ጦራቸው የዐማራ ሚስቶችንና ሕጻናትን ያባልጉ፣ ንብረትና ሀብትንም ይዘርፉ በነበረበት ወቅት ለንጉሣቸው አቤቱታ ቢቀርብ “ለወታደሮቻችን ከትግራይ  ሙ… ሪ  አላመጣንላቸውምና ሚስቶቻችሁንና ሴት ልጆቻችሁን ለትግሬ ወታደሮች አካፍሉ” የሚል ቅሌታምና እንደመለስ ሁሉ ለአፉ ለከት ያልነበረው ንጉሥ የነበራቸው ጉዶች እንዴት ነው ታምነው ኳስ አብረሃቸው የምትጫወተው? ምን ያለ ቂልነት ነው? ኤዲያ! አሁንስ ሁሉም ነገር እያስጠላኝ መጣ፡፡ ወያኔያዊ ብልጠቱም ዐማራዊ ሞኝነቱም ገደብ አጣ፡፡


በሚዲያ እንደምንከታተለው ወያኔ ትግሬዎች የዐማራን ዘር በሥውርም በግልጽም በቻሉት መንገድ ሁሉ ከምድረ ገጽ ለማጥፋት እየሞከሩ ነው፡፡ ሕጻናትን ሣይቀር እያመከኑ የዐማራን ትውልድ ከዚህ ዘመን እንዳያልፍ ለማድረግና በምትኩም የነሱን ዘር ብቻ ለማስፋፋት ከፍተኛ ጥረት እያደረጉ በሚገኙበት በአሁኑ የዐማራ የመጥፋት ያለመጥፋት ትግል ወቅት ወደትግራይ መሄድና ለጥቃት መዳረግ ከመነሻው ትርጉም አልባ ነበር፡፡ እነዚያ እወደድ ባይ የብአዴን “ባለሥልጣናት” ደግሞ “የአህያ ባል ከጅብ አያስጥል” ዓይነት ስለሆኑ እነሱን ተማምኖ ወደ የትም መንቀሳቀስ አይቻልም፡፡ እነሱ ራሳቸው በሕወሓት ሥር የሚገኙ የሆድና የወንጀል እስረኞች ስለሆኑ ሰውነታቸውን በገንዘብ ለወያኔ ባከራዩ አራሙቻዎች መተማመን በፍጹም አይቻልም፡፡ ስለዚህም ጥፋቱ የእግር ኳስ ቡድኑ አባላትና አመራሮቹ ናቸው፡፡ እንዲህ ያለ አጓጉል ድርጊት ወደፊት መደገም የለበትም፡፡ አታስቁብን፡፡

ትግሬዎች እግዜር ይማራቸው እንጂ ጨርሰው አብደዋል፡፡ እንደ ሙሉቀን ተስፋው ዘገባ ከሆነ ከማበድም በላይ በዘለቀ የውሻ ዕብደት ውስጥ የገቡ ይመስለኛል፡፡ የውሻ ዕብደት ከሌላው ይለያል፡፡ እውነተኛ የመቶ በመቶ ዕብደት በውሻ ላይ ብቻ እንደሚታይ ጥናቶች አረጋግጠዋልና ብዙዎች ትግሬዎችን የተጠናወታቸው የዕብደት ዓይነት ካልገደለ የማይለቀው የውሻ ዕብደት ነው ቢባል የማይቀጣጠቡት እውነት ነው፡፡ አቤት ለትውልዶቻቸው እያስቀመጡ የሚገኙት የግፍ ዓይነትና ብዛት!

 
እንግዲያውማ ስፖርት ለወዳጅነት፣ ስፖርት ለሰላም፣ ስፖርት ለመልካም ጉርብትና እየተባለ በሚሰበክበት ሰላማዊ ጦርነት ውስጥ የውጭ ጠላት የመጣ ይመስል ያ ሁሉ የጥላቻና የስድብ ናዳ እንዲሁም የዱላ ቅጥቀጣ ለምን ይታይ ነበር? ባለጌና ውሻ በቤቱ ይኮራል ይባላል፡፡ እውነት ነው - የነዚህኞቹ ደግሞ ባሰ፡፡ እነዚያን ካለትግራይ ሕዝብ አንድም መድኅን ያልነበራቸውን የዐማራ ወጣቶች በዚያ መልክ ቤተ ክርስቲያን እንደገባች ውሻ መቀጥቀጥ ትግራይ ውስጥ አንድም ጤነኛ ሰው እንደሌለ የሚጠቁም መሆኑን ብናምን ከፈጠጠው መራር እውነት አንጻር አልተሳሳትንም፡፡ ስለዚህ ትግራይ አደጋ ውስጥ ገብታለች ማለት ነው፡፡ እርግጠኛ ነኝ የትግሬ ተጫዋቾች ጎንደር ወይ ጎጃም ቢሄዱ ዝምባቸውን እሽ የሚል አይኖርም፡፡ ከዚህች ነጥብ አኳያ ራሱ  ዐማራ በርግጥም ጨዋና ትሁት ሕዝብ ነው፡፡ ይህ ክስተት ዐማሮችን ብዙ አስተምሮ እንደሚያልፍ ጥርጥር የለኝም፡፡ ጨዋው የትግራይ ሕዝብ እየተባለ የሚሞካሸው ያ ጨዋነት ወዴት እንደገባ ጤነኛ ትግሬዎች ሊያስቡበትና ሊጨነቁበትም ይገባል - ጊዜ ደግሞ መቼም ይሁን ማለፉ አይቀርም፡፡ የአእምሮን የአስተዳዳሪነት ቦታ ትዕቢትና ዕብሪት ተረክቦ ሁሉም አንድ ዓይነት የጡንቻ አምላኪ ከሆነ በርግጥም ሕወሓት በትግራይ ተሳክቶለታል፡፡ ወያኔ የሚፈልገው እንዲህ ዓይነቱን ዐማራ ላይ የነገሠና ድንበሩን ተሻግሮ የሚፈስ የትግሬ ጥላቻ በመሆኑ የወያኔዎች የዘመናት ትግል ከሚጠበቀው በላይ ግቡን መትቷል፡፡ ፈረንጆች ደስ ይበላቸው፤ ባንዳዎችና የባንዳ ልጆችም ጮቤ ይርገጡ፡፡ የዘሩት ሲበቅል እንደማየት የሚያስደስት ነገር የለም፡፡ ግን ግን የበቀለም ሁሉ አያድግም፤ ቢያድግም አያፈራም፤ ቢያፈራ እንኳን ለተወሰነ ጊዜ ነው፡፡ ክፋት ይቅርና ደግነትም እንኳን የመወለጃና አርጅቶ የመሞቻ ጊዜ አለው፡፡ ጊዜ ትልቅ ዳኛ ነውና፡፡

ከሁሉም በበለጠ አሣፋሪው ነገር ደግሞ የዐማራ ተጫዋቾችን  “ወንጀለኞች ነን ብላችሁ ካልፈረማችሁ ከትግራይ አትወጧትም!” ብለው ማስፈራራታቸው ነው - ይሄ የወያኔ ትንሽነት መለኪያ እዚያም አለ ማለት ነው፡፡ የሕወሓት inferiority complex ከሚገለጥባቸው አንዱና ዋናው ይሄው ራሱ በድሎ “ይቅርታ ጠይቁኝ” የሚለው የሰለቸን አባባል ነው፤ “የሞኝ ዘፈን ሁልጊዜ አበባዬ” አሉ? ለውጥና ወያኔ፣ ይሉኝታና ወያኔ፣ ሀፍረትና ወያኔ ሳይተዋወቁና ማዶ ለማዶ እንደተያዩ አረጁ፡፡ እነዚህ ሰዎች ወዴት እያመሩ ነው ግን? ኧረ መጨረሻቸውስ ምን ይሆን? ከጥቂት ግለሰቦች ጀምረው ማኅበረሰቡን እኮ አሳበዱት! እንዴት ነው “ሃይ!” የሚል አንድም ትልቅ ሰው ሊጠፋ የቻለው? ወደ ጠበል ወይም ወደሁነኛ ሐኪም ቤት የሚወስዳቸው ዘመድስ እንዴት ይጥፋ? በጥጋብ  የሚታወቁት የጀርመኑ ሂትለርና የጣሊያኑ ሙሶሎኒ እንኳ እንደዚህ ያለ ዕብሪት አላሳዩም፡፡ የነዚህን ሰዎች ዕብሪት ምናልባት የሚስተካከለው ሶዶምና ገሞራ በጠፉ ጊዜ እንዲሁም በኖኅ የውኃ ጥፋት ዘመን በጥጋብ ሁለመናቸው ታውሮ የሚሠሩትን ያጡት ጥንታውያኑ ወያኔዎች ቢሆኑ ነው፡፡ እነዚያ ጥጋበኞች እዚህ ላይ ለመግለጽ የሚቀፍ ነገር በምሥኪን ሴትና ወንዶች ላይ ይፈጽሙ እንደነበርና በዚያም ምክንያት የፈጣሪ መቅሰፍት እንደታዘዘባቸው  መጻሕፍትና መምህራን ይመሰክራሉ፡፡ እነዚያ ጥንታውያን ወያኔዎች በእሳትና በድኝ እንዲሁም በንፍር ውኃ እየተቀጡ በነበሩበት ጊዜ ሣይቀር ከበሮና እምቢልታ ይዘው በትላልቅ ዛፎችና በተራሮች አናት ላይ በቤቶች ጣሪያና በኮረብዎች ላይ እየወጡ ይዘፍኑ እንደነበር አሁንም ድረስ ከሃይማኖት ሰባኪያን አንደበት በየዐውደ ምሕረቱ የምንሰማው አሳዛኝ ሃይማኖታዊ ታሪክ ነው፡፡ እነዚያ የሶዶምና ገሞራ ጥንታውያን ወያኔዎች አሁን በምን ሒሣብና ከማንኛው የዓለም ሕዝብ የበለጠ ኃጢኣተኞች ሆነን ተገኝተን በኛ ዘመን ተፈጥረው እንዲህ በጥጋብ ሊሰክሩና ሀገር ምድሩን ሊያምሱ እንደበቁ ለማወቅ ሳስብ ውዬ ሳስብ ባድር አልከሰትልህ አለኝ፡፡ አንዳንዶቹን ወያኔ የሚሠራቸውን ወንጀሎችና ክፉ ድርጊቶች ሰይጣን ራሱም የሚያውቃቸው አይመስለኝም፡፡ ትግሬ ወያኔዎች ሰይጣንን ዕጥፍ ድርብ የሚያስከነዳ ዕኩይ ተግባር እንደሚፈጽሙ እዚሁ አፍንጫቸው ሥር ስላለሁ በሚገባ አውቃለሁ፡፡

  እንዴ? ይህ የኳስ ጨዋታ በራሱ ብዙ ይናገራል፤ መልእክቱ ጥልቅ ነው፡፡ እንደዚህ ዓይነት ቅሌት የሰማሁት በኞቹ የቅዱስ ጊዮርጊስ ተጫዋቾች ላይ በጋና ዱርዬዎች አማካይነት የደረሰው ግፍ ነው፡፡ የጋናው ክስተት ጋናዎች ለኢትዮጵያ ባዕዳን ናቸውና አደረጉት የተባለውን በደል ቢፈጽሙ በአንጻራዊነት ሲታይ ብዙም አይፈረድባቸውም፡፡ በዚያ የሰው ልጅ የስብዕና ውርደት ስንሳቀቅ እዚሁ ሀገራችን ውስጥ እንዲህ ዓይነት እጅግ አሣፋሪና ታሪክ ይቅር የማይለው በደል “ወንድም  በወንድሙ ላይ” ሲፈጽም በጣም አሳዛኝ ነው፡፡ እኛ ምንም አንልም፤ ምንም ማድረግም አይቻለንም፡፡ እግዚአብሔር ግን ፍርዱን ይስጥ፡፡ ጥጋባቸውን የሚያበርድ ነገርም ያምጣላቸው፡፡ የእንግሊዝ ጦር ጠግቦ በ“ጦር አምጪ” መሬት ሲደበድብ፣ የአንዳንድ የሀገራችን ነገሥታት ጦር ሠራዊት አባላትም እንዲሁ ጠግበው በጦር አምጪ መሬት ሲደበድቡ የለመኑትን የማይነሣ የነገሩትን የማይረሳ ጌታ እግዚአብሔር ጥጋባቸውን የሚያበርድ ጦርነትን እንደላከላቸው ከታሪክ ድርሳናት አንብበናል፡፡ አሁን ትግሬዎች የተቆጣጠሩት የኢትዮጵያ ሕዝብ ሀብትና ንብረት እንዲሁም ገንዘብ እስከዚህን አስክሯቸው በሕዝብ ላይ እንደዚህ ያለ ግፍና በደል ማድረሳቸውን በስፋት ከቀጠሉ ይህን ዓለማችን አይታው የማታውቅ ዕብሪት የሚያቀዘቅዝ አንዳች መለኮታዊ መቅሰፍት እንዲልክላቸው አምላክን በመማጠን እኛም የበኩላችንን ልንረዳቸው ይገባናል፡፡ በቁንጣን ተሰቃዩ፤ በጥጋብ አበዱ፡፡ ስለዚህ እንዲሰክኑ እንርዳቸው፡፡ አሁንስ አሳዘኑኝ፡፡

 
በመሠረቱ የጊዜ ጉዳይ እንጂ እነዚህ ጉዶች የሚቀጡበት ጊዜ መምጣቱ አይቀርም፡፡ የሚቀጡበት ጊዜ ከመምጣቱ በፊት ግን የወያኔ ጌቶች የእጃቸውን ማግኘት ሳይኖርባቸው አይቀርም፡፡ የዓለምን የኃይል ሚዛን እንዳሻቸው የሚዘውሩት ምዕራባውያን ለራሳቸው የቤት ሥራ የሚሰጣቸው ኃይል መኖር አለበት፡፡ የእኛ ልፋትና ጥረት ፍሬ ማፍራት የሚጀምረው ወያኔዎችን አዝሎ የያዘው ምዕራባዊ አንቀልባ መቀዳደድ ሲጀምር ነው፡፡ አለበለዚያ በጌታዋ  ተማምና ላቷን ከቤት ውጪ የምታሳድረዋ የወያኔ በግ በቀላሉ ዒላማችን ውስጥ አትገባም - ወያኔዎች ከኛ የበለጠ ጉልበትም ሆነ ጥበብ፣ ብዛትም ሆነ ዕውቀት… ኖሯቸው አይደለም እንዲህ ያንቀጠቀጡን፤ ወያኔዎችን እንቅፋት እንኳን እንዳይመታቸው እንደዐይኑ ብሌን ሌት ተቀን ተጠንቅቆ የሚጠብቃቸው በመረጃም በገንዘብም በሥልጠናም በምክርም በቴክኖሎጂም ወዘተ. ዕቅፍ ድግፍ አድርጎ የያዛቸው የኢትዮጵያ ትንሣኤ ጠላት አለ፡፡(ይህን ጽሑፍ የጻፍኩት ትናንት ማታ ነው፡፡ ወዲያው ሳልከው አደርኩና አሁን ላክሁት፡፡ ሌሊት ላይ ዘሀበሻን ስጎበኝ ግን በቬሮኒካ መላኩ የተጻፈ ግሩም መጣጥፍ አነበብኩ፡፡ ለዚህ ጽሑፍ አንዱ የኢ-ቀጥተኛ ዋቢ ሊሆን ይችላልና እሱን እንድታነቡ ልጋብዛችሁ፡፡) ያ ኃይል ነው ቀድሞ መሰበር ያለበት፤ ጊዜውን አናውቀውም እንጂ ያም ኃይል እንክትክቱ ይወጣል - ኢትዮጵያ ወደ ውጪ የሚሰደዱባት አስፈሪና የጭራቆች ዋሻ ሳትሆን ወደርሷ  የሚሰደዱባት የበለፀገችና የታፈረች ሀገር የምትሆነውም ያኔ ነው፡፡ ኢትዮጵያን በጥንቱ ገናና ታሪኳ እንድትነሣ የማድረጉ ትግል እንዲህ ቀላል እንዳይመስለን፡፡ ለኢትዮጵያ ጥፋትና ውድመት መንስኤውንና ውጤቱን ከወያኔዎች ጋር ብቻ የምናያይዝ ከሆነ ማንነታችንን የሚፈታተን ትልቅ ስህተት ነው፤ ጠላታችን ወያኔዎች ብቻ ቢሆኑ ኖሮ ሦስት ወርም ሥልጣን ላይ ባልቆዩ ነበር - እኔም አበዛሁት - ሦስት ወር አይደለም ከደደቢትም ባልወጡ ነበር፡፡ እነዚህን “ሰዎች” ኮትኩቶና ውኃ እያጠጣ አሳድጎ ለአቅመ-ኢትዮጵያን ማውደም ያደረሰው ያ ግዙፍ ዓለም አቀፍ ኃይል ነው፡፡ ችግራችን እንዲህ የጠነነውና መልክ አጥቶ የቀረው የችግራችን ቀንድ እዚሁ የሚደስቀን ቢሆንም ጭራው ግን ውጪ ሀገር መኖሩ ነው - ለማስታወስ እንጂ ይህን እውነት ብዙው ሕዝብ ያውቀዋል፡፡ የኢትዮጵያ ትንሣኤ ከምዕራባውያን የኃይል ሚዛን መለዋወጥ ጋር በቀጥታ የተገናኘ ነው፡፡ አንዳች ምድራዊም ይሁን ሰማያዊ ኃይል ለነዚህ ክፉ የዐውሬው ምርኮኞች የራሳቸው የቤት ሥራ ካልሰጠልን የማርያም መንገድ አግኝተን እነዚህን ጓዳችን ውስጥ የሚርመሰመሱ ትናንሽ ዐውሬዎች ማንበርከክ ያስቸግረናል፡፡ በዚያ ላይ የኛ የራሳችን ተደራራቢ መጥፎ ጠባያት አሉብን - መመቀኛኘት፣ መናናቅ፣ በሥልጣን ጥም መቃተት፣ ለሀብትና ለገንዘብ አቅልን መሣት፣ ብሔራዊ ስሜት ማጣት፣ ተስፋ መቁረጥ፣ ራስን ከመጠን ባለፈ መውደድና ሀገርንና ሕዝብን ጨርሶ መርሳት፣ ከሃይማኖታዊና ሞራላዊ የመልካም ሥነ ምግባር ዕሤቶች መራቅ፣ ሙስና ውስጥ መዘፈቅ፣ በጎሣና በነገድ ፍቅር መማረክ፣ ሰውነትን ለሚያረክሱ መጥፎ ተግባራት ለምሣሌ ለድግምት፣ ለቦረንትቻ፣ ለደንቃራ ጣይ፣ ለአንደርብ መታች፣ ለአውሊያ  ባዲገዝ፣ ለጥንቆላ፣ ለመተት፣ለኮከብ ቆጣሪ፣ ለሞራ አንባቢ፣ ለጥላ ወጊ፣ ለትብታብ፣ ወዘተ. መሸነፍ … ጥቂቶቹ ናቸው ፡፡ ከነዚህ ፅኑ ደዌያት በቶሎ ካልተፈወስን ደግሞ ለችግሮቻችን መጉላት የኛም ሚና ትልቅ ነውና አሁንም  በምንፈልገው ፍጥነት ከችግሮቻችን አንወጣም - በዓለም እንደተበተንን፣ መሣቂያና መሣለቂያም እንደሆንን ብዙ ጊዜ ልንቆይ እንችላለን፡፡ ተስፋ ለማስቆረጥ አይደለም፤ ችግሮቻችንን እንድናውቅ እንጂ፡፡
 

ትልቁ መፍትሔ ግን የወያኔ ጌቶች የማይቀርላቸውን “የቤት ሥራ” በቶሎ እንዲያገኙ መጸለይ ነው - ለጊዜው ከጸሎት ሌላ እነዚህን በላዔሰቦች ለመታገል አማራጭ ያለን አልመሰለኝም - ለጥቁሮቹ ናዚዎችም መፍትሔ አጥተናል እንኳንስ ለነጮቹ፡፡ እነሱን አደብ የሚያስገዛ ኃይል ደግሞ በየጓዳቸው ይዘውታልና ቀኑ ሲደርስ እኛም ነፃ የምንሆንበት አጋጣሚ ይፈጠራል የሚል እምነት አለኝ፡፡ ዳርዳርታውን ስናጤን ያ የመጨረሻ ቀን እየመጣ ይመስላል፡፡ እነሱ እኛን የሚረሱበት አጋጣሚ ካላገኙ እኛ በነሱ ተንኮልና ሤራ እንደተማረርንና በወያኔ ልጆቻቸው መቅኖ እንዳጣን እንኖራለን፡፡ ችግራችን ውስብስብ ነው - ወያኔዎች ግን ንፋስ ያመጣቸው የትልቁ ችግር ቅርንጫፎች እንጂ በራሳቸው ችግር ሊሆኑ የማይችሉ ኢምንት ነገሮች ናቸው፡፡ እኛ ብንስተካከል የነሱ ጉዳይ ቀላል ነው፡፡ መተማመኛችንን ሀገር ውስጥ እናድርግ፡፡ በውጭዎች መተማመን የሚቻል እንዳልሆነ ያሣለፍነው የመከራና የስቃይ ዘመን ምሥክር ነው፡፡ የኢትዮጵያንና የዐማራን ስም ሲሰሙ የሚያንዘረዝራቸው ኃይሎች ጋር ተጠግተን ፋይዳ ያለው ነገር ማምጣት አንችልም፡፡ የምንጠጋውንና የምናስጠጋውን ቀድመን እንወቅ፡፡ አለበለዚያ ታጥቦ ጭቃ ነው - እንደ እስካሁኑ፡፡ የጠላቶቻችን ክንድ ደግሞ የሚናቅ አይደለም፡፡ በጣም ረጂምና የዓለማችን ገዢዎች ሁለንተናዊ ድጋፍ የታከለበት ከፍተኛ ወታደራዊና ኢኮኖሚያዊ ኃይል አብሯቸው አለ፡፡ ይህን ግዙፍ ኃይል ለመቋቋም ልዩ ሥልት ነድፎ መንቀሳቀስ ይገባል እንጂ በስሜትና በደም ፍላት እነዚህን ነቀዞች ከአራት ኪሎ ቤተ መንግሥት አንድ ስንዝርም ፈቀቅ ማድረግ አይቻልም፡፡ የምኞትና የህልም ፈረስ መጋለብ ክልክል ባይሆንም ኢትዮጵያን እንደገና ለመፍጠር እስካሁን ይደረግ ከነበረው የተናጠል ሩጫና የሩቅ ለሩቅ የቃላት ጦርነት ባለፈ ተግባራዊ እንቅስቃሴ ማድረግ ከሁሉም የሚጠበቅ ወቅታዊ አንገብጋቢ ጉዳይ ነው፡፡ በተለይ ይህን የመገፈታተር  ዘመን አመጣሽ  ኢትዮጵያዊ መጥፎ ባህል ማስወገድ ካልቻልን በዚህ የቅምቡርስ አካሄድ የትም አንደርስም፡፡ ወያኔ ከጌቶቹ ከሚያገኘው ሁልአቀፍ ዕርዳታና ድጋፍ ይልቅ የኛ ጅላጅል ጠባይ በጣም አግዞታል፡፡   ከመከራ እንኳን የማንማር ጅሎች ነን፡፡

 
26 ዓመት ቀላል ጊዜ አይደለም፡፡ ለብልህ ዜጋ ይህ ያሣለፍነው ረጂም የመከራና የስቃይ ዘመን ብዙ ሊያስተምር በቻለ ነበር፡፡ እኛ ግን የዛሬ 26 ዓመት የነበርንበት ቦታ(ያስቀመጡን ቦታ) ላይ ነን፡፡ ብዙዎቻችን በሥጋ አረጀን እንጂ በመንፈስ አላደግንም፡፡ የመረገም እስኪመስል ድረስ ብዙ መጥፎ ነገሮች ተፈራረቁብን፤ እኛ ግን አሁንም እዚያው ነን፤ አሁንም አንዳችን አንዳችንን እንወነጅላለን፤ በትንሹም በትልቁም - ባለፈውም በአሁኑም እንወነጃጀላለን፡፡ አንዳችን ለአንዳችን አንተኛም፡፡ አንዳችን ለአንዳችን ወጥመድ ስንዘረጋ፣ መርዝ ስንበጠብጥና ገመድ ስንፈትል እንገኛለን - ይቅርባይነትን ተጠይፈን በጠብና በቂም በቀል አባዜ ተለክፈናል፡፡ በሌላም አቅጣጫ ራሳችንን ስንታዘብ ሁላችንም ሟች መሆናችንን የዘነጋን እንመስላለን፤ ምድራዊ ዕድሜያችን በሺዎች የሚቆጠር ያህል በጣም ሩቅ እናስባለን - ግን ማንኛችንም ቅርብ አዳሪዎች ነን፤ የአንድ ሐሙስ ሰዎች፡፡ በቅርቡ እንኳን ስንቶች ታዋቂና ጠቃሚ ሰዎች ተለዩን? እነጄኔራል ጃጋማ ኬሎ፣ እነአሰፋ ጫቦ፣ እነፈቃደ ሸዋ ቀና… አንዳንዶቹ ታምመው … አንዳንዶቹ እንደሰላቢ ድንገት አልተለዩንም?  ዛሬ የገደልነው ሰው ሳይቀበር ምሽቱን ቀድመን ልንገነዝና ልንቀበር እንደምንችል አናውቅም፡፡ ዕውቀትና ጥበብ ርቀውን በድንቁርና ባሕር የምንዋኝና በሥጋ ገበያ ጠፍተን ጤናማ ኅሊናችንንና የነፍሳችንን ጥሪ የምናማስን ጥቂቶች አይደለንም፡፡ ስለዚህም ለአንዳንዶቻችን ወያኔ ሲያንሰን እንጂ አይበዛብንም፡፡ የሆኖ ሆኖ እኛው ለኛው በምንፈጥረውም ይሁን ሌሎች በኛ ላይ በሚፈጥሩት ችግር ሳቢያ ችግራችን  ከመቀረፍ ይልቅ ከጊዜ ወደጊዜ ይበልጥ እየተወሳሰበ በመሄዱ ጥቂቶቻችን  በዋሻው ጫፍ የምናየው የነፃነት ብርሃን ከመድመቅ ይልቅ እየደበዘዘ መምጣቱን መካድ አይቻልም፡፡  

 
ዛሬና አሁንም ቢሆን ብዙም አልመሸም፡፡ እናም የደበዘዘው እንዲደምቅ፣ የራቀው እንዲቀርብ፣ የጠፋው እንዲገኝ…. እንደቴዲ አፍሮ ያሉ የጨለማ ዘመን ከዋክብትን እየተከተልን በፍቅርና በመተሳሰብ በአንድነት መጓዝ አለብን፡፡ ስህተት የሰው ባሕርይ ቢሆንም ከስህተት ለመራቅ እየሞከርን እርስ በርስም በመተራረም ደጉን ዘመን በጋራ ለማምጣት ታጥቀን እንነሳ፡፡ ከዕውቀትና ከማስተዋል የወጣ ሕዝብ ከባሕር እንደወጣ ዓሣ ነውና እነዚህን አንጡራ ሰብኣዊ ሀብቶች የባሕርይ ገንዘቦቻችን ለማድረግ መጻሕፍትን እናንብብ፤ ታሪክን ዕንወቅ፤ አንደበታችንን እንግራ፤ ቁጣን በትግስት፣ ግልፍተኝነትንና ተሳዳቢነትን በጨዋነት እንለውጥ፡፡ … በምን ተነስቼ እዚህ ደረስኩ በል ግን - አዎ፣ ያ የእግር ኳስ ጨዋታ ነው ነገር ለኩሶብኝ ጠባየን እንደውኃ ያቀጠነብኝና ብዕሬን አስቆጥቶ እስከዚህን ያስቀባጠረኝ፤ ቻው፡፡

ለገምቢ አስተያየት - ma74085@gmail.com (ውይ ረስቼው፤ ባለፈው ሰሞን መጣጥፌ ላይ ምሥጋናም ወቀሣም የሰደዳችሁልኝ አላችሁ፡፡ ሁላችሁንም አመሰግናለሁ፡፡ ብዙ የስሜት ጫፎች አሉ፡፡ ይህንንም ያኛውንም መንካት መቻል ጥሩ ነው፡፡ መጨረሻው ግን መሀል አካባቢ መገናኘት ቢሆን ይበልጥ ደስ ይላል፡፡ የሚዲያዎችም የጸሐፊዎችም ዓላማ ልዩነቶችን አቻችሎና እስከተቻለም ለማስወገድ ሞክሮ ሕዝብን በሰላማዊ መንገድ ማቀራረብና የግጭት መንስኤዎችን ማጥፋት ነውና፡፡)