Wednesday, November 2, 2022

ከዚህ በኋላስ ወዴት? ከዚህ በኋላ ወያኔ ውስጥ ለውስጥ ተዋጊ አንጃ ይፈጥራል ጌታቸው ረዳ Ethiopian Semay 11/2/22


ከዚህ በኋላስ ወዴት?  ከዚህ በኋላ ወያኔ ውስጥ ለውስጥ ተዋጊ አንጃ ይፈጥራል

ጌታቸው ረዳ

Ethiopian Semay

11/2/22

ወደ ትንታኔየ ከመግባት በፊት፡ የሁለቱ ፌርማ የሚነግረን በስምምነቱ መሰረት ስምምነቱ ዘላቂ ሰላም እንደማያመጣ  አጭር መስመር ለማስመር “አከራካሪ ቦታዎች (የወልቃይትና የራያ ማለቱ ነው) በሕገመንግሥቱ መሰረት ይፈታል ማለት “ወደ ቀድሞው ሁኔታ ይመለሳል፡  ማለት ነው፤ የቀድሞ ሁኔታ ማለት ደግሞ “በአማራና በትግራይ መካካል ያለው የመሬት ጥያቄና የዘር ማጥፋት ወንጀሎች” ይቀጥላል ማለት ነው። እዚህ ላይ ድሉ የማን ነው? የወያኔዎች /የትግሬዎች!! ማጠንጠኛው በዚህ ስምምነት ውስጥ ሆን ተብሎ የአማራ ማሕበረሰብ ተወካዮች እንዳይካተት የተደረገበት ዋናው ምክንያት ለዚህ የስምምነት ሴራ ነው። የአልጄሪስ ስምምነቱ እንደገና በወልቃይትና በራያ ስሙን ለውጦ ተከስቶ ይመጣል ስል የነበረው ለዚህ ነው።

አሁን ወደ ትንታኔየ ልግባ!!

ዛሬ በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ ውስጥ በወያኔ እና በኦሮሙማው መንግሥት ሲካሄድ የነበረው ድርድር ተቋጭቷል። ብዙ ሰው ደስታውን ገልጿል። የስሜት ህዋሳቶች ለመቆጣጠር አስቸጋሪዎች ናቸው። ደስ ብሎኛል፡ እልል፤ የዛሩ ቀን ልዩ የልደት በአሌ አድርጌ እቆጥረዋለሁ ..ወዘተ ..ወዘተ… የሚል ቡረቃ በየሚዲያው የፖለቲካ ተንታኞች ሳይቀሩ ሲቦርቁ ሰምተናል።

ሰላም ጥሩ ነው። ግን ይህ ሰላም የማን ነው? ይህ ስምምነት ወያኔ ያደረሰው የጦር ወንጀል እና ራሱም በተለያዩ ንግግሮቹ ያመነባቸው አብይ አሕመድ የፈጸማቸው  ወንጀሎች ሁለቱ ፋሺስቶች የፈጸሙዋቸው አገራዊና ሰብአዊ የሕግ ጥሰቶች ማን ይጠይቃቸዋል?  የሚለው ጥያቄ አልተመለሰም።

ሰዎች ለጊዜው መጀመሪያ ሰላም ይምጣ እና ከዚያ ተጠያቂነት ይመጣል የሚሉ ሊኖሩ ይችላሉ። ያ ግን ሊሳካ አይችልም። ምክንያቱም በሁለት ተደራዳሪ ወንጀለኞች የሚካሄድ ማንኛውም ስምምነትና ውይይት የመጨረሻ ግቡ “ሁለቱም ወንጀለኞች” ተጠያቂ የማያደርግ ስምምነት ነው የሚስማሙት። ዋናው ነገር ምን ስለሆነ ነው ወደ ድርድር የገቡት? “ሰውና ንብረት ስለወደመ” ነው። ውድመት ደግሞ ከሰማይ አልመጣም በነዚህ ሁለት ተፋላሚዎች መካካል የመጣ ውድመት ነው። ውድመት ወንጀል ነው። ውድምት የፈጸሙ ወንጀለኞች ድግሞ  የጦርነት ወንጀል የሚያጣራ ገለልተኛ ተቋም እስካልተመሰረተ ድረስ ይህ ሰላም የሁለቱ ወንጀለኞች ሰላም ብቻ ነው ሊሆን የሚችለው።

ከዚህ በኋላስ ወዴት? የሚለው ጥያቄ ካልተጠየቀ ውጤቱ ዞሮዞሮ በሌሎች ትንተናዎቼ እንደጻፍኩት የአልጀሪስ ስምምነት ሆኖ ይቋጫል (70 ሺ ሰው አልቆ ተጠያቂ አልባ ስምምነት) ማለት ነው።

ሁለቱም ፋሺስቶች መጨረሻ ሕዝብ አስፈጅተውና ፈጅተው አርስበርሳቸው ተቃቅፈው ያለ ምንም ተጠያቂነት ጦርነቱ ይቋጫል ብየ ደጋግሜ ከነሓሴ ጀምሮ ጽፌአለሁ፡ ስንት ሰው እንዳነበበው ባለውቅም እውነታው ይኼው ዛሬ ተፈራረሙ። ሆኖም ችግሩ እስካልተፈታ ድረስ የፋሺስት ሰላም እንጂ የማሕበረሰባችን ሰላም ሊፈታ አይችልም።

እንድታውቁልኝ የምፈልገው ፤ ወያኔ የሰላም ስምምነት ያድርግ እንጂ ፤ ትግራይ ውስጥ “የትግራይ ሪፑብሊክ”  ዓላማ ለማስቀጠል በውጭም በውስጥም ቁጥራቸው የማይናቅ የሚንቀሳቀሱ አክራሪ የትግራይ ብሔረተኞች አሉ። ወያኔ አሁን ይዋቀራል በሚባለው የትግራይ አዲስ አስተዳዳር ካልተካተተበት ወይንም ካልመራው፤ ውስጥ ለውስጥ አንጃዎችን  መልምሎ  ጦርነቱ እንዲቀጥል ያደርጋል (ተካትቶም ቢሆን ያንን ተንከሉን ይቀጥልበታል)።

ምን መለቴ ነው? ትንሽ ዘርዘር ላድርገው። አሁን ያሉት የወያኔ ተዋጊዎች ትጥቃቸው ፈትተው ወደ ሰላማዊ ህይወት ይገባሉ የሚል ስምምነት ቢደረግም፤ በዚህ ስምምነት የማይስማማሙ በወንጀልና በሙስና የተጨማለቁ የወያኔ ወታደራዊ መሪዎች እና አክራሪ ብሄረተኞች አንጃ ፈጥረው “አንገባም” ብለው (ከወያኔ ጋር ውስጥ ለውስጥ ምክክር በማድረግ) ታጣቂው ቡድን ትግሉ እንዲቀጥል ያደረጋሉ።

ይህ ደግሞ በኦነግ (አሁን በዳቦ ስሙ “ሸኔ” እየተባለ የሚጠራው) ያየነው ታሪክ ትግራይ ውስጥ ይደገማል። ዞሮ ዞሮ ዋናው ጥያቄ ጦርነት ሲቆም “የተፈጸመው ወንጀል” መቋጫ ካልተሰጠውና በዚህ ድርድር እንዳይካተቱ የተደረጉ “የጦርነቱ ሰላባዎች የሆኑ ተወካዮችና ሌሎች ተዋናዮች” ድምጻቸው እስካልተደመጠ ድረስ የሰላም ትርጉሙ የወንጀለኞች ሰላም እንጂ “የተጠቂዎች (የvictims)” ሰላም አይደለም።ወጣም ወረደ በተንኮል የተካነው  ወያኔ ትግራይ ውስጥ “አንጃ ተዋጊ” ትግራይ መፈጠሩ “አይቀሬ”  ነው! አንጃው ባለበትም ሆነ ዘግይቶ ጦርነት ሲቀጥል “ወያኔ” በለመደው ተንኮሉ “የኔ ስራ አይደለም እኔ የለሁበትም” እያለ ልክ አብይ አሕመድ እና ኦነግ “ሸኔ” አንጃ እንጂ የኔ ሰራዊት አይደለም ብሎ “እያታለለ” የምስኪን አማራ ገበሬዎችና ሰላማዊ ሰዎች ነብስ እየቀጠፈ እንደቀጠለው  ሁሉ “ወያኔም” እንዲሁ አንጃውን አስቀድሞ በመመካከር የሽምቅ ተዋጊነቱን መቀጠሉ አይቀሬ ነው።  

በዚህ አጋጣሚ አንዳንድ የሚዲያ ተንታኞች ሲሉ የምሰማው ያስገረመኝ ነገር፡ “ እባካችሁ ጦርነቱ ይቁም ለድርድር እንዲቀመጡ ጦርነት አቁሙ ብለን እንግፋበት ስንል አምቢ ያለችሁ አሁን ይኼው ተደራደሩ” ምን ይዋጣችሁ! እያሉ ሲናገሩ ሰምቼ ሁሌም የሚገርሙኝ ትንታኔዎች ናቸው። የኔ ጥያቄ “ጦርነቱን አቁሙ ፤ጦርነት እልቂት ነው” ብለን ብንጮህባቸውስ ወያኔዎች ጦርነቱን ያቆሙ ነበር ወይ? የሚለው ግን መልስ የላቸውም። ጦርነቱ ጀመሪዎች ወያኔዎች ወደ አማራ መሬቶች ገብተው ያሻቸው ሲያደርጉ “መልሱ ምን መሆን ነበረበት?” ጦርነት አይጠቅምም እባካችሁ አቁሙ ተብለው ሊሰሙ ይችሉ ነበር ወይ? አሁን ደግሞ ያለተጠያቂነት “ሰላም” (ጦርነቱ ቆሞ) ሰላም ተብሎ ሊጠራ ይቻላል ወይ?

ዞሮ ዞሮ ወደዳችሁም ጠላችሁም ትግራይ ውስጥ ወያኔ ውስጥ ለውስጥ አንጃ ተዋጊ ማዘጋጀቱን አይቀሬ ነው።               

ጽሑፉን ተቀባባሉት፤ መረጃ የሕሊና መሳሪያ ነው

ጌታቻው ረዳ

Ethiopian Semay