Tuesday, October 24, 2023

ከጦርነት በፊት እንወያይ፤ መወያየት መልካም ጌታቸው ረዳ Ethiopian Semay 10/25/23

ከጦርነት በፊት እንወያይ፤ መወያየት መልካም

ጌታቸው ረዳ

Ethiopian Semay

10/25/23

 

በዚህ ቪዲዮ የምታደምጡት ቅን ልቦና ያለው ኤርትራዊው ፕሮፌሰር ተስፋጽዮን ነው። ፕሮፌሰር ተስፋጽዮን በጀርመን ብረይመን ከተማ በብረይመን ዩኒቨርሲቲ ውስጥ የሕግ መምህር ነው። ፕሮፌሰሩ ከጦርነት ይልቅ እንደ መፍትሔ ይህንን ሃሳብ በማቅረቡ፤ያቀረበው ሃሳብ በሃሳብ ከመሞገት ይልቅ  በጽንፈኛ ኤርትራኖች ከፍተኛ የጥላቻ እና የስም ማጥፋት ዘመቻ ተደርጎበታል። ይህንን ካልኩ አሁን ወደ ርዕሴ ልግባ።

ሰሞኑን የታዘብኩት ነገር አለ። በተቃዋሚው በኩል ወደብንና የባሕር በርን ጉዳይ አስመልክቶ ሕዝቡ እንዳይወያይበት እያደረጉት ያሉት የማጣጣልና የማገድ ጫጫታ ፤ እንዲህ  ያለው አስገራሚ ባሕሪ ይከሰታል ብየ አልገመትኩም ነበር። ሆኖም እየሆነ ነው።

 ስለ ሁኔታው መቀጨጭና መጎልበት አብረን የምናየው ይሆናል። ዛሬም የምወያየው ሌላ ጉዳይ የለኝም። ትግሉ አሁን ወዳለበት ድረስ እንዲደርስ የበኩሌን አድርጌአለሁ፡ ከዚህ ወዲያ ተረካቢዎቹ ይቀጥሉበት። ዛሬ ትኩረቴ በ1983 “ዘላቂ የሆነ ከባድ ብሔራዊ ወንጀል” በተፈጸመባት ኢትዮጵያ ላይ ነው። ባለፈው ሰሞን እንደገለጽኩት ስለ ወደብ ጉዳይ አብይ አሕመድ ያንሳው የአብያ አሕመድ እኩያ ሰይጣን ያንሳው፤ የምክንያቱ መነሻ የፈለገው ምክንያት ይሁን ተዳፍኖ አቧራ ለብሶ የነበረው ጉዳይ ለውይይት መቅረቡ በኔ በኩል ትክክል ነው። መለስ ዜናዊ ሰይጣን ነበር፤ ግድቡ አስጀመረው፤ ተከታዩ የሆነው ሰይጣንም ስለ ወደብና ስለ ባሕር በር መዘጋት ጉዳይና ስለተፈጸመብን ወንጀል ዓለም  እንዲወያይበት ማድረጉ ትክክል ስለሆነ ልዩነታችንን ይዘን በዚህ እንቀጥል። አብይ አሕመድም ሆኑ ሌሎች ሰዎች “ወደብ ለማግኘት በክራይ” ስለሚለው ጨዋታ ግን መወገዝ አለበት።

እዚህ ጭለማ ውስጥ እንዴት ገባን? የወያኔ አጫፋሪዎችና ካድሬዎች የነበሩት መልስ ይስጡን። ዛሬ የገባንበት አጣብቂኝ ተጠያቂው ወያኔና ካድሬዎቹ እንዲሁም አጫፋሪዎቹ ናቸው።  ከዘመነ አክሱም ጀምሮ እስከ 1983 ዓ.ም ዘመነ ደርግ ድረስ አንጡራ የሆነው ኢትዮጵያ የተፈጥሮ የቀይ ባሕራችን ወደቦችና ድምበሮችዋ  የሆነው  መሬትና ሕዝብ (ህዝቡ ሲፈልግ አሁን ባለበት ሰፊ እስርቤትና ስደት ለመኖር መቀጠል ከፈለገ “ምርጫው ነው”፡ መሬታችንና ወደቦቻችንን ግን “በውይይት፤በሕግ እና በጉልበት” እንጂ  እንዳለፈው ቀልድ “ለምርጫ የሚቀርቡ አይደሉም”።

ሰሞኑን እየታዘብኩት ያለሁት ከቶ መማር ያልቻሉት አስገራሚ የሆነ ባሕሪ ያላቸው በተለይ ብዙዎቹ ኢትዮጵያውያኖቹ  እና የኤርትራኖች (ኤርትራኖችስ ግድ የለም “ተሰድደውም ተዋርደውም፤ባሕር ውስጥ እየሞቱም፤ “በበደዊን አረቦችና በራሻይዳ አረቦች” እየተሰለቡም፤እየተገረፉም፤እየተጠለፉም” ለምን እንዲህ እንደሆኑ ከኢትዮጵያ መለየት ምክንያት እንደሆነ መማር የማይችሉ አመላቸው ነው) እኔ የገረመኝ ግን የኛዎቹ ግን እየተለቀቁ ያሉት “ፌዞች” ዘላቂ ጉዳት ያላቸው መሆኑን ሳይረዱ ወይንም በግድየለሽነት በየሚዲያው  በማዳመቅና በማሰራጨት ላይ ያለው “በቀይ ባሕርና በወድብ “የኩመካ ድራማ” (ፌዝ) በሰፊው እየተካፈሉበት ነው።

በ1983 ዓ’ም ባለ ዘመነኞቹ ወደ ሥልጣን እርካብ ወጥተው የነበሩት ትግሬዎች ፤ ኢትዮጵያን ለማፍረስ በዛቱበት ዓላማ እና የታገሉለትና የሞቱለት የኤርትራዊነት ዘላቂ ጥቅም እውን በማድረግ የሕዝባችንን ህይወት እነሆ በጨለማ ዓለም ውስጥ ከትተውት ሄደዋል። አገር ማፍረስ እነሱንም የሚጎዳ እንደሆነ ያልተረዱት የትግሬ ፋሺሰቶች ሥልጣን ከተነጠቁ ወዲህም ቢሆን በዛቱበት መንገድ ለመቀጠል የጀመሩት የመገንጠል መንገድ ሳይሳካላቸው ቀርቶ እነሆ እነሱም ቢሆን አልጣማቸውም።ራሳቸውን ጭለማ ከትተው እኛንም ጨመሩን።ትግላችን ዘርፈ-ብዙ ነው። ቀዳሚነት አብይን ማስወገድ ነው። ያንን አታድርጉ ያላችሁ ሰው የለም። በበኩሌ አላልኩም። ግን አብይ ሥልጣን እስካለ ድረስ የባሕር ወደብ ጉዳይ በሕግም በውይይትም ህያው እንዲሆን ተዳፍኖ "ጥቀርሻ ለብሶ" የነበረው ጉዳይ ፤ ባጭር አማርኛ “የሞተውን ጉዳይ” ትንፋሽ እዘራበታለሁ ካለ ልክ መለስ ግድቡ እንደሰራው አብይም የባህር ጉዳይ የተፈጸመብንን ወንጀል ለውይይት አቀርባለሁ ይህንን የማድረግ አቅም አለኝ ካለ መንገዱ  ጨርቅ ያድርግልህ ተብሎ ነገሮችን ሳያጣጥላሉና ሳያሰናክሉ መመልከትም እኮ ጨዋነት ነው።  በተለይ አማራዎች ናቸው በዚህ በማፌዝና በማጥላላት ጉዳይ “ከኤርትራውያን በላይ” እየገፉበት በሰፊው ተዋናይ እየሆኑ ያሉት እና ጥያቀተው ጥላሸት መቀባትና ተውኔታዊ  ፌዞችን ማሰራጨት በለመዱበት በሙዚቃ ሲዘፍኑላቸው በነበረው የማሽቃበጥ ባሕሪያቸው ዛሬም ለኤርትራኖች እያሽቃበጡ  ከነሱ ጋር ወገንነታቸውን ለማሳየት ብዙ ርቀት እየሄዱ እንደሆነም በየሚዲያው እየታዘብኩ ነው።ለኤርትራኖች በመወገን እየነተራችሁት ያለው ዳንኪራ እንኳን ለናንተ በጠላትነት ለሚፈርጅዋችሁና ለጥላቻቸውም ዘፈኖች ለዘፈኑላችሁ ቀርቶ አብረው ለሞቱላቸው ወደብና ነጻነታቸው በወርቅ ሳህን  ላበረከቱላቸው ለትግሬዎቹም ያንን ዳንኪራ መምታት ብድራቸው ያየነው ነው። ስለዚህ  የዳንኪራ ድለቃ ትታችሁትታችሁ በያዛችሁት ትግል አትከኩራችሁ ቀጥሉ ነው የኔ ምክር።