Friday, December 10, 2021

ለምን አሁን? የሆነ የተደገሰልን ነገርማ አለ! ዳግማዊ ጉዱ ካሣ ETHIO SEMAY (12/9/2021)

 

ለምን አሁን? የሆነ የተደገሰልን ነገርማ አለ!

ዳግማዊ ጉዱ ካሣ

ETHIO SEMAY   (12/9/2021)


ስለአስከፊው የኑሮ ውድነት ከጻፍኩ አንድ ሣምንት እንኳን አይሞላኝም፡፡ ትናንት ማታ ደግሞ ከዛሬ ጀምሮ ተግባራዊ የሚሆን በነዳጅ ውጤቶች ላይ ታይቶና ተሰምቶ የማያውቅ የዋጋ ጭማሬ መደረጉን ሰማሁ፡፡ ለታሪክ ፍጆታ ያህል ትንሽ ማለት ፈለግሁና የግዴን ብዕር አነሳሁ፡፡

 

ነገሩ ሁሉ “የበላችው ያስገሳታል፣ በላይ በላዩ ያጎርሳታል” እንዲሉ ሆኗል የአቢያችን መንግሥት ነገር፡፡ ይሁን፡፡ እየሆነ ያለው ሁሉ የሚጠበቅ ደግሞም በጣሙን የዘገዬ ነው፡፡ አስገራሚውና ለአንዳንዶች ደግሞ አስደንጋጩ ነገር የሰሜኑ ጦርነት በረድ ሲልና በተወሰነ ደረጃም ቢሆን እፎይታን ሲሰጥ የመሀል አገሩ ጦርነት (ኢኮኖሚዊው ማለቴ ነው) ባልታሰበና ባልተጠበቀ ሰዓት ማገርሸቱ ነው፡፡ ይህን ጦርነት የሚለኩሱት ወገኖች ዓላማና ፍላጎት ግልጽ ቢሆንም መንግሥት ተብዬው የነሱን ዓላማ አራማጅ ካልሆነ በስተቀር ጤናማ ነኝ የሚል አንድም የአቢይ መንግሥት ወገን ይህን ጭማሬ መደገፍ አልነበረበትም፡፡ የኛ የምንለው መንግሥት ቢኖረን ኖሮ እንዲያውም ከሚታዬው የኑሮ ውድነት አንጻር የነዳጅን ጨምሮ የሌሎች ሸቀጦችንና የአገልግሎት ዋጋዎችን መቀነስ ይጠበቅበት ነበር፡፡

 

 ግን የተባለ አይቀርምና ሁለንተናዊ ጦርነቱ በአንዱ ወገን ከጥይት አረር ዐረፍ ወደማለቱ ስናዘነብል በሌላ ወገን በኑሮ ውድነቱ ሕዝብን መቁላት የዚያኛው የመድፍና መትረየሱ ጦርነት አካል ሆነና ከእሳት ወደእሳት የመገለባበጣችን ዕጣ የማያልፉት ሆነ፡፡ የፈጣሪ መምጫው አይታወቅም፡፡ ይህን ዓይነት ጭማሬ አይቼ አላውቅም፡፡ ሕዝብን መናቅ ነው፤ ምን አባታቸው ያመጣሉ ብሎ በሕዝብ ላይ መሣለቅ ነው፡፡ ግን አይምሰላቸው፡፡ ሕዝብ መንግሥትን ለመጣል አቅም ባይኖረው በዕንባ ዶፍ እየታጠቡና በንጹሓን የደም ባሕር እየዋኙ ዕድሜ ልክ መግዛት አይቻልም - የቀን ጉዳይ ነው፡፡ ከወያኔና ከቀደምት አምባገነን መሪዎች መማር ብልህነት ነበረ፡፡ እነዚህ ግን ደናቁርት ናቸውና ከማንም አይማሩም፡፡ 

 

አሁን በአንድ ሊትር ቤንዚን ላይ የተጨመረው ገንዘብ (ብር 5.88) በቀ. ኃ. ሥላሤ ዘመን በአማካይ 15 ሊትር ቤንዚን ያስገዛ ነበር፤ በደርግ ዘመን በአማካይ 5 ሊትር ያስገዛ ነበር፤ በወያኔ የመጀመሪያ ዓመታት ወደ 3 ሊትር አካባቢ ያስገዛ ነበር፡፡ የአሁኑ ጥቅል የአንድ ሊትር ቤንዚን መሸጫ ዋጋ (ብር 31.74) ደግሞ በቀ.ኃ.ሥ ዘመን በአማካይ 79 ሊትር ያስገዛ ነበር፤ በደርግ ዘመን በአማካይ 30 ሊትር ያስገዛ ነበር፤ በወያኔ ዘመን በተለይ በመጀመሪያዎቹ 10 ዓመታት ገደማ በአማካይ 7 ሊትር ያስገዛ ነበር፡፡ ለትውስታ ያህልና ከጊዜ ወደጊዜ ኑሯችን እንዴት ወደላይ እንደተወነጨፈ ለማስታወስ ያህል ነው፡፡ በሌላ በኩል ግን ገቢያችን ሲታይ ብዙም ሲንቀሳቀስ አይታይም፡፡ እጅግ በጣም ዘገምተኛ ነው፡፡

 

አንድ ብልጥ ሰው ወይም ድርጅታዊ አካል አገርንና ሕዝብን መጉዳት ሲፈልግ ወይም ማኅበራዊና ፖለቲካዊ ቀውስ ማቀጣጠል ሲሻ የማኅበረሰቡን ስስ ብልት ፈልጎ ያቺን ይነካካል፡፡ ይህን ለማድረግ መጠነኛ ጥናትም ያስፈልጋል፡፡ ሰውዬው ክፉ ከሆነ “አገርን በቀውስ ለማናጋት ምን ባደርግ ይሻላል?” ብሎ ማሰብና ማሰላሰል አለበት፡፡ ከዚህ ነጥብ አኳያ ሁሉን የኅብረተሰብ ክፍል የሚያጠቃ ቫይረስ ፈልጉ ቢባል ከነዳጅ ምርቶች የሚበልጥ አይገኝም፡፡ የነዳጅ ምርቶችን ዋጋ መቀነስ ወይም መጨመር ሁሉን ሕዝብ ከሞላ ጎደል እኩል የማግኘት ያህል ነው፡፡ ይህ ተጠየቃዊ አካሄድ ለማንም ግልጽ ነው፡፡

 

ከቤትህ ወደ መሥሪያ ቤት፣ ከመሥሪያ ቤት ወደ ቤትህ፣ ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ … የምትንቀሳቀሰው በአብዛኛው በመኪና ነው፡፡ እህል የሚጓጓዘው፣ በሽተኛ የሚጓጓዘው፣ ፋብሪካዎች የሚንቀሳቀሱት፣ የፋሪብካ ምርቶችና ሸቀጦች የሚጓጓዙት… በነዳጅ ነው፡፡ ነዳጅ የአንድ ሀገር የደም ሥር ነው፡፡ ስለዚህ ነዳጅን መቆጣጠርና በነዳጅ ዋጋ ላይ የአሁኑን የኛን መሰል ትልቅ ዋጋ መከመር የአንድን ሀገር ሰላም ለማናጋትና ድብቅ ዓላማን ለማሳካት ዓይነተኛ ብልኃት ነው፡፡ የሆነ ኃይል ኢትዮጵያ ውስጥ እያደረገ ያለውም ይህንን ነው፡፡ በአራዳ ቋንቋ ይመቸው! ሕዝብ ሲተኛ ጥሩ አይደለም - ይበድ እንጂ፡፡

 

የአቢይ መንግሥት የተሞላው እምብዝም ማሰብ በማይችሉ ወጣት ቄሮዎችና ቄሪቶች ነው፤ ሃይማኖታቸውም የአብዛኞቹ ፕሮቴስታንት መሆኑ የአደባባይ ምሥጢር ነው፡፡ ከሃይማኖታቸውም ሆነ ከነገዳቸው ጋር ጠብ የለኝም፡፡ ሃይማኖታቸውንና ነገዳቸውን መሠረት አድርጎ ከተጣባቸው አጋንንታዊ ልክፍት ጋር ግን መቼም የማይታረቅ ጠብና ተቃውሞ አለኝ፡፡ እነዚህ ንፍጣቸው ያልደረቀ ኮረዳዎችና ጉብሎች የሚያስተዳድሯት ኢትዮጵያ ልትገኝበት የምትችለው ማኅበራዊና ፖለቲካዊ ቀውስ አሁን ካለው ቢብስ እንጂ ሊያንስ እንደማይችል በበኩሌ ከግምት ባለፈ መረዳት እችላሁ፡፡

 

 እኔ በልጅነቴ የማውቃት ኢትዮጵያ በነዚህን መሰል ጎደሎዎች እንዲህ ስትበሻቀጥ ሳይ ኢትዮጵያዊነቴን ብቻ ሳይሆን እንደሰው መፈጠሬን ራሱ እረግማለሁ - ትልቅ አለመታደል ነው፡፡ ሀገርን  በአግባቡ ለማስተዳደር ከዘረኝነት ልክፍትና ያን ተመርኩዞ አእምሮ ውስጥ ከተቀበቀበ የሀሰት ትርክት ነጻ መሆንን፣ በትምህርትና በልምድ መበልጸግን፣ በዕድሜና በተሞክሮ የዳበረ የአስተዳደር ጥበብና ማኅበረሰብኣዊ ዕውቀት መጎናጸፍን ይጠይቀል፡፡እንጂ ገና ለገና የሠፈሬ ልጅ ነው ተብሎ፣ በካድሬነት አብረን ብዙ ጊዜ ሠርተናል ተብሎ፣ የአንድ ምድራዊ ጌታ ሎሌዎች ነበርን ተብሎ፣ የአንድ አክራሪ ሃይማኖት ተከታዮች ነን ተብሎ፣ እነእገሌን ለማጥፋት የአንድ እርኩስ ዓላማ ተባባሪና ደጋፊ ነው ተብሎ፣ … ከየሥርቻው እየለቃቀሙና እየተጠራሩ ይህን ክቡር የመንግሥት አስተዳደር ቦታ በቀማኛና በመንደር ወጠጤ ቢሞሉት ውጤቱ አሁን እንደምናየው ሀገርን ማፍረስና ከዚህም የዘለለ ነው፡፡ አዎ፣ ገና ምን አየንና! የተደገሰልን እኮ አልተነካም፡፡

 

መለስ ዜናዊ ተናገረው የሚባል አንድ እኔ እዚህ ልጠቅሰው የማልፈልገው ነገር ታወሰኝ፡፡ እውነቱን ነው፡፡ እናም እሱ እንዳለው ሀገራችን እግዜር ይሁናት እንጂ በነዚህ ልጆች እንደብርጭቆ ልትፈረካከስ የቀራት ጊዜ እጅግ በጣም ትንሽ ነው - እንደነሱና እንደላኪዎቻቸው፡፡ እንደ አንድዬ ግን አይሳካላቸውም፡፡

 

ሶማሌዎች ያኔ በወያኔዎች ዘመን መጀመሪያ አካባቢ ተናሩት የተባለውም አሁን ትዝ አለኝ፡፡ ልክም ናቸው፡፡ ምን እንዳሉ ደግሞ እዚህ አልናገርም፡፡ በተግባር ግን በቅርቡ እናየዋለን፡፡ ጊዜ ዳኛ ነው፡፡በጊዜ ሂደት የማይታይ ጠማማና ወልጋዳ፣ ቀጥ ያለና ሸበላ የለም፡፡ ዳር ላይ ነን ለማንኛውም፡፡ አይዞን!!

 

“የአቢይ መንግሥት ምን ይመስላል?” ብለን ራሳችንን ብንጠይቅ ኢየሱስ ክርስቶስ ፈሪሣውያንና ሰዱቃውያን ጠላቶቹ ሊሰቅሉት እየተዘጋጁ ባሉበት ወቅት “የሚያደርጉትን አያውቁምና ጌታ ሆይ ይቅር በላቸው” ብሎ የተናገረውን ቃል የሚያስታውሰንን የዚያን ዘመን ሁኔታ የሚዘክር ይመስላል፡፡ ከላይ እስከታች ይራወጣሉ እንጂ ምን እያደረጉ እንደሆነ እንኳንስ ለኛ ለነሱም ግልጽ የሆነላቸው አይመስልም፡፡

 

ይገርማል፡፡ በአንድ በኩል አንድ ሚሊዮን ዲያስፖራና የውጭ ሀገር ዜጋ በመጪው ገና ወደ ኢትዮጵያ እንዲመጣና እንዲጎበኝ ይጋብዛሉ፡፡ ይህን ግብዣ ባስተላለፉ ማግስት ደግሞ ማንም ከውጭ የሚመጣ ሰው ከለበሰው ልብስና ከተጫመተው ጫማ ውጭ ሶፍትና መሀርብም እንኳን ይዞ እንዳይገባ ህግ ያወጣሉ፡፡ ዕብደት ነው፡፡ እነዚህ ወፈፌ የጎሣ ፖለቲካ ልክፍተኞች የሚያደርጉትን አያውቁም ማለት ታዲያ ስህተት የለውም፡፡

 

ይታያችሁ - አክስቴ ከእንግሊዝ ስትመጣ - አጎቴ ከአሜሪካ ሲመጣ፣ልጄ ከስዊድን ስትመጣ፣ እናቴ ከአውስትራሊያ ስትመጣ … ድሃ ነኝና አንዲት ቁራጭ ጨርቅ ወይም አንዲት አሮጌ ላፕቶፕ መጠበቄ አይቀርም፡፡ ይህን እንደምጠብቅ ደግሞ እኔ ብቻ ሳልሆን መጪዎቹ ቤተሰቦቼና ጓደኞቼም፣ ጎረቤትም፣መንግሥትም፣ ሌላው ታዛቢም ሁሉ ጠንቅቀው ያውቃሉ፡፡ ታዲያ መንግሥትን ያህል ትልቅ አካል እንደአንድ ተራ ምቀኛ የመንደር አውደልዳይ እጅግ ወርዶ “ልባሽ ጨርቅ ሳይቀር አንዲትም ውራጅ ይዛችሁ ብትገቡ ትነጠቃላችሁ” ብሎ ማወጅ ምን ይባላል? ምን ዓይነት የአስተሳሰብ ዝቅጠት ነው? በዚህ መልክ ስንትና ስንት ቆሻሻ መመርያና ደምብ ወጥቶ እየተተገበረ ይሆን?

 

አማራው ይጠንቀቅ፡፡ከእስካሁኑ የወደፊቱ ይብሳል፡፡ አቢይ እባብ መሆኑን ለመግለጽ ብዙ ጮኸናል፡፡ ለሥልጣኑና ለሰይጣናዊ ኢትዮጵያን በዘርና በሃይማኖት የማፈራረስ ተልእኮው ሲል የማያደርገው ነገር የለምና በተለይ አማራው ይህ ሰው ካዞረበት አንደርብ በአፋጣኝ ይውጣ፡፡ ወያኔ ከአብዛኛው የአማራ ክልል ብትወጣም ያላዳረሰችውን ክፍል እንድታዳርስና የዕልቂትና የውድመት “ትሩፋቷ” ላልደረሳቸው አማሮች እንዲደርስ የሆነ ድብቅ አጀንዳ ሊኖር ይችላልና በተለይ ወልቃይቶችና ጎንደር ጎጃሞች ተጠንቀቁ፡፡

 

ወያኔ ደብረ ብርሃንን ባለማጎሳቆሏ በኦሮሙማ መንደር የተፈጠረውን ንዴት አሳምሬ አውቃለሁ፡፡ ግን ደብረ ብርሃን እንዲደርሱ መፍቀድ አራት ኪሎንም ስለሚያሰጋ ሰውዬው ሄዶ ተቆጣቸውና በጨለማ ውልቅ እያሉ እንዲወጡ ተደረገ፤ በአጋጣሚውም የአማራ ፋኖና ሚሊሻ እንዲሁም ልዩ ኃይል በግርግር ጠላቱን ድባቅ ለመምታት ቻለ፡፡ ይህ ግን ገና ጅምር ነው አሁንም፡፡ ዋናው ጠላት አራት ኪሎና አዲስ አበባ አካባቢ መሽጓልና ኢትዮጵያውያን በተለይ በቀጣይ ወራት በእጅጉ ይጠንቀቁ፡፡

 

 ብአዴን ደግሞ አስጠቂ ነውና አትመኑት፡፡ ብአዴን ማለት በጠርሙስ ውስጥ ተረግዞ ቤተ ሙከራ ውስጥ የተወለደ የወያኔና ኦህዲድ ውህድ ጽንስ ነው፡፡ ሆድ እንጂ አእምሮ እንዲኖራቸው አልተፈቀደላቸውም፡፡ መጨረሻቸውም እንደጌቶቻቸው ነው፡፡

 

ኦሮሙማዎች በአማራ አንገት ቀና ማለት ይበሳጫሉ፡፡ የሽመልስ አብዲሣ ዝግ ንግግር ብዙ ነገር አሳውቆናል፡፡ እየሆነ ያለው ሁሉ የዚያ ንግግር መሬት ወርዶ የሚታዬው ግልባጩ/ቅጂው ነው፡፡

 

እርግጥ ነው፡-

 

እርግጥ ነው - አቢይ አህመድ ሀሽሽ ስለሆነ ብዙ ሰዎችን አስክሯቸዋል፤ በቁማቸው ገድሏቸዋል፡፡ ሀሽሽ በመሠረቱ ግዑዝ ነገር ነው፤ በመርፌ ወይም በጭስ መልክ እየተወሰደ የሚያሳብድ፡፡ አቢይ ግን ስሜትን የሚቆጣጠር ራሱ ሀሽሽ ነው፡፡ እርሱን የወሰደ ሰው መዳኛ የለውም፡፡ አቢይ የገባበት ሰው ከሀሽሽም በበለጠ ማንነቱንና ሰውነቱን ጥሎ ያብዳል ወይም እንደጣዖት ለሚያመልከው አቢይ ጨርቁን ጥሎ ክንፍ ይልለታል፤ ነፍሱን ስቶም ያብድለታል፡፡

 

የሴቶቹን እንተወው - በጣም ግልጽ ነውና፡፡ ብዙ ጨምላቆችን ስለታዘብንበት ሔዋን ትረፍበት፤ ትዘንበትም፡፡ ስንቱ ፍናፍንት ወንድ ተብዬም እየሆነ ያለውን እናውቃለንና እሱም ይቅር፡፡ እግዜር ፊቱን አዙሮለት ልጁን መልከ ቀና አድርጎ ፈጠረውና አዳሜ ተቸገረ - ለነገሩ በስንቱ ይበድለው፡፡ ተግባሩን ቀርቶ መልኩን የሚያየው በዛና እርሱ ራሱም ናርሲሳዊ ግለ-አምልኮት ውስጥ ገብቶ ሳይቀረቀር አልቀረም፤ በራስ ፍቅር ተጠምዶ እየዳከረ ይገኛል፡፡

 

በመሠረቱ ሊቀ ሣጥናኤልም እኮ በውበቱና በዕውቀቱ ከማንም ይበልጥ እንደነበር ድርሣናት ይመሰክራሉ፡፡ የአቢይ ዕውቀት ባለበት ይቀመጥና በውበቱ ግን ብዙዎችን እንዳነሆለለ አለመመስከር በጊዜው አገላለጽ ንፉግነት ነው፡፡ ነገር ግን ውበትንና የአስተዳደር ጥበብን አለመለየት የድንቁርናዎች ሁሉ ቁንጮ በመሆኑ የተበለሻሻችሁ ዜጎች በቶሎ ነፍስ ግዙ፡፡

ከዚህ በላይ ከተጠቀሰው ነጥብ አኳያ በተቃራኒው በአንዳንድ መጥፎ ምግባሮች የማይታሙ ስንትና ስንት ምሁራንና አክቲቨስት ተብዬዎች እንዲሁም አርቲስቶች እውነቱን እንዳያዩ በሀሽሹ አቢይ አንጎላቸው ተበክሎ እየሆኑ ያሉትን እያስተዋልን ነው፤ “ምን ነካቸው?” የሚል ጥያቄም ያጭራል፡፡አንዳንድ ነባር የሃይማት ሊቀ ሊቃውንትማ ሰውዬው ሃይማቱ ጴንጤ ሆኖ ተቸግረው እንጂ ገና ሳይሞት በቁሙ ጽላት አስቀርጸውለት “ቅዱስ አቢይ አህመድ” የሚል 45ኛ ታቦት ሊያደርጉትና ወር በገባ በ24ኛው ቀን ከአቡየ ጋር ደርበው ሊቀድሱት ሳይዳዳቸው አልቀረም፡፡ በውነት በርሱ ፍቅር ሙክክ ያላለ ሰው ማግኘት እኮ እየከበደን ነው፡፡ ምን ዓይነት አፍዝ አደንግዝ ነው ግን ያለው ጎበዝ!!

 

ዛሬስ ዛሬ ነው፡፡ መንጋም አይቀርም፡፡ እናም ምናልባት እነዚህ ወገኖቻችን ነገ በሀፍረት ተሸማቀው ራሳቸውን የሚያጠፉ ሊኖሩ እንደሚችሉ ከወዲሁ መገመት አይከብድምና ለነሱም እንጸልይላቸው፡፡ ነገ ሌላ ቀን ነውና እነዚህ ምስኪን ወገኖቻችን ወደ “rehabilitation centers” ገብተው ከዚህ ሀሽሽ እንዲገላገሉ ብዙ ሥራ ይጠበቅብናል፡፡ሀሽሽ ምክንያትንና ምክንያታዊነትን የሚያጠፋ ትልቁ የዓለማችን ደዌ ነው፡፡ እንጠንቀቀው ውድ ምዕመናን!!

 

ወደድንም ጠላንም ኢትዮጵያ ታሸንፋለች፤ አጭበርባሪና አስመሳዮችም ይህችን ጨለማ አያልፏትም!!