Friday, June 25, 2021

ብስራት አማረ ማን ነው? ከ ጌታቸው ረዳ (Ethiopian Semay) 6/25/2021

 

 

ብስራት አማረ ማን ነው?

ከ ጌታቸው ረዳ

(Ethiopian Semay)

6/25/2021

ወደ እማጫውታችሁ ሰነድ ለምን እንደገባሁ ምክንያቱን ላስተዋውቃችሁ። ብስራት አማረ ማለት በዚህ አስገራሚ የወንጀል ሰነድ የተገለጸ የወያነ ትግራይ የጸጥታ፤ የስለላ እና የሓለዋ ወያነ (እስርቤቶች) ዋና ሓላፊ የነበረ ሰው ነው። ትውልዱ የቀኛዝማች አማረ ልጅ “ዓዴት- አክሱም”-ነው።

 ዛሬ የሚኖሮው “በሰሜን አሜሪካ” ኦሃዮ ውስጥ ነው። ባለፈው ሰሞን Teddy press ተብሎ በሚጠራ የወያኔዎች ቱልቱላ የሆነ ኤርትራዊ ዩቱብ ሚዲያ ላይ “ፖለቲካዊን ወተሃደራዊን ምዕባሌታት ቀርኒ ኣፍሪቃ” (ፖለቲካዊና ወታደራዊ ሁኔታዎች በአፍሪቃ ቀንድ) በሚል ርዕስ ለማነጋገር ጋብዞት ነበር። ያደመጥኩት ገና ዛሬ ነው። በዛው ውይይቱ እንደማንኛቸውም የተማረው የትግራይ “Herd mentality” እርሱም በለመደበት የአማራ ማሕበረሰብ ጥላቻውና “በመጽሐፉም አሳትሞ በገለጸው መሰረት” እዚህ ቃለ መጠይቅም የአማራ ስም ካላነሱ ‘ሆድ ቁርጠት’ የሚይዛቸው እንደሚሰማቸው እንደ ማንኛቸውም የትግራይ ምሁራን ሁሉ ብስራትም እንደለመደው ዛሬም “አማራዎች እንኳን ሊገዙህ አብረውህ ለመኖርም አስቸጋሪዎች ናቸው” ሲሉ ኤርትራ ነፃነት ከመሰረቱት አንዱ ከሆኑት አክሱማዊው ኤርትራዊ ‘ወልደአብ ውልደማርያም’ እንዳሉት ሁሉ እያለ “አማራዎች ጋር” መኖር እንደማይቻል የገለጸበት ጥላቻው እና አማራው ትግራይ ውስጥ “የኮሰቦ ጦርነት” እያካሄደ እንደሆነ ከዚያው ጋር እያመሳሰለ ሳደምጠው እጅግ ገረመኝ እና ይህ ሰው ዛሬም ካለፈው ጥላቻው እንዳልተማረ ስገነዘብ፤ እነሆ ብስራት አማረ ማን መሆኑን ላስተዋውቃችሁ ፈለግኩ።

ወዳጄ ገብረመድህን አርአያ እኔ ዓዲ አቡን (ቡሎኮ) ዓድዋ እያለሁ ከጓደኛው ተኽሉ ሓዋዝ ጋር ትውውቅ ስለነበረን አንድ ቀን ስለ ተክሉ ሓዋዝ አሳዛኝ አገዳደል አንስቶ አጫውቶኝ ስለነበር፤ ይህንን በጽሑፍ መልክ ጻፈው ብየው በዚህ ተስማምተን ስለነበር፤ አጋጣሚውን አግኝቼ አዲስ መጽሐፍ ለመጻፍ እያሰብኩኝ እንደሆነ ሳማክረው “የትግራይ ብሔተረኞች በአማራ ላይ ያላቸው ጥላቻ ከምን የመነጨ ነው?” በሚባለው መጽሐፌ ውስጥ እንዲካተት በቃል ያጫወተኝን በጽሑፍ እንዲሰነድ ጠይቄው እስክጽፈው ድረስ ጠብቀኝ ብሎኝ ፤ ጽፎ ልኮልኝ በመጽሐፌ ውስጥ አብሮ ከታተመው ያሳተምኩት አስገራሚ ሰነድ እነሆ አንብቡት። ስለ ተክሉ ሓዋዝ እና ብስራት አማረ በቃሉ ያጫወተኝን ያሳተምኩትን ሰነድ መጽሐፌ ውስጥ በገጽ መጣበብ ምክንያት ተቆርጠው የቀሩ ታሪኮች ስለነበሩ እዚህ ውስጥ ተካትተዋል።

ጌታቸው እንደምን አለህ?

ስለ ተክሉ ሓዋዝ እና የመሳሰሉ ታታሪኮች በተነጋገርነው መሰረት በጽሑፍ ልኬልሃለሁ እነሆ።

ተክሉ ሃዋዝ የተ.ሓ.ህ.ት. ማ/ኮሚቴና የድረጅቱ የደህንነት ዋና ሃላፊ ሆኖ እስከ 1977 ቆይቷል። እኔና ተክሉ ሃዋዝ ከልጅነታችን ጀምሮ የጠበቀ ጓደኝነት የነበረን አብሮ አደግ ስንሆን፤ በትግሉም ወቅት ሁሉም ታጋይ የሚያውቀው የቅርብ ግንኙነትና በጣም እንደምንዋደድ አመራሩም ያውቃል፤ በትግሉ በዚሁ የወጣን ነን።

በ1976 ተምቤን አብይ አዲ ተገኘተን ስንጫወት የዱሮ ትዝታ በማንሳት እነ ይህደጎ ዝብሎ፤ አብርሃ ሃጎስ፤... ስናነሳ እነዚህ በደርግ ቀይ ሽብር ተገደሉ በማለት ስንነጋገር ቆየን። ተክሉ ሃዋዝ ቀበል አድርጎ እንዴት እንደተገደሉ አጫውትሃለሁ፤ ከባድ ምስጢር አለው፤ ተጠንቀቅ አለኝ። እኔም ምን አገባኝ ብየ ነው ከሌላ ሰው ጋር የምነጋገርበት አልኩት። በዚህ ጊዜ አንድ በአንድ በምን መልኩ የተ.ሓ.ህ.ት. አመራር ቀይ ሽብርን እንደተጠቀመበትና ከ80% በላይ የትግራይ ዜጎችን እንዳስገደሉ እንደሚከተለው አድርጎ ነገረኝ።

እነ አብርሃ ሃጎስ ብቻ ሳይሆኑ ብዙ የኢ.ህ.አ.ፓ. አባላት፤ የግንባር ገድሊ ሓርነት ትግራይ (ግ.ገ.ሓ.ት.) ፤ ጸረ-ተ.ሓ.ህ.ት. የሆኑትን ጨምሮ በአዲስ አበባ፤ ጎንደር፤ ወሎ፤ ወዘተ በእጅ አዙር ሁሉንም በደርግ ቀይ ሽብር አስገድለናል። አዲስ አበባ ብቻ ከአርባ በላይ ተገድለዋል። በትግራይ ሁሉንም ጸረ-ተ.ሓ.ህ. ት፤ ኢ.ህ.አ. ፓ፤ ግ.ገ.ዳ. ትን አስገድለናል።

በፖለቲካ ጽ/ቤት ሁሉም አመራር በመስማማት ስብሃት ነጋ፤ መለስ ዜናዊ፤ አባይ ፀሃየ ሃለፊነቱን ወስደው የሚገደሉትን ስም ዝርዝር ተከፋፍለው በመያዝ ደብዳቤ በትግርኛ እየተጻፈ የተ.ሓ.ህ.ት. አርማ ባለበት ወረቀት በግርጌው ማህትም እያረፈበት እንዲበተን እና በደርግ እጅ እንዲገባ በማድረግ እቅዱ እንደተጠናቀቀ ነገረኝ። የደብዳቤው አጻጻፍ በትግርኛ፤

የተ.ሓ.ህ.ት. አርማ

ወር ቀን ዓ.ም.

ነብ ብፃይ አብርሃ ህጎስ

አቐዲምና በሽም ቃልሲ ህዝቢ ትግራይን ተ.ሓ.ህ.ት. ዝደምቐ ሰላምታ ነቕርቦልካ።

ቃልሲ ህዝቢ ትግራይ ኣብ ልዕሊ ፀላኢ ህዝቢ ትግራይ ገዛእቲ ኣምሓሩ ገፊሕ ዓወት እንዳመዝገበ አብ ዓወት ልእሊ ዓወት ይጎናፀፍ ኣሎ።

ንሰኻን ዝኣምሰሉ ተቓለስቲ ብትህቡና ዘለኹም ሓበሬታን ደግፍን ንዝካየድ ዘሎ ቃልሲ ዓብይ አሳልጦ ዘብርክት ዘሎ መኳኑ እንዳገለፅና በርትዑ እንደበልና ሓደራ ንብለኩም።

ማህተም ተ.ሓ.ህ.ት.

ፊርማ

መለስ

ከላይ የተጻፈው ደብዳቤ ወደ አማርኛ ሲተረጎም እንዲህ ይላል።

ክብ አርማ ተ.ሓ.ህ.ት.

ወር ቀን ዓ.ም.

ለጓድ አብርሃ ሃጎስ

አስቀስድመን በትግራይ ህዝብና በተ.ሓ.ህ.ት. ስም የደመቀ ሰላምታችንን እናቀርብልሃለን።

የትግራይ ህዝብ ትግል በደመኛው ጠላት በአማራው አገዛዝ ሰፊ ድል በማስመዝገብ ከድል ወደ ድል እየተሸጋገረ ይገኛል።

እናንተና እንዳንተ የመሰሉ ታጋዮች በምትሰጡን ጥቆማና ሰፊ ድጋፍ ለምናካሂደው ትግል ትልቅ እመርታ እያበረከተ መሆኑን እየገለጽን በርቱ እያልን አደራ እንላለን።

ክብ ማህተም

ተ.ሓ.ህ.ት. ክብ አርማ

ፊርማ

መለስ

በዚህ መልክ እየተጻፈና በፓስታ እየታሸገ፤ በፓስታው ላይም የተ.ሓ.ህ.ት. ክብ ማሀትም እያረፈበት ከተዘጋጀ በኋላ ለተክሉ ሃዋዝ በመስጠት፤ በምስጢራዊ የድርጅት አባላት አዲስ አበባ በመላክ ሰዎቹ በሚኖሩበት ፖሊስ ጣቢያ አካባቢ እየተጣለ ወደ ደርግ ደህንነት አባላት ቢሮም ሆነ በግልና በምስጢር በሚቻለው ሁሉ እጃቸውን በማስገባት ሁሉም ተይዘው እንዲታሰሩና የቀይ ሽብር ሰለባ እንዲሆኑ የተደረገበትን ምስጢር ነገረኝ። እነማን እንደተገደሉና የሰዎቹን ስም ዝርዝር ነገረኝ። በጊዜ ብዛት የሁሉንም ስም ለማስታወስ ባልችልም፤ የትምህርት ቤት ጓደኞቼን ግን አስታውሳለሁ፤ እነሱም፤ ኃ/ሥለሴ መስፍን፤ አብርሃ ሃጎስ፤ ይህደጎ ዝበሎ፤ ልኡል ሥዩም፤ ፍስሃ ገዛኸኝ፤ ታረቀ ብርሃነ፤ ገ/ዝጊሄር ጠረጋ፤ ዮሃንስ ተ/ሃይማኖት (የግ.ገ.ሓ.ት. አባል የነበረ) ፤ ስለሺ መኮንን (የኢ.ህ.አ.ፓ. አባል የነበረ) ከነገረኝ መካከል ይገኙበታል።

ረጋ በማለትም ስለ ወልደሥላሴ ግርማይ በዚህ በኩል የነበረውን ሚና ስጠይቀው ከሰጠኝ ሃሳብ፤ አዲስ አበባ ውስጥ የተገደሉት በወልደሥላሴ እንቅስቃሴ እንደ ነበር ገልጦልኛል። አዲስ አበባን መግቢያና መውጫውን አጠናቆ ያውቃል። እነዚህ ከአርባ በላይ የተገደሉትን የሁሉም ደብዳቤ የተሰጠው ለእርሱ ነበር። በዛን ጊዜ የደርግ ከፍተኛ ካድሬ ሆኖ ከተማረ በኋላ ወደ በረሃ እንዲመጣ ያደርግሁት እኔ ነኝ። የደህንነት ቢሮ በየፖሊስ ጣቢያው አካባቢ እንዲገደሉ የተፈለጉትን ሁሉ መኖሪያ ቤታቸውን እንዲያጠና አስቀድመን ነግረነው ስለነበር ሁሉንም በተሳካ ሁኔታ ስለሰራነው በሙሉ ተገድለው ደርግ በተለያዩ ቦታ አስፋልት ላይ ዘረጋቸው።

ትግራይ ውስጥም በተሳካ ሁኔታ ደርግ ተጠራጥሮ ከገደላቸው ከፍተኛ ቁጥር ያለው በስምንቱ አውራጃዎች በደርግ እጅ እንዲገደሉ አደረግን። በጎንደርና በወሎም ተመሳሳይ ደብዳቤ እየጻፍን በየመንገዱ ጥለን ወረቀቱ በፖሊስና ደህንነት እጅ ገብቶ ሁሉም ጠባብ ብሄረተኛ እየተባሉ የፍየል ወጠጤ ተዚሞላቸው ተገድለው በየመንገዱ ተዘረጉ። በቀይ ሽብር ጊዜ ተጠቃሚ የሆነው ተ.ሓ.ህ.ት. ነበረ በማለት ምስጢሩን ሁሉ ነገረኝ።

በመጨረሻም ስለ አስመላሽ አሳየኸኝ ግድያ ጠየቅሁት። አስመላሽ አሳየኸኝን የገደሉት አረጋዊ በርሄ፤ ስብሃት ነጋና መለስ ዜናዊ ናቸው። በቀይ ሽብር በእጅ አዙር ያሰገድልናቸው፤ በመጀመሪያ ደሴ ከተማ ለስራ ጉዳይ እንደነበረ የነ ኃ/ሥላሴ መስፍን እና ሌሎችም መገደላቸው እንደተሰማ ከደሴ ተነስቶ አዲስ አበባ በመሄድ ወ/ሥላሴ ግርማይን አግኝቶ ተ.ሓ.ህ.ት. እንዳስገደላቸው በግልጽ ነገረው። አስመላሽ የዚሁ አካባቢ የተ.ሓ.ህ.ት. የሕዝብ ግንኙነት የበላይ የከተማዎች ሰላይ ስለነበር ተደናግጦ ከአዲስ አበባ ተነስቶ አድዋ ድረስ በመምጣት ለአረጋዊ በርሄና ስብሃት ነጋ በየግል አድራሻቸው ደብዳቤ በመጻፍ ንጹሃን የትግራይ ዜጎችን ካለምንም ጥፋታቸው የቀይ ሽብር ሰለባ ስላደረግናቸው፤ ይህ ድርጊት በአስቸኳይ አቁሙት፤ ነገ በወንጄል ያስጠይቀናል ብሎ ጻፈላቸው። ደብዳቤውን ተቀብልው ካነበቡት በኋላ ለሁለት ዓመት ያህል ደብቀውት ቆዩ። በዚህ የተነሳ ያጋልጠናል ብለው ከፍተኛ ስጋት አድሮባቸው ነበር፤ እስከ አሁንም ይደነግጣሉ። አስመላሽ አሳየኸኝ (ወዲ ምህረት) የተደረገውን ያውቃል። እሱ የማያውቀው ምስጢር የለም። ከዚህ ተነስተው 1972 መቀሌ አካባቢ አስጠርተው ዓዲ በቕሉ፤ ሓለዋ ወያነ ተረሸነ፤ አንተም ታውቀዋለህ አለኝ። በትክክልም እንደ ተክሉ ሃዋዝ አገላለጽ የተገደለው ዓዲበቅሎ ነው። በኋላ በሰፊው እገልጠዋለሁ።

እነዚህ የቀይ ሽብር ሰላባ ያደርግናቸው ወገኖች ደብዳቤው በኔ በኩል በመላኩ ጥፋት መፈጸሜን አሁን ተረዳሁት። ተቀብዬ ላቃጥለው እችል ነበር። ግን አላደረግሁትም። በትግራይ ውስጥም ያ ሁሉ ተማሪና የተማረ ወገን በተ.ሓ.ህ.ት. ጠላትነት ፈርጀን አስገደልናቸው። ይህ የኔ ጥፋት ነው አለኝ።

በየከተማው አውራጃዎች የተፈጸሙት የሽብር ጥቃቶች በብስራት አማረ ሃላፊነት፤ ስምሪትና መሪነት ነው። ብስራት አማረ ከኔ ቀጥሎ የስለላና አፋኝ ቡድን ሃላፊ ነው። ትእግስት አሰፋ፤ አክሊሉ፤ ልኡል በርሄ፤ አሰፋ መርአዊ (ጉሬዛ)፤ ነጻነት ሰንደቕ ወዘተን በማሰማራት በአድዋ፤ ገብረዝጊ አለማየሁ፤ ቢተው ብርሃን፤ አብርሃ አበራ ወዘተ አስገደልኩ። አድዋ ሁለት ጊዜ፤ መቀሌ ሁለት ጊዜ የሽብር ጥቃት በማድረግ ገድለናል። ወቅሮ፤ ሽሬ፤ አክሱም፤ አዲግራት፤ ራያ፤ ማይጨው፤ እንትጮ፤ በዚሁ የሽብር ጥቃት ያለፈው ሕይወት ቁጥር የለውም። ይህ ሁሉ በኔ መሪነት የተፈጸመ ነው አለኝ። በዛን ጊዜ የተ.ሓ.ህ.ት. መሪዎች ተክሉ (ወዲሃዋዝ) እያሱ ሲያሞካሹኝ የነበሩ አሁን ፊታቸውን እያዞሩብኝ ይገኛሉ። ከሁሉም የሚገርመኝ አረጋሽ አዳነም የነሱ ደጋፊ ሆና ስንገናኝ፤ እንደምነህ ተክሉ ሃዋዝ፤ ብላ ፊቷን ታዞራለች ብሎ በመረረ አነጋገር ገለጠልኝ።

በትክክልም በብስራት አማረና በተክሉ ሃዋዝ ያልተፈጸሙ ድርጊቶች የሉም። ብዙ ጥፋትና ወንጀል የፈጸሙ ሰዎች ናቸው። ትግራይ ውስጥ በተክሉ ሃዋዝና በብስራት አማረ እንዲሁም በመሪዎቹ ያልተማረረና ያላለቀሰ ይገኛል ማለት ዘበት ነው።

ከቀይ ሽብር ሰለባ ያመለጡት፤ አስፋው ወ/አረጋይ፤ ቀ/ኛ ተክሊት መኮንን፤ አለምሰገድ ገብረእግዚአብሄር፤ ገብረኪዳን ደስታ ሲሆኑ፤ አስፋው ወ/አረጋይ ቤተሰቡን ሊጠይቅ ወደ አድዋ በመሄድ ከዚያም ወደ ትውልድ ወረዳው ይሃ እንደመጣ በብስራት አማረና አሰፋ ጉሬዛ ታፍኖ ተወስዶ በተ.ሓ.ህ.ት. አመራር በለሳ ማይሃማቶ ወስጥ በጥይት ተደብድቦ ሃለዋ ወያነ ውስጥ ተገደለ። ብስራት አማረ የገደላቸው በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ናቸው። ቀ/ኛ ትክሊት መኮንን በተመሳሳይ ሁኔታ አድዋ፤ ፈረስ ማይ ወረዳ በተ.ሓ.ህ.ት. ተይዘው ሃለዋ ወያነ ውስጥ በማስገባት ሊገደሉ ሲሉ፤ የ80 ዓመት አዛውንት ነኝ፤ አትግደሉኝ፤ የምትፈልጉትን የነብስ ማዳኛ ክፍያ ልክፈልና ልውጣ በማለት በአመራሩ ብር 40,000 ክፈሉ ከተባሉ በኋላ፤ ያላቸውን እና ያፈሩት ሃብታቸው ተሽጦ ብር 37,000 ከፍለው ወጡ። አፍኖ ያመጣቸው ብስራት አማረ ነበር። ብስራት ስንት አዛውንትና ወጣቶችን የገደለ ግለሰብ ነው።

አለምሰገድ ገ/እግዚአብሄር ከደርግ ቀይ ሽብር ሰለባ አምልጦ ወደ ትግራይ በረሃ በመግባት ከተ.ሓ.ህ.ት. ተቀላቅሎ ሂስ በማካሄድ ትንሽ ከቆየ በኋላ ሃለዋ ወያነ እንደላኩት ከዛው አምልጦ ሱዳን ገብቶ አሁን አውሮፓ የሚኖር ግለሰብ ገልጦልኛል።

ገብረኪዳን ተስፋይ ከማ.ገ.ብ.ት. በተሰጠው ፍቃድ ትግራይ ውስጥ እየሰራ በነበረበት ጊዜ በስህተት የተጻፈለትን ደብዳቤ ወሬ በማግኘቱ ከተ.ሓ.ህ.ት. በረሃ እንደተደባለቀ በ1972 ተመልሰህ ከተማ ግባ ተብሎ የተ.ሓ.ህ.ት. ስራውን ቀጠለ። ከዚህ ኑዛዜ በኋላ ተክሉ ሃዋዝ እያለቀሰ ተያይዘን ወደ ጎምባስ ሞሞና ሄድን።

አስመላሽ አሳየኸኝን አዴት አገኘሁት?

ዓዴት ውስጥ ዓዲ በቕሊ የዘለዓለም መኖሪያው የጠራቺውን አስመላሽ አሳየኸኝን ያገኘሁት በ1972 አጋማሽ ነበር። እኔ ለስራ ወደ ሽራሮ ለመሄድ ወርዒ ቆላ ቁልቁሉ ዳገቱን ለመወጣት ብዙ ሰአታት ስለሚጨርስ ወደ ማታው ጂራ የምትባል ትንሽ ቁሽት ከኔም ጋር ሁለት የታጠቁ ታጋዮች ስላሉኝ ጂራ አድረን ከዚሁ ተነስተን ረፋዱ ላይ ዓዴት ስንገባ አስመላሽ አሳየኸኝ ከርቀት እየሮጠ ደረሰና አቅፎ ሳመኝ። መቸ መጣህ ስለው አምስት ቀኔ ነው አለኝ። ለምን መጣህ ስለው፤ ስብሃት ነጋ በጣም ስለምፈለግህ ዓዴት ጠብቀኝ ብሎ ላከብኝ፤ ነገ ወይም ከነገ ወዲያ እዚህ ይመጣል አለኝ። ከዛም ወሬ ጀመርን። በርካታ ገንዘብ ከአባላት አሰባስቦ እንደመጣም ነገረኝ። በፊቱ ላይ ምንም ጭንቀት አይታይበትም፤ ደስተኛ ሆኖ እየሳቀ ነበር። ስንጫወት እዚህ አካባቢ ክፍሎች አሉ? ብሎ ሲጠይቀኝ ደጅ እንሁን አልኩት። ከፊታችን የሚታየው ረባዳ መሬት ዓዲ በቕሊ ይባላል። በዚሁ ወሰን በፊታችን የሚታየው ፎቅ ቆርቆሮ አጠገቡ 03 ህክምና አለ። ዶ/ር አባዲም እዚሁ አለ። በእጄ እያመለከትኩት ከህክምናው በስተደቡብ የሚታይህ ወደ ውስጥ የገባው መሬት 06 ሓለዋ ወያነ በአለምሰገድ ኢንቺ የሚመራ ብዙ እስረኞች ያሉበት ነው፤ ከህክምናው ከ15-20 ደቂቃ ይወስዳል። ሁለቱም እዛው አሉ። አሁን ያለንበት ቤት ደግሞ 05 ክፍሊ ኢኮኖሚ ጨንፈር ነው ብየ ነገርኩት። አምስት ሰዓት ያህል አብረን ቆይተን አረጋሽ አዳነም እዛው ስለነበረች እሷንም እሱንም ተሰናብቼ ጉዞዬን ወደ ሽራሮ ቀጠልኩ።

ከአንድ ወር በኋላ ዓዴት ደርሼ ዓዲ በቕሊ በቀኑ ህክምና ክፍል ስገባ በአጋጣሚ አበበ ዘሚካኤል የ06 ሓለዋ ወያነ የዓዲ በቕሊ ምክትል ሃላፊው ከዶ/ር አባዲ ጋር ሲጫወት አገኘሁት። የመጣው በእነሱ አካባቢ የቤተ ክርስቲያን ዓመቱ ስለነበረ ኗሪው ከየቤቱ ያመጣላቸው ጠላና ምግብ ስለነበር አብረው ምሳ ለመብላት ሊጠራው እንደመጣ፤ እኔም በአጋጣሚ ስለገባሁ እንሂድ አለኝ። ዶ/ር አባዲ ትንሽ የህክምና ስራ ስለነበረው እናንተ ሂዱ፤ እኔም ከግማሽ ሰዓት በኋላ እደርሳልሁ አለ። እኔና አበበ ዘሚካኤል ተያይዘን ወደ ሃለዋ ወያነ ስንሄድ፤ በመንገድ ላይ እንዳለን አስመላሽ አሳየኸኝ፤ በአቦይ ስብሃት ነጋ ትእዛዝ፤ በምርመራ አለምሰገድ ኢንቺን አሰቃይቶ እንዲገድል፤ ሲረሽንም ስብሃት ቆሞ እንዳየና በጥይት እንዳስደበደበው፤ በተጨማሪም ስብሃት የታጠቀውን ሽጉጥ አውጥቶ እንደመታውና ብዙ ጥይት አርከፍክፈንበት ገድለነው ሲለኝ ከባድ ሃዘን ተሰማኝ።

አስመላሽ አሳየኸኝ ጠንካራ ሰው ስለሆነና ለድርጅቱ እድገትም ሰፊ አስተዋጽኦ ያበረከተ እንዴት ይገደላል አልኩት? የሰጠኝ መልስ፤ በቀይ ሽብር ጊዜ በተ.ሓ.ህ.ት. የሃሰት ወረቀት እየተበተነ ብዙ ሰው ተገድሏል አልኩት። የሰጠኝ መልስ በቀይ ሽብር ጊዜ በተ.ሓ.ህ.ት. ወረቀት እየተበተነ የተገደለ ብዙ ነው። አስመላሽ የተገደለበት ምክንያትም የተቃውሞ ደብዳቤ ለአረጋዊና ለስብሃት ልኮ ነበር። በዚህ ምክንያት ነው የተገደለው አለኝ። እጁን ለደርግ ከሰጠ ያጋልጠናል ብለው ስለፈሩ በከንቱ ገደሉት አለኝ።

ትንሽ ቆየት ብሎም የአለምሰገድ ኢንቺን መገደልና ብዙ እስረኞች ማምለጣቸውን ነገረኝ። እንዴት ስለው? አንዲት ወጣት የአድዋ ንግሥት ሳባ ሁለተኛ ደረጃ ተማሪ የነበረች ብስራት አማረ አፍኖ በማውጣት የደርግ አደገኛ ሰላይ ናት ብሎ ባቀረበው ሪፖርት መሰረት እዚህ አዲበቕሎ ሃለዋ ወያነ ላካት። አለምሰገድ ኢንቺ በምርመራ በእሳትና በድብደባ ሲያሰቃያት በእጁ ላይ እንዳለች ሞተች። ቅበሯት ብለን በተቀበረች በነጋታው አንድ ከሽሬ ተይዘው የመጡ በመካከለኛ እድሜ የሚገኙ ሴት አለምሰገድ ሲመረምራቸው በእሳትና በፈላ ውሃ ሲቃጠሉ እሳቸውም ሞቱ። ከትንሽ ሰዓታት በኋላ እንደተለመደው ተቀበሩ። ይህ ሁሉ ሰቆቃ ሲፈጸም ሁል ጊዜ እየተከታተሉ አምስት ነባር ታጋዮች ተማክረው አለምሰገድ ኢንቺን ሲያገኙት ገደሉት። ሞት የተፈረደባቸው ታጋዮችና ሲቪል ሰላማዊ ዜጎች አባይ፤ ስብሃት፤ አስመላሽ አሳየኸኝን (ወዲምህረት) ለመግደል በመጣ ወደ 400 የሚጠጉ ሞት የተፈርደባቸውን አስወጥተው ለመሄድ ሳምንት ሙሉ ሁሉን አስተካክለው ከጨረሱ በኋላ አለምሰገድን እና ሌሎች ሶስት ታጋዮችን ገድለው ሁሉም እስረኛ በሩን ከፍተውት ስለቆዩ አስወጥተው አመለጡ። ይህን ተግባር የፈጸሙት ልክ ከማታው 12 ሰዓት ነበር። ወዲህ ወዲያ ስንልም መሸ። የበረሃውን መንገድ ስለሚያውቁት፤ ጨለማን ተገን በማድረግ ሌሊቱን ሙሉ ተጉዘው ዛና ወረዳን ወደ ቀኝ በመተው ግመሎ ተብሎ በሚጠራ ቦታ ሽሬ እንዳሥላሴ አጠገብ ገቡ። ሲቪሎቹ በቀጥታ ከተማ ገብተው እንዳመለከቱ ፖሊስና ጦር ሰራዊት መጥቶ ሁሉንም ታጋዮች ሰብስቦ ወደ ደህንነት ቢሮ በመውሰድ ልብስ አልብሰው፤ ጫማ ገዝተው አንድ ወር ካቆዩአቸው በኋላ ሁሉንም በአይሮፕላን ወደ የቦታው በተኗቸው በማለት እየተከዘ አጫወተኝ።

ሓለዋ ወያነ ገብተን ዶ/ር አባዲም መጥቶ ስለነበር በልተን ተመልሰን ስንሄድ ዶ/ር አባዲ አበበ ምን ነገረህ ብሎ ጠየቀኝ። የነገረኝን ሁሉ ስነግረው እኔንም ይህንኑ ነበር ያጫወተኝ አለኝ። ይህ ሁሉ የወረደባቸው የአስመላሽ (ወዲምህረት) መሰቃየት ነው። ስላገለገላቸው ሽማግሌው ስብሃት የሞተው ሰው እንዳይነሳ ፈርቶ የሽጉጥ ጥይት አርከፈከፈበት ተባብለን ወደ ህክምናችን ገባን።

ከዚያ በኋላ ዓዲበቕሎ ሓለዋ ወያነ ተነስቶ ግማሹ ወደ ወርዒ ወርዶ ቀድሞ ወደነበረበት ሓለዋ ወያነ ሲገባ፤ ግማሹ ደግሞ ዓዲ መሃመዳይ  መስሪያ ቤት ሰርቶ ገባ።

በእነዚህ ስፍራዎች በሃላፊነት የተሾሙት፤ ዓዲ መሃመዳይ አበበ ዘሚካኤል፤ ወርዒ  ዘአማኑኤል ለገሰ (ወዲሻምበል) ናቸው።

ተክሉን ስለ ብስራት አማረ ወንጄል ለማወቅ ጉጉት ስለነበርኝ ጠየቅሁት። ብስራት፤ እንደምታውቀው፤ በዚህ ድርጅት ውስጥ በሰው ደም የተጨማለቀ ነው። በስንት ሺህ የሚቆጠሩ ግለሰቦችን አፍኖ በማስወጣት ብዙ ሺህ ንጹሃንን በሰቆቃ የገደለ ነው። ከዛላንበሳ እድሜአቸው 12 የማይሞላ 5 ህጻናትን አፍኖ በማስወጣት የደርግ ሰላይ ናቸው ብሎ ለአውአሎም ወልዱ ሪፖርት አቅርቦ አውአሎም ይገደሉ ብሎ ስለፈረደባቸው በድሊዊ አስገድሏቸዋል። ብስራት አማረ ከመለስ፤ ከአረጋዊና ከስብሃት ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት አለው። ብስራት ብዙ ከባድ ወንጄሎችን የፈጸመ ግፈኛ ነው። ስለ አበበ ተ/ሃይማኖትም ስጠይቀው እሱም የስንት ሺህ ሕይወት የቀጠፈ ግለሰብ ነው አለኝ።

 ቀጠል አድርጎም፤ ብስራት አማረ እስከ በሴት ማሕጸን የጋለ ብረት በማስገባትና በማሰቃየት የገደለ ወንጀለኛ ነው አለኝ።”

ሲል ወዳጄ ገብረመድህን ተኽሉ ሓዋዝ ያጫወተውን አጫወተኝ። ብስራት ዛሬ ይህ ሁሉ ጉድ ተሸክሞ አፉን ሲከፍት መስማት ብስራትን ሳይሆን የናቅኩት ውጭ አገር ያለው የሕግ ምሁር ኢትዮጵያዊና እሱን ተሸክማ እየኖረች ያለቺውን መሬት ረገምኳት።

ዛሬም “ሼር” ማድረግ አይክበዳችሁ።

አመሰግናለሁ

ጌታቸው ረዳ (Ethiopian Semay)