Thursday, December 26, 2019

የፋሽዝም አነሳስ (አገሬ አዲስ) (ETHIO SEMAY) ታህሳስ 16 ቀን 2012 ዓም( 26-12-2019)


የፋሽዝም አነሳስ
ለዱላ ምስጋና ይግባው!
ታህሳስ 16 ቀን 2012 ዓም( 26-12-2019)
(ETHIO SEMAY)
የአሸባሪነትና የፈላጭ ቆራጭነት ምልክትና  መብት
ፋሽዝም የሚለው ቃል ፋሽዎ ከሚለው የጣልያን ቃል የመጣ ሲሆን ትርጉሙም ፋስ ወይም መጥረቢያ(ጥልቆ)ማለት ነው።ጥንት በሮማንያን ዘመን ቀጫጭን ዱላዎች በጠፍር (በገመድ) ዙሪያውን ታስረው በመካከላቸው ያለውን ፋስ የተሰካበትን ወፍራም ዱላ ከበውና አጅበው የሚታዮበት አርማ በመፍጠር ቅጣትና ፈላጭ ቆራጭነትን የሚገልጹበት ምልክት ነበር።ይህንን ተከትሎ የሞሶሊኒ ፋሽስታዊ እንቅስቃሴ አርማው አድርጎ ወሰደው።ይህንኑ አርማና ዱላ የተሸከሙት ተከታዮቹ በሕዝቡ ላይ ሽብርና ኢስብአዊ ግፍ እንዲፈጽሙ ነጻነት ሰጣቸው፤ሞሲሊኒም የተፈራ መሪ እንዲሆን እረዳው።

የእንግሊዝኛው መዝገበቃላት ወይም ጎግል ሲያብራራው እንዲህ ይለዋል “The original symbol of Fascism,in Italy under Benito Mussolini was the Fasces.This is an ancient Roman Symbol of power carried by lictors.A bundle of sticks featuring an Axe,indicating the power of life and death.”

የፋሽዝም አነሳስ ከቤኒቶ ሞሶሊኒ ጋር የተያያዘ ሲሆን ፖለቲከኞች ከሁሉም ጊዜ የከፋ ፋሽዝም ይሉታል። የመጀመሪያው ዓለም ጦርነት ዘማችና የማርክሲዝም/ኮሚኒዝም ጋዜጣ አዘጋጅ የነበረው ሞሶሎኒ (1883-1945) ከሶሻሊስቶች ካምፕ ተገንጥሎ በ1919 የራሱን እንቅስቃሴ ጀመረ።ፋሲ ዲ ኮምባቲሜንቶ (Fasi di combatimento)የሚለውን የ19ኛውን ዘመን የጣሊያን አርሶ አደሮችን/ ገበሬዎችን አብዮታዊ እንቅስቃሴ በጣልያን ሰሜናዊ ግዛት በሚላኖ መሠረተ።ይህንን እንቅስቃሴ በመምራት በኦክቶበር ወር 1922 እአአ መጀመሪያ ላይ  ባደረገው የቅስቀሳ ዲስኩር ሥልጣኑን በውድ ወይም በግድ እንወስዳለን በሚል መፈክር በተከታዮቹ ቀናት  ወደ ሮም ከተማ ጉዞ በማድረግ በጊዜው ከነበረው ንጉሥ አማኑኤል ሁለተኛ ፊት ቀረበ።ንጉሱም የሞሶሊኒን አጃቢ በመፍራት አዲስ መንግሥት እንዲያቋቁም ጠዬቀው።

ሞሶሊኒም ጥያቄውን ተቀብሎ በሰላሳ ዘጠኝ ዓመት ዕድሜው በኦክቶበር 29 ቀን 1922 ዓም የጣልያን  የመጀመሪያው ወጣት ጠ/ሚኒስትር ሆኖ የመንግሥቱን ሥልጣን ተረከበ።በርዕዩተዓለም ላይ የተነደፈ  ፕሮግራምና በተግባር የዳበረ የፖለቲካ ድርጅት ሳይኖረው በባዶ የተስፋ ቃላትና የጥላቻ መልእክት ሰክረው በደም ፍላት የሚሰግሩ ጥቁር ሸሚዝ በለበሱ፣ዱላና ስለት ባነገቡ የመንገድ ጦረኞች ጭፍራዎቹ ተማምኖ የመንግሥትነት ሥራውን ጀመረ።ዕድሜ ለዱላ ለጊዜው ተሳካለት። ከሁሉ በፊት ግን በነዚሁ አጃቢዎቹ ዘመቻ  ተቃዋሚዎቹን በተለይም ሶሻሊስቶቹንና ኮሚኒስቶቹን    ከያሉበት ጥርግርግ አድርጎ አጠፋቸው።ተከትሎም በ1925 እ.አ.አ የፋሽስት መንግሥት አውጆ እራሱን ዳግማዊ ዱቼ በማለት መሪነቱን አረጋገጠ።ያንን ተከትሎ በአውሮፓ የፋሽስት ድርጅቶች ብቅ ብቅ ማለት ጀመሩ።ከ1930 እ.አ.አ ጀምሮም የአዶልፍ ሂትለር የብሔራዊ ሶሻሊስት እንቅስቃሴ የዘር ማንነትን መመሪያው አድርጎ የፋሽዝም ዋና አቀንቃኝና ተሸካሚ ምሰሶ ሆነ።ከአርያን ዘር ውጭ የሆኑትን ከምድር ገጽ ለማጥፋት ቆርጦ ተነሳ።በሌሎቹም አገሮች የፋሽዝም ተከታዮች ብቅ ብቅ ማለት ጀመሩ፤ለሥልጣንም በቁ።በዚህ ግብታዊ እንቅስቃሴ በብዙ አገሮች የንጹሃን ደም ፈሰሰ፤በሚሊዮን የሚቆጠሩ ስዎች ጭዳ ሆኑ።አገሮች ፈራረሱ፣ታሪካዊ ቅርሶችና ንብረቶች ወደሙ።
ፋሽዝም ርዕዩተዓለም ነውን?
በአንዳንዶቹ ዘንድ ፋሽዝም የሊበራል ካፒታሊዝምና የማርክሲዝም ተቀናቃኝ የፖለቲካ አማራጭ ተደርጎ ይወሰድ ነበር።ሆኖም ግን መሪዎቹም ሆኑ ተከታዮቹ በቴዎሪ የዳበረ እውቀት የነበራቸው ሳይሆኑ ሃይልን እንደ እውቀት የሚቆጥሩ ሰዎች የክፋትና የጭካኔ ምግባር የሚፈጽሙበት እኩይ አስተሳሰብ ነበር፤ነውም።ሞሶሊኒ በአንደበቱ የጣሊያንን ችግር ለማሶገድ ፕሮግራም ያለው ድርጅት መመሥረት ሳይሆን የቆራጥ ወንዶች መኖር ነው ሲል አመጽንና ሃይልን መመሪያው እንደሆነ በይፋ ገልጾታል።

ምንም እንኳን የፋሽስት እንቅስቃሴዎች እንደዬአገሩ የተለያዬ መልክና አቀራረብ ቢኖራቸውም ከ1945 እ.አ.አ ጀምሮ የጋራ አስተሳሰባቸውና አቋማቸውን ለማወቅ ጥናትና ምርምር ሲካሄድ ኖሩዋል።በውጤቱም በጋራ የሚመሳሰሉበት እንዳለ ለማወቅ ተችሉዋል።ከሚመሳሰሉበትም ዋናዋናዎቹ የሚከተሉት ናቸው።

1= የገነነ ጎሰኝነት/ ዘረኝነት ወይም ብሔረተኝነትና ጥላቻ(hyper Nationalism,racism,ethnicity and haterade)

2 -ወታደራዊነት/ሃይል ተኮርተኝነት(militarism)

3 -አመጽ ወዳድነት(Violence monger)

4- ንቅናቄውን ለተሻለ ለውጥ የሚደረግ ተጋድሎ አድርጎ በማቅረብ ወጣቱን አሳስቶ ማጥመድና ለጥፋት ማሰለፍ /False propaganda

5-መሪዎቹ ጨካኝ ወንዶች፣ወሳኞች ፣የማይደራደሩና አስቸጋሪ ስብእና ያላቸው መሆናቸው(Unnegotiable,merciless and brutal manhood manifestations)

6-ያለፈውን የጎሳና /የብሔር ትልቅነት የሚያስተጋቡ ትርክቶችን መፍጠርና መንዛት የሚችሉ ቅጠኞችን ማሰለፍ/ create and hired fake propagandist and historians)

7-የህብረተሰብን የእርስ በርስ ጥላቻ የሚፈጥሩ፣ትያትራዊ በሆነ አቀራረብ ለመቀስቀስ ችሎታ ያላቸው ሰዎች የሚሰበሰቡበት ተቋም መፍጠርና ማመቻቸት
ከዚህ በላይ ከሞላ ጎደል የቀረቡት የጥናት ውጤቶች ለፋሽዝም መመዘኛዎች ሆነው ተገኝተዋል።
ይህንን ትንታኔ እንደመመዘኛና መነሻ አድርገን በአገራችን ውስጥ የነበሩትንና ያሉትን የፖለቲካና የቡድን ስብስቦች  ስንመረምራቸው የፋሽዝም መለያ ባህሪዎች እንዳላቸው እንገነዘባለን።

ደርግ፣-በወታደራዊ ተቋም ላይ ያረፈና የሚተማመን(Militarist)፣የሕዝብ ጥያቄና ችግር በሃይል እንጂ በጥበብ የማይፈታ፣ለእውቀት እንግዳና ጸር የሆነ፣ኢትዮጵያ ትቅደም በሚል ባዶ ቃልና መፈክር ሕዝቡን የተስፋ ዳቦ እያገመጠ ለእልቂት የዳረገ፤በፍርሃትና በሽብር ለጥ ሰጥ አድርጎ የሚገዛ፣እንደ ሞሱሊኒ ፋሲ ዲ ኮምባቲሜንቶ ካድሬና የአብዮት ጥበቃ የሚባል በዝቅተኛነቱ የሚያፍርና በቅናት የሰከረ ገዳይ ቡድን አስታጥቆ በነጻ እርምጃ በሚል ገደብ የለሽ የሽብር እርምጃ ወጣቱንና ምሁሩን በጠራራ ጸሃይ የጨፈጨፈ፣ለዓይን ማረፊያ የሆነውን አንድ ልጁዋን ገሎ እናትን በአስከሬኑ ላይ እንድትጨፍር ያስገደደና ለተገደለበት ጥይት ዋጋ የሚያስከፍል ፣ የማይደራደር፣ጨካኝ፣በሶሻሊዝም ስም አምባገነንነትን ያሰፈነ።ከአገር በላይ ለሥልጣኑ የሚጓጓና የሚጨነቅ በመሆኑ ከፋዥዝም ጎራ ይሰለፋል።

ሕወሃት/ኢሕአዴግ፣- በብሔር/ጎሳ ስም የተሰባሰበ፣ህብረተሰብን በጎሳና በሃይማኖት ለይቶ የሚያፋጅ፣የሶሺያሊስትና የሊበራል ከበርቴ መርሃ ግብርን ጨምቆ አብዮታዊ ዴሞክራሲ የሚል መመሪያ ነድፎ በተለይም የገጠሩን አርሶ አደር ልብ የሰቀለ ግን ከድህነትና ከስደት ያላዳነ፣ ህብረተሰቡን በጎሰኝነት፣በጥላቻ፣በጥርጣሬ፣በፍርሃት፣በእራስ ወዳድነት ቫይረስ የበከለ።የአገርን ጥቅም አሳልፎ የሚሰጥ፣ሕዝብን በጎሳ ማንነቱ ለያይቶ የክልል አጥር ገንብቶ እርስ በርሱ የሚያባላ፣የሚያፈናቅል ፣በሽብር ለመኖር የሚሻ፣የጭካኔ መሃንዲስ፣ የአገር መሪነት አደራና ሃላፊነት የማይሰማው፣ሕገወጥና ዘራፊ፣ለነገው ትውልድና አገር እጣ ፈንታ የማይጨነቅ፣ደንታ ቢስ።ለጥቂቶች ድሎትና መንደላቀቅን ለብዙሃኑ ችግር፣ስደትና ስቃይን  ለሚዳርግ ስርዓት የቆመ። ለሆዳቸው ያደሩ ሰላዮችን፣ ፕሮፓጋንዲስቶችን፣ምሁሮችን”፣ጋዜጠኞችን ሰብስቦ የሚያጭበረብርና በሽብር የሚገዛ በመሆኑ ከፋሽዝም ጎራ ይሰለፋል።
በተቃዋሚ ስም የኢሕአዴግ ስውርና ገሃድ ደጋፊዎች
በተቃዋሚ ስም የሚነግዱ፣ፖለቲካን እንደሱቅ በደረቴ የቤተሰብ የንግድ ተቋም ያደረጉ፣የጎሳ ፖለቲካን የሚያራምዱ፣ሕዝብን በማፈናቀል፣በመግደል ፣በመዝረፍና ንብረት በማውደም የሚረኩ፣ወጣቱን ለጥፋት የሚቀሰቅሱ፣የሚያሰልፉ፤የህብረተሰብ ትስስርን የሚበጥሱ፣የጋራ ባህልና የእምነት ተቋማትን የሚያፈርሱ፣በእሳት የሚያጋዩ፣ከአንድነት ይልቅ ልዩነትን የሚያናፍሱ፣እንደ ቤንቶ ሞሶሊኒ ያሉ ፕሮፓጋንዲስቶችን የሚያመልኩ፣እንደሞሶሊኒ ፋሲ ዲ ኮምባቲሜንቶ ቆንጨራና ዱላ የተሸከሙ አረመኔ ጽንፈኞችን ያሰለፈ ቡድን እንደልቡ የሚፈነጭበት፣ሕግና ሰላም ያልሰፈነበት ስርዓትን ያሰፈኑ፣ከአገር በላይ ለራሳቸው ጥቅምና ሥልጣን የሚጨነቁ፣የኢሕአዴግ የመንፈስ ልጆች በመሆናቸው ከፋሽዝም ጎራ ይሰለፋሉ።

እነዚህ ከዚህ በላይ የተዘረዘሩትን ጸባያት የሚያንጸባርቁና ወንጀል የሚፈጽሙ በቡድንም ሆነ በድርጅት ስም፣በተቃዋሚም ሆነ በመንግሥት ስም የሚንቀሳቀሱት ሁሉ የፋሽዝምን ስነምግባራት በሚገባ የሚያስተናግዱ በመሆናቸው ቦታ ጊዜውና ስማቸው ቢለያይም የዚያው የቢኔቶ ሞሶሊኒ፣ የአዶልፍ ሂትለርና የሌሎቹም የፋሽዝም አስተሳሰብ አቀንቃኞች  ናቸው።ስማቸውን እዬቀያየሩ የመጡትና ወደፊትም የሚመጡት የጎሳ ፖለቲካ አቀንቃኞች የዛው የጥፋት ጎራ፣ የፋሽስቶች ጥርቅም የሆነው የኢሕአዴግ የመንፈስ ልጆችና ሠራዊቶች ናቸው።

በአገራችን ላለፉት ዓመታት ጎልቶ የመጣው ቄሮ በመባል የሚታወቀው(ቀሮ ቢባል ይሻላል፣ምክንያቱም ዃላ ቀርና ማስተዋል የጎደለው፣መንጋ፣ የድንጋይ ዘመን ግልባጭ ትውልድ (recarniated of stone age generation) ስለሆነ)  ዱላና ቆንጨራ የተሸከመው የጥፋት ሰራዊት እንደቢኔቶ ሙሶሊኒ ፋስና ዱላ ተሸክሞ በየመንገዱ ተሰማርቶ ሕዝብ ሲያሸብር እንደነበረው ፋሲ ዲ ኮምባቲሜንቶ ሠራዊት በአንድ ጁዋር ሙሃመድ በሚባል ጎሳንና ሃይማኖትን መሳሪያ አድርጎ በተነሳ፣ የፖለቲካ ፕሮግራምና ድርጅት በሌለው  አሸባሪና ቅጥረኛ  ግለሰብና ኦነግ በሚባል ጸረ ኢትዮጵያ  ድርጅት የሚንቀሳቀስ  አሸባሪ ሃይል ነው።ይህንን የጥፋት ሃይል  ለመብት የሚታገል አድርጎ መቁጠር የመበታተኑን አደጋ በጸጋ መቀበል ማለት ነው። የጎሰኝነት ፋሽዝምን አሜን ብሎ መቀበል ማለት ነው።ጁዋር ሙሃመድም እንደ ሙሶሊኒ ሥልጣኑን በውድ ወይም በግድ እወስዳለሁ ብሎ ቋምጦ የተነሳ፣በቄሮ(በቀሮ) የሚተማመን ግለሰብ ነው።ስለሆነም ለሰላምና ለአንድነቱ ቀናኢ የሆነው ዜጋ ሃይሉን አስተባብሮ ሊመክተውና ብሎም ሊያሶግደው ይገባል።በሥልጣን ላይ በአለው የጎሰኞች ቡድን ስርዓት ተማምኖ ሊዘናጋ አይገባውም።ብልህ ከአንድ ጊዜ በላይ አይታለልም !ከስህተቱ ይማራል!  

አገራችንን ከነዚህ አይነቶቹ የፋሽዝም መንኮራኩር ከሆኑት የጥፋት ሃይሎች ለማዳን ዋና መመሪያቸው የሆነውን ጎሰኝነትንና የጎሳን ፖለቲካ እንዲሁም በዛ ላይ የተዋቀረውን ስርዓት ማሶገድ ነው።ጎሰኞች የፈጠሩትን ክልል የተባለ የልዩነት ግምብ ማፍረስና ብሔር ብሔረሰብ የሚሉትን ጸረ ሰውነት፣ጸረ ኢትዮጵያዊነት፣ ጸረ ዜግነት ስያሜ መጠየፍና አለመጠቀም ነው።ለመከራውና ለችግሩ፣ ለሰላሙ መጥፋትና ለመፈናቀሉ ብሎም ለአገር መበታተን ስጋት   መነሻና መመሪያ የሆነውን ሕገ-ጎሳ አሶግዶ ኢትዮጵያዊ ሁሉ በአንድ አገር ዜግነት መብቱ ተከብሮለት በአንድነትና በሰላም  እንደሰው ለመኖር የሚችልበትን ስርዓት ማስፈንና ለዚያም  ከሁሉምና ከመንግሥትም በላይ የሆነ መተዳደሪያና መመሪያ ሕግ አርቅቆ በተግባር ላይ እንዲውል ማድረግ ነው። ያንን በተግባር የሚተረጉም ከሁሉም የህብረተሰብ ክፍሎች የተውጣጣ የሽግግር መንግሥት ማቋቋም የመፍትሔው ቁልፍ ነው። ሰላም ፣መረጋጋት፣ዴሞክራሲ፣ሃገራዊ ተቋም፣  ፣የመንቀሳቀስ መብት በሌለበት ሁኔታ ምርጫ ይካሄድ ቢባል በሥልጣን ላይ ያለው በኢሕአዴግ ማህጸን ውስጥ የተፈለፈለ፣ለባዕዳን መሳሪያ የሆነ የጎሰኞች ቡድን  በሥልጣኑ ላይ እንዲቆይ መፍቀድ ማለት ነው።
ጎሰኝነት ፋሽዝም ነው!

አገራችንን ከፋሽዝም መዳፍ ፈልቅቀን እናውጣ፣ሕዝባችንን ከእልቂት ማዕበል እናድን!!
አገሬ አዲስ