Sunday, August 7, 2022

ለኢትዮጵያ ትንሣኤ መራቅም ሆነ መቅረብ ብቸኛ ተጠያቂው አማራው ነው! ዳግማዊ ጉዱ ካሣ Ethiopian Semay 8/7/22

 

ለኢትዮጵያ ትንሣኤ መራቅም ሆነ መቅረብ ብቸኛ ተጠያቂው አማራው ነው!

ዳግማዊ ጉዱ ካሣ

Ethiopian Semay 8/7/22

ተወደደም ተጠላ የትንሣኤ ቀን ቀርባለች፡፡ የተዘራው ሁሉ በቅሎ፣ ቡቃያውም አድጎና አዝመራው ጎምርቶ ምርቱ ሊታፈስ የቀረን ጊዜ እጅግ አጭር ነው፡፡ በወላድ አነጋገር ዘጠነኛው ወር ውስጥ ገብተን የመጨረሻው ምጥ ላይ ነን፡፡ መጠራጠር ይቻላል፤ አለማመንን ማንም መከልከል አይችልም፡፡ ቶማሶች ዱሮም ነበሩ፤ አሁንም አሉ፡፡ እውነታው ግን ይሄው ነው፡፡ ኬኛዎች ተዘጋጁ!!

እንደውነቱ እንደብዙውን ጊዜው ሁሉ ዛሬም ምንም ነገር መጻፍ አሰኝቶኝ አልነበረም፡፡ ባበቃ ሰዓት፣ በኳስ አበደች የውቂው ደብልቂው ስካር ወዕብደታዊ ቅጽበት ማንም ምንም ቢጽፍ ለውጥ እንደማያመጣ አውቃለሁ፡፡ ግን ትዝብትን ከትቦ ማስቀመጡ “በዚያን ክፉ ዘመን ምን ተብሎ ነበር?” ለሚለው የታሪክ ዓምድም ቢሆን ይጠቅማልና አንዳንዴ ዝምታን መስበሩ መጥፎ አይመስለኝም፡፡

ብዙዎቻችን ብዙ ጊዜ የጮህንበትን ጉዳይ ላስቀድም፡፡ ለኢትዮጵያ ትንሣኤ መምጣት ዋናው እርሾና ጉልላት አማራው የመሆኑን ያህል ከዚህ ሕዝብ የወጡ ውሉዳነ አጋንንት ለትንሣኤያችን መጓተትና የመስዋዕትነት ክብደት ትልቁን ሚና ይጫወታሉ፡፡ ይህ እጅግ በጣም የሚያሳዝን ግን ልናመልጠው ያልቻልን እጅጉን አደገኛ የሚባል ክስተት ነው፡፡ የረጂም ጊዜ ወዳጄ የሆነው ትግሬው የኢትዮ-ሰማይ ድረ ገጽ አዘጋጅ ጌታቸው ረዳ አማራን ከታወጀበት የዘር ፍጂት ለማዳን ቀን ከሌት ሲማስን በምናይበት ዐይናችን፣ የሕወሓቱን ቃል አቀባይ የቀድሞ የመቀሌ ዩንቨርስቲ ወስላታ መምህር በነገዱ አማራ የሆነውን ጌታቸው ረዳን ስንመለከት አሽሙረኛው ታሪክ በትውልዶች ላይ ምን ያህል እንደሚያላግጥ እንታዘባለን፡፡ ሆድና ኅሊና፣ እውነትና እብለትም ምን ያህል እንደሚለያዩ እንረዳለን፡፡

ከዚህ ዋና ነጥብ አኳያ አማራንና የገጠመውን ታሪካዊ አሳዛኝ ክስተት ስንፈትሸው ብዙ ነገሮችን በወፍ በረር መቃኘት እንችላለን፡፡

ከአሳፋሪ ታሪኮቻችን ብንጀምር በጣሊያን ጊዜም ሆነ ከዚያ በፊት ለጠላት ባንዳ ሆነው ኢትዮጵያን ካዋረዱና ወገናቸውን በጠላት ካስጨፈጨፉ ወገኖች መካከል ከአማራ ጉያ የወጡ ባንዳዎች ቁጥር ቀላል እንዳልነበር ታሪክ ምስክር ነው፡፡ ስለሆነም የአማራም ሆነ በደፈናው የኢትዮጵያ ጠላት ከሩቅ ሳይሆን እዚሁ ከቅርብ መሆኑን መገንዘብ አያቅተንም፡፡ የእናት ሆድ ዥንጉርጉር መሆኑ በብሂላችን የሚወሳውም ለዚህ ነው፡፡ በዚያ ላይ በተፈጥሮ ካለን የተንሸዋረረ ጠባይ በተጨማሪ ይሄ ሆድና ሥልጣን የሚሉት አማላይ ነገር ታክሎበት ዜጎችን ለሚዘገንን ውርደት እየዳረገ ዛሬ ድረስ በርካታ አማሮችን ለባንዳነት በመዳረግ ላይ ይገኛል፡፡ ከለየለት ጠላት ይልቅ ደግሞ የውስጥ ባንዳና ምንደኛ እጅግ አደገኛ ነው፡፡ ይህንንም ጠላቶቻችን ይገነዘቡታል፤ በደምብ አድርገውም ይጠቀሙበታል፡፡ ግርማ የጅብጥላ ነው የሽጥላ የሚባለውን የብአዴን ሰውዬ ብናይ ለምሳሌ በብአዴን ስም ተደራጅቶ ሲያበቃ ከጳጳሱ ቄሱ እንዲሉ ከኦነግም በላይ ኦነግ ልሁን ብሎ አማራን እያሳደደ እንደሚገኝ የአደባባይ ምሥጢር ነው፡፡ ዕዳችን ብዙ ነው፤ ጣጣችን ገና ነው፡፡

የዱሮውን እንተወውና የቅርብ ጊዜውን ባጭሩ እንይ፡፡ ገነት ዘውዴን የመሰለች አማራ፣ መለስ ዜናዊን ለመሰለ የአማራን ዕልቂት በዐዋጅ ደንግጎ ለኦነግና ኦህዲድ ሥልጠና የሰጠን መሠሪ ሰው ስትደግፍና በርሱ ፖለቲካዊ ፍቅርም ወድቃ ፓርላማ ተብዬው ላይ በዕንባ ስትነፋረቅ ማየት ለማመን የሚከብድ ዕንቆቅልሽ ነበር፡፡ በሌላ ወገን ደግሞ ፕሮፌሰር ኃይሉ አርአያን የመሰሉ ትግሬዎች የመለስን የዘር ፍጂትና የጎሣ ፖለቲካ ተቃውመው ለእሥርና ለእንግልት ሲዳረጉ ማየት በርግጥም የሰውን ልጅ ማንነት ለማወቅ የሚከብድ አስቸጋሪ ወቅት ተፈጥሮ ነበር፡፡ ብአዴን የተባለ ከእስስት ቆዳና ከጅብ ቀፈት የተሠራ የመጋጃዎች ቡድን በአማራው ላይ አሁንም ድረስ እየሠራው ያለው ግፍና በደል ሕወሓትና ኦነግ/ኦህዲዶች በዚሁ ሕዝብ ላይ ከሠሩት ግፍና በደል በእጅጉ ይበልጣል፡፡ እጅግ ብዙ አማራ ከዚህ በድን ቡድን ጋር ለሆዱ ሲል ተሰልፎ የገዛ ወገኑንና ምትክ-የለሽ ሀገሩን እያወደመ እንደሚገኝ ማንም ይገነዘባል፡፡ ግን የጊዜ ጉዳይ እንጂ ሁሉም ሒሳቡን ማወራረዱ አይቀርም፡፡

በአጭር አነጋገር አማራው በቁጥርም ሆነ በማንኛውም መሥፈርት - ከይቅርታ ጋር የይሉኝታን ድምበር በሚጥስ የአነጋገር ድፍረት እንድገልጽ ይፈቀድልኝና - የላይኛውን ሥፍራ ከሚይዙ ነገዶች መካከል የሚመደብ ሆኖ ሳለ ማንም ልቅምቃሚ ሸረኛ ከየሰሥርቻው እየተጠራራ ኢትዮጵያ ላይ እንዲሣለቅና ጥሬ ካካውን እንዲጸዳዳ ዕድሉ የተከፈተለት በጠላቶቹ ጉብዝና ሳይሆን በውስጡ በተደገሰለት ፀረ አማራ አንደርብና በአማራው ስንፍና ነው፡፡ አዎ፣ እውነቱ ሲታይ የድግምት ወይም የዲያቢሎሳዊ አፍዝ አደንግዝም ይመስላል፡፡ ደግነቱ ይህም መፈቻው ተቃርቧል፡፡ መጀመሪያ ያለው ሁሉ መጨረሻ እንዳለው ያለማወቃችን ምሥጢር ነው ብዙዎቻችንን እያነሆለለ ገደል እየከተተን የሚገኘው፡፡ እንጂ አቢይ ከመለስ ቢማር፣ መለስ ከመንግሥቱ ቢማር፣ መንግሥቱ ከግርማዊ ጃንሆይ ቢማር፣ … እኔ ካንቺ ብማር፣ አንቺ ከርሱ ብትማሪ … ይህችን አጭር የምድር ሕይወት ጣዕም እንዲኖራት ማድረግ እንችል በር፡፡ አለመታደል ነው ወገኖቼ፡፡ ለአንድ ቀን ኑሮ ብለን የሽህ ዓመት በደል በሰው ላይ ስንፈጽም አናፍርም፡፡

አማራው አማራውን እንዴት እየጨፈጨፈው እንደሆነ ደግሞ ከሰሞነኛ መረጃ ተነስቼ አንድ መረጃ ላካፍላችሁ፡፡ አማራን ከውስጥም ከውጭም ሰቅዞ የያዘው ጉድ መቼም ተወርቶ አያልቅም፡፡

ያው እንደሚታወቀው የኦሮሙማዎች ጥጋብ ለከት አጥቷል፡፡ በተለይ በአማራ ላይ የማያደርጉት ነገር የለም፡፡ ጥጋብን የማይችል ሰው የእግዜርንም ዐይን እስከመጠንቆል መድረሱ ያለና የነበረ ነውና እነዚህ ጅሎችም ከወያኔ በባሰና በከፋ ሁኔታ አማራውን በገዛ ሀገሩ ሳይቀር እንዳይንቀሳቀስ እያደረጉት ነው - ጅሎች የምለው የጅል ሥራ የሚሠሩትን አክራሪ ኦሮሞዎች መሆኑን መጠቆም እፈልጋለሁ (ቅይጡን የአዲስ አበባን ሕዝብ እየመሩ “የኦሮምኛን መዝሙር ማዘመራችንን፣ ኦሮምኛንም የመስተዳድራችን የሥራ ቋንቋ ማድረጋችንን እንቀጥላለን” ብሎ ኦሮምያን በሌላ ክልል በግልጽ ወክሎ መናገር ጅል ካላስባለ ሌላ ምን ሊያስብል ይችላል?)፡፡ እነሱ በሚኔሶታ ቤት እየገዙና ንብረት እያፈሩ በማንኛውም የዓለም ክፍል በነጻነት እንደማይሽከረከሩ ሁሉ እዚህ ኢትዮጵያ ውስጥ ግን አንድ ዜጋ በአማራነቱ ምክንያት ብቻ ከሰሜን ሸዋ ጠባሲት ወይንም ከጎጃሟ አቸፈር አዲስ አበባ መግባት አይችልም፡፡ በታሪክ ታይቶም ሆነ ተሰምቶ የማይታወቅ በድፍን ቅሎች የሚመራ ዘረኝነት ኢትዮጵያ ውስጥ ተከስቶ ጆሯችን እስኪዝል ብዙ ጉድ እየሰማን ነው፡፡ ይህ ክስተት እንደሚፈጠር ቀድመን የምናውቅ ጥቂት ሰዎች በነዚህ ኦሮሙማዎች ድፍረት ከመገረምና ከማዘንም አልፈን አሁን አሁን እየሣቅንባቸውም ነው፤ ምክንያቱም አንድ ሰው ካልታመመ በስተቀር መታወቂያ አይቶ “አማራ ስለሆንክ አዲስ አበባ አትገባም” ማለት ሊያምኑት የሚከብድ የ21ኛው መቶ ክፍለ ዘመን አዲስ ግኝት በመሆኑ፡፡ አማሮች ገዙ በተባለበት ዘመን - ብቻቸውን ገዝተው ከሆነ ማለቴ ነው - ይህን ያህል የከፋ ወንጀልና በደል በሌሎች ላይ አድርሰው ይሆን? ጓደኞቿ ስለሳቁባት ብቻ ስሟን ከጫልቱ ወደ ሠናይት የቀየረች ኦሮሞ፣ አማራ በድሎኛል ብትል ስህተት ነው፡፡ ጓደኞቹ ስለሳቁበት ስሙን ከጓንጉል ወደ ኤርምያስ የለወጠ አማራም ነበርና፡፡ በተጋነነና በተፈበረከ የሀሰት ትርክት የጠፋችሁ ወገኖቼ እባካችሁን ከዚህም ብዙ ሳይመሽ በቶሎ ወደኅሊናችሁ ተመለሱ፡፡ ቋንቋ ደግሞ ቡዴና (እንጀራ) እንጂ የማንነት መገለጫ አይደለም፡፡ ስትሞት ይዘኸው የማትሄደው ነገር ሁሉ ያንተ አይደለምና አትኩራበት፡፡

ከፍ ሲል ከተጠቀሰው ነጥብ ጋር በተያያዘ ወሎየዎች በመኪና ተሳፍረው ሲመጡ ከደብረ ብርሃን ጀምሮ መታወቂያቸው ይፈተሸና ያ ሳይፈለግ የተወለደ መታወቂያ ፈርዶበት “አማራ” የሚል ከሆነ የኦነጉ ወታደር ወይንም ለኦነግ ያደረ የብአዴን ሎሌ ተሣፋሪውን ያስወርደውና ወደመጣበት እንዲመለስ ከባድ ማስጠንቀቂያ ይሰጠዋል፡፡ ደብረ ብርሃን መዋል ማደር ራሱ አይፈቀድለትም፡፡ ወዲያውኑ ከከተማ እንዲጠፋ ያካልቡታል፡፡ መመለሻ ገንዘብ ያለው ሲመለስ የሌለው ግን እስኪመለስ ተደብቆ እንዲቆይ ይገደዳል፡፡ ይህ ሕዝብ እንግዲህ በኦነግም በብአዲንም እየተንገላታ ነው፡፡ “እዛፍ ላይ ብሠራ አሞራው መከራ፣ እካብ ላይ ብሠራ እባቡ መከራ … የት ውዬ የት ልደር” አለች አሉ የጎንደር ወፍ - አማራም እንደሷው ሆነ፡፡

“ደብረ ብርሃን ላይ የእሳት ዝናብ ይዝነብ” ብዬ የተራገምኩበት አሰቃቂ ነገር ደግሞ ይሄውላችሁ፡፡ በገዛ ሀገራቸው ስደተኛ የሆኑት እነዚህ ወገኖች አልጋ ሲጠይቁ ነጋዴው ከዳር እስከዳር የተነጋገረ በሚመስል መልኩ ለአንድ አዳር ከብር 1000 እስከ ብር 1500 ይጠይቃቸዋል፡፡ ሊያውም እንደዚያም ከፍለው የሚያድሩ ካሉ ሚሊሻዎች በሌሊት ይመጡና ከእንቅልፋቸው ቀስቅሰው ወደመጡበት እንዲመለሱ ያደርጓቸዋል፡፡ የምግብ ቤቶቹም ዋጋ እንደዚያው ዕጥፍ ድርብ ነው፡፡ አማራው በአማራው መዶሻ እየተቀጠቀጠ ነው፡፡ የሀገር ሽማግሌዎችና የሃይማኖት አባቶች በዚህ ዙሪያ ጣልቃ ብትገቡ ደስ ይለኛል፡፡

አማራ ለአማራ እስከዚህ ከጨከነ ከሽመልስ አብዲሣና ከሌላው ኦሮሙማ ምን ደህና ነገር መጠበቅ እንችላለን? አማራ ከላይ ከአገኘሁ ተሻገር እስከታችኛው ተራ ነጋዴ እንዲህ ከሆነ ምን እንበል?

በሰው ስቃይ ማትረፍ፣ በወገን ቁስል ጨው መነስነስ፣ በገዛ ሕዝብ ላይ እንዲህ ያለ ግፍና በደል ማድረስ ፈጣሪንም ታሪክንም ማሳዘን፣ ለትውልድም ከፍተኛ ዕዳ ማውረስ አይደለም ወይ? በነጻ ማሳደሩ ይቅር፤ በነጻ መመገቡም ይቅር፤ ያ ዓይነቱ ደግ ተግባር ከጤናማ ሰዎች እንጂ ሃይማኖታዊና ሞራላዊ ዕሤቱን ተነጥቆ ለሆዱ ካደረ የንግድ ማኅበረሰብ አይጠበቅምና እንተወው፡፡ ግን አገልግሎትንና ሸቀጥን በነበረው ዋጋ በማቅረብ ወገንን ማስተናገድ ለምን ተቸገሩ? አማራውን ምን ነካው? አማራው አማራው ላይ እንዲህ እየጨከነበት ሲታይ ነገን ይበልጥ እንድንፈራው ያደርገናል፡፡ በዚህ መልክ በግፍ የሚከማች ገንዘብና ሀብት ደግሞ መቅኖ እንደሌለው መታወቅ አለበት፤ በላተኛ ነው የሚልክበት፡፡ ለነገሩ ደብረ ብርሃን ለኦሮሙማ ቅርብ ናትና ነገሩ እየጠነከረ ሲሄድ አይቀርላትም፡፡ በዚህ ነውር የተሰማሩ ሰይጣኖች ግን ልጅ አይውጣላቸው፡፡ የኢትዮጵያን ትንሣኤም አይዩ፤ በእውነቱ እጅግ ያሳዘነኝና ኅሊናየን ያቆሰለ ነገር ነው፡፡

በተረፈ አቢይ ጠፋ አልጠፋ፣ ተሰወረ ተከሰተ የኦሮሙማን ወረደ መቃብር አይለውጥም፡፡ የኦሮሙማን ሥርዓተ ቀብር እያጣደፈ የሚገኘው ደግሞ ራሱ ኦሮሙማ እንጂ ሌላው አይደለም፡፡ አሁን ላይ ሆኜ ሳስበው እነዚያኞቹ ከነዚህ በተሻለ መጠነኛ ይሉኝታ እንደነበራቸው መገመት ችያለሁና በዚያም ምክንያት መቃብራቸውን ለ27 ዓመታት ያህል አዘግይተዋል፡፡ ብልጦች ነበሩ፡፡ እንደነዚህ የለዬላቸው ሞኞች አልነበሩም፡፡ የነዚህ ጅልነት እኮ በቃላት አይገለጽም፡፡ እንዴ፣ በነዚያኞቹ ጊዜ እኮ ከአሥር ነገር አንድ ሁለቱን ለሌላ ይሰጣሉ፤ አብረው መብላትን ያውቁ ነበር - በተለይ በመጀመሪያው አካባቢ፡፡ ጠባብነታቸውና ያንንም ተከትሎ የተጣባቸው ፍርሃት ነበር ጨካኝ አድርጓቸው ዕድሜያቸውን ያሣጠረው፡፡ እንጂ የኢትዮጵያ ሕዝብ እኮ ማንም ይግዛው ማን ጉዳዩ አይደለም፡፡ ይሄውና ሕዝቡማ ተከባብሮና ተቻችሎ አሁንስ ቢሆን ያለ መንግሥት እየኖረ አይደለምን? አቢይ ሞተ ኖረ ጉዳዩ ነው? በቃ፡፡ ዝም ብሎ ይኖራል፡፡ እንዲያውም ያለ መንግሥት መኖሩ ሳይሻለው አይቀርም፡፡ ለማንኛውም የእነዚህን አካሄድ ስንመለከት ለየት ይላል፡፡ ስግብግብነታቸው ወደር የለውም፤ ነገረ ሥራቸው ሁሉ ሱቅ እንደገባ ሕጻን ነው - በ“ሁሉንም ለኔ” የማይጠግብ ጉጉታምነት የተሞሉ እምብርት የለሾች ናቸው፡፡ ለምሣሌ መቶ ነገሮች ቢኖሩ መቶዎቹንም ራሳቸው መዋጥ መሰልቀጥ ብቻ ሳይሆን በድህነትህም አብረሃቸው አጠገባቸው እንድትኖር አይፈልጉምና ሊያጠፉህ ይሽቀዳደማሉ፡፡ በውነቱ የተለዩ ጉዶች ናቸው፡፡ ከደጉ የኦሮሞ ዘር እንዲህ ያለ ትውልድ መውጣቱ ይገርመኛል፡፡ ከትግራይ የወጡትንም አየናቸው - ብዙውን ሕዝብ በፀረ ኢትዮጵያነት አብክተውት ባንዲራዋን እንኳን እንዲጠየፍ አደረጉት፡፡ ታሪክ ጥርሱን ተነቅሶ የሚስቅብን ብዙ ጉድ እያየን ነው፡፡

ሰውዬኣቸው ስለመጥፋቱ ይነገራል፡፡ አኪሩን ስለጨረሰ ተደበቀ አልተደበቀ ለውጥ እንደማይኖረው በበኩሌ አምናለሁ፡፡ በነሮበርት ግሪንና በነማኪያቬሊ የፖለቲካ ሤራ ትንተና እየገቡ የዚህን ሰውዬ ሁኔታ የሚያብራሩ ሰዎችን ስመለከት ምን ያህል ሥራ መፍታት እንደሆነ እገነዘባለሁ፡፡ ይሄ ጨዋታ ነው፡፡ የጠነዛ ቀልድ ነው፡፡ ለዚያ ዓይነቱ የፖለቲካ ፌዝ ቢሆን ኖሮ ሣምንትም አሥራ አምስት ቀንም በቂ ነበር፡፡ አሁን ግን ከወር በላይ ነው፡፡ መናፈቅን ሲፈልጉ መረሳትም እንዳለ አቢይ አይጠፋውም፡፡ ስለሆነም አንዳች ነገር እንዳለ መጠርጠሩ የማይከፋ ሆኖ ሳለ የራስን የቤት ሥራ መሥራት ግን ጊዜ የሚሰጠው አይደለም፡፡ ሰው ሸክላ ነውና ለመታመምም ሆነ ለመሞት፣ ለማበድም ሆነ ለመቀወስ አቢይ የመጀመሪያም የመጨረሻም አይደለምና ለማንኛውም መርዶ ተዘጋጅቶ መጠበቁ አይከፋም ባይ ነኝ በበኩሌ፡፡ ከአንደበቱ የሚያመልጡትን አሳሳቢ አነጋገሮች ከበፊት ጀምሮ ለሚታዘብ ሰው ሰውዬው በእርግጥም በአእምሮ ጤንነቱ ብዙም ሊዘልቅ እንደማይችል ቢገምት አይፈረድበትም፡፡ “ዛፍ ትከሉ፣ ቢያንስ ለምንገድላቸው አማሮች አስከሬን ጥላ ይሆናቸዋል” ብሎ በሚመራቸው ዜጎች ሞት የሚያላግጥ ብቸው የሀገር መሪ ያለን እኮ ነን፡፡

ለማንቻውም እንደሚባለው አቢይ አንዳች ነገር ሆኖ ከሆነ ችግሩ ቀላል አይደለም፡፡ ብዙ ነገሮችን ስላበለሻሸ እርሱ በሕይወት እያለ ነገሮችን ለማስተካከል ቢሞከር እርግጥ ነው ከብዙ ችግር እንድናለን፡፡ አለበለዚያ የሚፈራው የሩዋንዳ ሁኔታ ስላለመከሰቱ ማንም እርግጠኛ መሆን አይችልም፡፡ የሆነው ቢሆን ፈጣሪ ይህችን ሀገር ይታደጋታል ብለን የምናምንና ለዚያም የሚጸልዩ ብዙዎች ስላሉ ያሰፈሰፈው ጠላት ሁሉ እንዳሰበው ሀገራችንን ሊያጠፋ እንደማይችል ታሪካችን ራሱም ምሥክር ነውና በእርግጠኝነት ሀገራችን አፈር ልሳ ትነሣለች፡፡ ነገር ግን የተሳለው ሠይፍ፣ የተሰበቀው ጦር፣ የተወደረው ጠበንጃ ቀላል አይደለምና መስዋዕትነቱን ቀለል እንዲያደርግልን አንድዬን እንለምነው፡፡ ሀገራችን ጫካዎቿም ከተሞቿም ጋራ ሸንተረሮቿም ሁሉ ደም በጠማቸው ዐውሬዎች በመሞላቱ ነጻነት በቀላሉ እንደማትመጣ መረዳት ብልኅነት ነው፡፡ ጨለማዋ ድቅድቅ ናት - ግን ፀሐይ ትወጣለች፡፡ ለኦርቶዶክሳውያን መልካም ፆመ ፍልሰታ፡፡  

Ethiopian Semay