Thursday, October 17, 2019

ያለንበት ሁኔታ! አቻምየለህ ታምሩ Ethio Semay 2019-10-17


ያለንበት ሁኔታ! አቻምየለህ ታምሩ
Ethio Semay
2019-10-17
Photo above the Renowned Ethiopian Scholar Achamyeleh Tamiru
ኢትዮጵያ ዛሬ የደረሰችበትን ቁልቁለት አንዳንድ ሰዎች ከዘመነ መሳፍንት ጋር ያመሳስሉታል። ይኽ ግን ፍጹም የተሳሳተና ዘመነ መሳፍንትን ካለመመርመር የሚሰጥ ግልብ አስተያየት ነው። ዘመነ መሳፍንት በግራኝና በኦሮሞ ወረራዎች ፈርሶ የነበረውን የኢትዮጵያ ክፍሎች እንደገና አንድ ለማድረግና ጠንካራ ማዕከላዊ መንግሥት ለመገንባት የማይሞት ራእይ የነበራቸው የአካባቢ መሳፍንት የተነሡበት የሐሳብ ዘመን ነበር። በዘመነ መሳፍንት፣ የአካባቢ መሳፍንት የተደራጁት በዘመናዊ መንገድ ነበር።
ይኽ የዘመነ መሳፍንት ዘመናዊነት መገለጫው በሐሳብ እንጂ እንደ ዛሬው በነገድ ያልነበረው አደረጃጀታቸው ነው። ዛሬ የምንገኘው ከዘመነ መሳፍንት ዘመን በመቶ እጥፎች ወደ ኋላ ሄደን የባንቱስታን ዘመን ላይ ነው። ዛሬ የደረስንበት ቁልቁለት የዘመነ መሣፍንቱ ደረጃ ቢኾን ኖሮ በስንት ጣዕሙ በታደልን ነበር። ባጭሩ ዘመነ መሳፍንት ኢትዮጵያን እንደገና አንድ ለማድረግና ማዕከላዊ መንግሥት ለመመሥረት የየአካባቢው መሳፍንት በሐሳብ ተደራጅተው ይፎካከሩበት የነበረ ብሩህ ወቅት ነበር። የዘመነ መሳፍንት መኳንንቶችና መሣፍንቶች ራእይ፣ በቋንቋ አጥር የተከፋፈሉ የጎሳ ሀገሮች የመመሥረት ሳይኾን የዐፄ ዐምደ ጽዮንንና የዐፄ ዘርዓ ያዕቆብን የሁሉም የኾነች ኢትዮጵያን መልሶ ማቋቋም ነበር። የዛሬዎቹ ኋላቀር ብሔርተኞች ራእይ ግን በሐሳብ ሳይኾን በቋንቋ ተሰባስበው የጎሳ ሀገር የመመሥረት ኋላቀርነት ነው።
ስለዚህ የዛሬው ኋላቀር የቋንቋና የጎሳ ፖለቲካ የሚካሄድበትን፣ በድንቁርና የጎሳ ሀገር ለመመሥረት የሚራኮቱ ጎሰኞችን ዘመን ትልቅ ሐሳብና የማይሞት ራእይ የነበራቸው የአካባቢ መሣፍንቶች ታላቅ የጋራ ሀገር ለመመሥረት ይወዳደሩ ከነበሩበት ከዘመነ መሳፍንት ጋር አንድ አድርጋችሁ ብርሃንንና ጨለማን አታመሳስሉ። በዘመነ መሳፍንት ማዕከላዊ መንግሥትና የኢትዮጵያ የግዛት አንድነት ባይጠናቀቅም እንደዛሬው ሕግና ኅሊና ጨርሶ አልጠፋም ነበር። ዛሬ ግን ሕዝብን የሚገዛ ሕግና ኅሊና የማይገዛቸው ጎሰኞች የተፈጠሩበት ዘመን ላይ ነን። በዘመነ መሳፍንት በተለይም በሰሜኑ የሀገራችን ክፍል የአካባቢ መኳንንቶች ሁሉ የማይሽሩት የአውራጃ ይዞታ፣ የመሬት ባለቤትነት መብት እና የአስተዳደር ወሰን ነበር። ዛሬ ግን ማንም ጎሰኛ ተነስቶ የጎሳ አባላቱን አሰልፎ ያሻውን አካባቢ ‹ይኽ ግዛት የኔ ነው› የሚልበት የባንቱስታን ዘመ  ላይ ደርሰናል።
 በእውነቱ ‹አንድ ሕዝብ የሚገባውን መሪ ያገኛል› የሚለው አባባል ስህተት የለበትም። ዐቢይ አሕመድ ራሱን ያለምንም ሐፍረት ንጉሥ አድርጎ ነው የሚያስበው፤ ተከታዮቹም እንደመኳንንት ነው የሚያደርጋቸው። ምንም እንኳን የሕዝብ ይሁንታ ሳይኖርበት ተሽለኩሉከው ሥልጣን ላይ የወጡ ወንጀለኞች ቢኾኑም፣ የሀገርና የሕዝብን ሀብት ሲያባክኑ፣ የሕዝብ ይሁንታ የሚያስፈልገውን ውሳኔ ሁሉ በዘፈቀደ ሲወስኑ ያለምንም ሐፍረት ነው። ጃዋር መሐመድ ራሱን ፈላጭ ቆራጭ አድርጎ አንግሷል። ራሱን ፈላጭ ቆራጭ አድርጎ አንግሷል ማለቴ ራሱን ከሕግ በላይ አድርጓል ማለቴ ነው። ይኽንን የሚጠራጠር ቢኖር ራሱን ይመርመር። በዐቢይ ኢትዮጵያ ጃዋር ከሕግ በላይ ነው። ምንም ቢያደርግ ተጠያቂነት የለበትም። ጃዋር እንደ ዐቢይ ንጉሥ ነኝ ባይልም ሥልጣኑ ግን ‹ከሰባተኛው ንጉሥ›ም ከሕግም በላይ ነው። አንዳንዴ ሳስበው ጃዋር ራሱን የቄሮ መሪ አድርጎ በአቋቋሙ ግን የኢራኑን አያቶላህ ዐሊ ኻሚኔይን የሚኮርጅ ይመስለኛል። ጃዋር የሚያደራጀው በሕግ የማይጠየቀውና ሕገ ወጡ የቄሮ ድርጅት አያቶላህ ከሚመራው የኢራን ዐቢዮታዊ ዘብ ጋር አደረጃጀቱ ተመሳሳይ ነው። አያቶላህ የሚመራው የኢራኑ ዐቢዮታዊ ዘብ ተጠያቂነት የለበትም፤ ሕግም አይገዛውም።
የአያቶላህ ኻሚኔይ ዐቢዮታዊ ዘብ የሀገሪቱ የጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዥ አያዘውም፤ ጦር ሠራዊቱን ሳይቀር ያዛል። አያቶላህ ጃዋር የሚመራው ቄሮም እንደዚያው ነው። ባለፈው ዓመት አያቶላህ ኻሚኔይ ‹የባሕል ወረራ› ነው ያለውን እንግሊዝኛ ቋንቋ በኢራን አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ውስጥ እንዳይሰጥ እገዳ ጥሏል። አያቶላህ ጃዋርም በዘንድሮው ዓመት የትምህርት ሚኒስቴር አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ውስጥ የፌዴራል መንግሥቱ የሥራ ቋንቋ አማርኛ በተደራቢነት እንዲሰጥ የወሰነውን ውሳኔ ተቃውሞ አማርኛን ልክ አያቶላህ እንግሊዝኛን የባዕድ ቋንቋ እንዳደረገው ሁሉ የባዕድ ቋንቋ አድርጎት ግዛቴ ብሎ ባወጀው ኦሮምያ በሚባለው ክልል ውስጥ እንዳይሰጥ እገዳ ጥሏል። ተቃዋሚ ነን እያሉ ወደሚያደርቁን ስንመጣም ጉዳዩ ያው ነው። 

ብርሃኑ ነጋ ኢ.ማ.ሌ.ድ.ኅን የሚመስል አማራ ጠል ስብስብ ጨፍልቆ፣ ሊቀመንበር መንግሥቱ ኃይለ ማርያም የተመረጡበትን የኢሠፓ ጉባኤ በሚመስል ቲያትር የዐቢይ ጃንደረባ ኾኖ ተመርጧል። የዲሞክራሲ ቀንዲል ተብለው የነበሩ፣ በጉባኤው ላይ የታደሙ አንዳቸውም ጃንደረባ የመረጡበትን ቲያትር ቅር ሳይላቸው ታድመው፣ እነሱም ምክትል ጃንደረባና ባህታዊ ኾነው ተሹመው ወጥተዋል። ትግራይ በታሪኳ አይታ የማታውቃቸው ዓይነት መሳፍንት መቀሌ ላይ ተሰይመዋል። በተቀረው የኢትዮጵያ በየዞኑ፣ በየወረዳው፣ በየቀበሌ ያለው ሁኔታ ተመሳሳይ ነው። በየአካባቢው የሚኖረው ሕዝብ ሁሉ ያንተ ወገን ነን እያሉ ወንጀልንና ቅጥፈትን ሥርዓት አድርገው ራሳቸውን በላዩ ላይ በሰየሙ መሳፍንት ቁጥጥር ስር ታፍኖ እየተበዘበዘ ይገኛል። ሥልጣን ላይ የሌሉም ቢኾኑ ዓላማቸው በተመሳሳይ ሁኔታ በሕዝብ ይሁንታ ሳይሆን በአመጽ፣ በማስፈራራት እና በጉልበት ወደ ሥልጣን ለመምጣትና የቆዩቱ የቆሉትን እያሳረሩ በተራቸው መዝረፍ ነው። ይኽ በኢትዮጵያ ያለፉት አርባ አራት ዓመታት ፖለቲካ ውስጥ የተለመደ አሠራር ኾኗል። በራሱ ጭንቅላት የሚያስብ፣ የነገሩትን እንዳለ የሚቀበል ሳይኾን የሚመረምር፣ የሚያጣራ፣አመዛዝኖ የሚቃወም ወይም የሚደግፍ፣ የሱ ብቻ ሳይኾን የወገኑ መብቱ ሲነካ አይሆንም የሚል ኢትዮጵያውያዊ እስካልተፈጠረ ድረስ ከፍ ሲል ለማቅረብ የሞከርሁት ዛሬ የደረስንበት ሁኔታ እጣ ፈንታችን ነው።
Posted at Ethio Semay