Tuesday, November 30, 2021

ይድረስ ለትግራይ ሕዝብ ከእስክንድር ነጋ (Ethio Semay) 12/1/2021

 

ይድረስ ለትግራይ ሕዝብ

ከእስክንድር ነጋ

(Ethio Semay)

12/1/2021

ቅድሚያ ሰላምታዬ ለኢትዮ ሰማይ ድረገጽ አንባቢዎች እንደምንድ ናችሁ፡

ከላይ የጠቀስኩት ርዕስ በፋሺስቱ የኦሮሙማ መንግሥት መሪ በሆነው በአብይ አሕመድ ሥርዓት ውስጥ “የዘር ፍጅት እየተካሄደ መሆኑን በመቃወሙ” በተገላቢጦች “የዘር ፍጅት ለማድረግ ዝግጅት አድርገሃል” ብለው በሃሰት አስረው እርሱና ቤተሰቦቹን በግፍ እየተሰቃየ ያለው ብርቱው ሰው ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ “ምርጫ 97 መረጃና ትንታኔ” በሚል ባሳተመው በ1997 ዓ.ም መጽሐፍ ውስጥ ከብዙ ርዕሶች አንደኛው ምዕራፍ የሰፈረ ርዕስ የቀነጨብኩት ጽሑፍ ነው።

ለእስክንድር ነጋ ስቃይ ተጠያቂዎቹ ወያኔዎች እና አብይ አሕመድ መሆናቸውን በዓለም የታሪክ ማሕደር የተመዘገበ ነው።

ዛሬ ጽሑፉን ላቀርብ የፈለግኩት ምክንያት መጽሐፉን አላነበባችሁትም ይሆናል በሚል ሳይሆን፤ ወያኔና አብይ አሕመድ በቆሰቆሱት የሥልጣን ሽሚያ ምክንያት ጦርነት በከፈተላቸው መስኮት ገብተው ዛሬ የእስክንድር አሳሪዎችና ተባባሪዎች “እንደ ጀግኖች እየተሞካሹ” ስመለከት አንጀቴ መቃጠሉ አልቀረምና ሌላ ጀግና ከመፈለግ ይልቅ ጭለማ ውስጥ ታስሮ የሚገኘው ይህ ውድ የቁርጥ ቀን ልጅ ያበረከቱሉንን የተባረኩ ብጹአን ወላጆቹን እያመሰገንን የኢትዮጵያዊነት ተምሳሌነታችን የሆነው እስክንድርን ላለመርሳት በሚል ነው።

እስክንድር ይህን ርዕስ በሚመለከት ሲያትት በጣም በርካታ ሰነዶችን እያጣቀሰ ስለጻፈው፤ ሙሉውን ለማንበብ መጽሐፉን ማግኘት ይኖርባችሀሗል።  በሰነዱ ብዛት በዚህ ጽሑፍ ማቅረብ አይመችም። ስለዚህ እየዘለልኩ ፍሬ ነገሮችን እየጠቀስኩ አስነብባችኋለሁ። ብዙ ነገሮችን ይጠቅሳል “ስለ ዓፋሮች” ስለ “ኤርትራ ብሔሮች” ስለ “ወያኔ” ስለ ፡ባድሜ” ወዘተ፣..

እንደምታውቁት አብይ አሕመድ ከሚፈራቸው ፖለቲከኞች ውስጥ ቀዳሚው እስክንድር ነጋ ነው። ከእስክንድርን አጠፋዋለሁ ባለው መሰረት የኦሮሞዎች መንግሥት ፋሺሰቱ አብይ አሕመድ በተጠናወተው የሥልጣን ጉጉት እስክንድርን አስሮታል።  “በመዲናዋ ላይ የዘርና የሃይማኖት ብጥብጥ ለማንሳት” በሚል “ኢንተርሃሙዌ” ለመፈጸም ዝግጅት እያደረገ ነው ብሎ በሃሰት እንዳሰረው ሁሉ ወያኔም በምርጫ 97 እነ እስክንድር በተመሳሳይ መልኩ ተቃዋሚዎችን ወንጅሎ አስሮአቸው ነበር።

ወያኔ በበተነው የሃሰት ወረቀት” ላይ እስክንድር እንዲህ ይላል፡-

“….አንድን ትግራዋይ በትግራዋይነቱ ብቻ የሚጠላ ወይም የሚጠራጠር ኢትዮጵያዊ የለም።…………. ታዲያ በምን ተዓምር ነው በትግራይ ሕዝብ ላይ “ኢንተርሃሞይ መንፈስ” የምንዘምተው? ኢትዮጵያ ያለ ትግራይ ምን ዓይነት ኢትዮጵያ ነው የምትሆነው?......ፈጽሞ ሊታሰብ የሚችል አይደለም።የኢሕአዴግ መሪዎች ይህንን ውንጀላ ማንሳታቸው ምን ያህል ከገሃዱ ዓለም እንደራቁ ምልክት ይመስለኛል፡……….እያለ ይቀጥላል

የተከበርከው የትግራይ ሕዝብ ሆይ…

እውነት ለመናገር ይቺን ደብዳቤዬን ለመጻፍ ካሰብኩኝ ሰንብቻለሁ።

 የብአዴን መሪ የሆኑት የተከበሩ አቶ አዲሱ ለገሠ ተወልደው ያደጉበት ሐረርጌ ውስጥ በአሥር ሺዎች የሚቆጠሩ ዐማሮች የዘር ማጥፋት ጦርነት ሰለባ  (በሞት፤በመቁሰል፤በመፈናቀል) ስለ መሆናቸው (በ60 ዓመት ውስጥ ለ2 ጊዜ፤ ማለትም አንዱ በጣሊያን፤ለሁለተኛ ጊዜ ደግሞ  በ1983 እና በ1984 ዓ.ም. ) አንዱም ትንፍሽ ብለው አያውቁም።

ባለፈው ሰሞን ግን ወደፊት ይከተላል ብለው ስለገመቱት ሌላ ዙር የዘር ማጥፋት ዘመቻ (“ኢንትርሃሞይ” ብለው የገለፁት) ከተናገሩ ወዲህ ይህችን ደብዳቤ ለመጻፍ ሳወጣ ሳወርድ ቆይቻለሁ።

የተከበሩ አቶ አዲሱ ለገሠ፤ በቀድሞዎቹ የህወሓት አመራር አባላት (እነ ገብሩ አስራት ማለቴ ነው) አንደበት “ፀረ ትግራይ አመለካከት አላቸው” ሲባሉ ቆይተው እንደ ድንገት የትግራይ ሕዝብ ጠበቃ ሆነው በመቅረባቸው ብዙ ሰዎችን ያስገረመ ክስተት እንደሆነ አውቃለሁ።

በኔ በኩል ግን  የተከበሩ አቶ አዲሱ ለገሠ ለትግራይ ሕዝብ መቆርቆራቸው ጥሩ ነው፤አግባብም ነው፤ለትግራይ ሕዝብ አለመቆርቆር የግድ ትግራዋይ መሆን የለባቸውም።ችግሩ ለትግራይ ሕዝብ የሚያፈሱትን ዕንባ ዐማራ (ወይም በሳቸው አጣራር “ነፍጠኛ”) ጋር ሲደርስ ለምን ዕንባቸው ይደርቃል? የሚለው ነው።

በኔ ሚዛን የአንድ ነፍጠኛ ህይወት ከአንድ የትግራዋይ ህይወት አያንስም፤ እኩል ይመዘናል።የሰው ልጅ ህይወት ሁሉ እኩል ዋጋ አላት። የሰው ልጅ ነፍስ፤ብሔር የላትም። ብሔራችን፤አኗኗራችን ታሪካችን፤ቋንቋዎቻችን፤ሥነ-ልቦናዎችንና መልክአምድራዊ አሰፋፈራችን ከሥጋችን ጋር የተሳሰረ ነው።ነፍሳችን ግን ከዚህ ሁሉ በላይ ናት።

አንደ ነፋስ የማትጨበጥና የማትዳሰስ ናት። መተኪያ ስለሌላትም በጣም ውድ ናት። ትክክለኛ ምንነቷን እስከ ዛሬ ድረስ አናውቅም።…….. ስለዚህ የእግዚአብሔር ምሥጢር ነውና  የሰው ልጅ መቸም ቢሆን ሊረዳው አይችልም የሚለው ሃይማኖታዊው ትንታኔ እጋራለሁ።

ስለዚህ የትግራዋይ ነፍስ የነፍጠኛ ነፍስ፤አሜሪካዊ ነፍስ፤የጃፓናዊ ነብስ፤ የመለስ ዜናዊ ነፍስ፤የመንግሥቱ ሃይለማርያም ነፍስ…ብለን ዋጋ የምናወጣላት ነገር አይደለም። ሁሉም እኩል ክብር አላቸው። ከዚህ አኳያ ነው የተከበሩ አቶ አዲሱ ለገሠ በግፍና በጭካኔ ስለጠፋው “የነፍጠኛ ህይወት” አንድም ቀን ሳይተነፍሱ ቆይተው ገና ሊጠፉ ይችላሉ ስለሚሏቸው ነፍሶች መናገራቸው ብቻ በቂ አይደለም የምለው።

ለማንኛውም የተከበሩ አቶ አዲሱ ለገሠ ያነሱት ሃሳብ እንደመነሻ አድርጌ፤ ኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ ከሥልጣን ቢለቅ የትግራይ ሕዝብ የመጨፍጨፍ አደጋ ያሰጋዋል ወይ? የሚለው ጥያቄ መዳበስ እፈልጋለሁ። ..”

ካለ በሗላ እስክንድር ስለ አማራ ምሁር ያነሳውን በቂ ቦታ ካገኘሁ እዚህ አቀርበዋለሁ፤ ካልሆነ በክፍል 2 እከፍለዋለሁ። አሁን ስለ ኤርትራ ከሕግ ውጭ ስለ መገንጠል፤ ኤርትራ ውስጥ ስላሉ ብሔሮች ራስን በራስ የመወሰን መብት ሳያከብር ኤርትራ እንደ አንድ ብሔር አይቶ ስላስገነጠላት የተሳሰተው የብሔር እይታ እና መብት ረገጣ በሚገርም ትንተና በሰፊው ያትታል።

በዚህ ምክንያት የትግርኛ ተናጋሪዎች ብቻ ሳይሆን በትግራይና ኤርትራ ውስጥ የሚኖሩ በርካታ “ነገዶች” ለሁለት ከፍሎ ቤተሰቦችን እና ነገዶችን ባዕድ እንዳደረጋቸው የወያኔ ውሳኔ በታሪክ ተወቃሺነት ያትታል።

በዚህ መልክ ያቀረበውን ትንሽ ቀንጭቤ ላስነብባችሁ፤

“የተከበርከው የትግራይ ሕዝብ”

“እንግዲህ እዚህ ላይ ነው ትልቁ ጥያቄ የሚነሳው። ህወሓት ማስቀደም የነበረበት የቱን ነበር? ሃገሩን ነው? ወይስ ድርጅታዊ ጥቅሙን?

አንዳንድ የድርጅቱ ደጋፊዎች አንድ የሚያነሱት ጥያቄ አለ። ህወሓት የራስን እድል በራስ የመወሰን መብት እስከደገፈ ድረስ ለሀገሩ ብሎ እንዴት የኤርትራ ነጻነት መቃወም ይችላል? ይላሉ።

ኤርትራ ግን የተለያዩ ብሔሮች ስብስብ ናት እንጂ “ወጥ ብሔር” አይደለችም። መርሑ የሚለው “የራስን ዕድል በራስ የመወሰን መብት በቀጥታ ያላቸው ብሔሮች ናቸው” ነው። ማለትም በቋንቋ፤በመልክአ ምድር፤በስነ ልቦና፤በታሪክና ኢኮኖሚ የተሳሰሩ ብሔሮች። ሆኖም እንደ ኢትዮጵያና ኤርትራ የመሳሰሉ ሕብረ ብሔራዊ ቀጠናዎች እነዚህ ብሔሮች በመፈቃቀድ የሚመሰርቷቸው ናቸው።

ስለዚህ ከመርህ አኳያ ኤርትራ የራሷን ዕድል በራስ የመወሰን መብት አላት የሚባለው በውስጧ ያሉ ብሔሮች በመፈቃቀድ ሲመሰርቷት ብቻ ነው። የኤርትራ የራስን ዕድል በራስ የመወሰን  መብት “ከብሔሮቿ የራስን ዕድል በራስ የመወሰን መብት” ሊቀድም አይችልም። ቢያንስ በመርህ መሠረት ማለት ነው።

ህወሓት ከሻዕቢያ ለሚያገኘው የጦር መሣሪያ ቅድሚያ በመስጠት ግን በኤርትራ ውስጥ ባሉ ብሔሮች (ኢትዮጵያ ነን በሚሉ አፋሮችና ኩናማዎች..) መብት ላይ ፊቱን አዙሯል። በሌላ አነጋገር በኤርትራ ውስጥ ያሉ አፋሮችና ኩናማዎች “ኢትዮጵያዊ ነን” እያሉ “በግድ ኤርትራዊያን ናችሁ” ብሏቸዋል ማለት ነው። ስለዚህም ነው “ኤርትራን ሸጠ” ፤ “ኢትዮጵያን ካደ” እየተባለ የሚወነጀለው።

(አስገራሚው ነገር) በኤርትራ ውስጥ ያሉ አፋሮችና ኩናማዎች “ኢትዮጵያዊ ነን” ሲሉ ህወሓት እንደ ኢትዮጵያዊነቱ “ከጎናችሁ አልቆምም” ከማለቱም ባሻገር፤ ሌሎቻችን ከጎናቸው እንዳንቆም ጠፍሮ ይዞናል። ታዲያ የኢትዮጵያዊነት ትርጉሙ የቱ ላይ ነው?

የባድመ ሕዝብ “ኢትዮጵያዊ ነኝ” እያለ መላ ኢትዮጵያዊያን “ማንም በሃይል አይወስዳችሁም” ብሎ ከጎናቸው እንደቆመ ሁሉ ፤ የኤርትራ ረፈረንደም ከመካሄዱ በፊት አፋሮችና ኩናማዎች እንዲሁም ሳሆዎች “ኢትዮጵያዊያን ነን፤ ወገኖቻችን ፊታችሁን አታዙሩብን” ሲሉ ፤ ህወሓት ከጎናቸው መቆም አይገባወም ነበርን?

የባድመ ሕዝብ ኢትዮጵያዊነቱን ለማስከበር ዕዳ ለብቻው ካልተጣለበት የዓሰብ ባለቤት የሆኑት አፋሮች፤ ኢትዮጵያዊነትን ለብቻቸው የማስከበር እዳ እንዴት ይጣልባቸዋል?

እውነት ለመናገር ህወሓት እራሱ “በኤርትራ ያሉ ብሔሮች ዕጣ ፍንታውን በተናጠል መወሰን አለባቸው” የሚል አቋም ወስዶ ነበር። በዚህም ሳቢያ ሻዕቢያ ነበር ከህወሓት ጋር የነበረውን ግንኙነት ወዲያውኑ የበጠሰው። በሗላ ላይ ህወሓት ደርግን ለመጣል ሲል ብቻ ይህን አቋሙን ወደ ጎን በማድረግ በኤርትራ ውስጥ ያሉ ብሔሮች ወደዱም ጠሉም “ኤርትራዊያን ናቸው” ሲል ፈርዶባቸዋል። ከአፋሩ ኢትዮጵያዊነት ለደርግ መውደቅ ቅድሚያ በመስጠት በነዚህ ዜጎችቻችን ይቅር የማይባልለት ወንጀል ፈጸመ።

በጣም የሚያሳዝነው ግን፤ ሥልጣን ላይ ከወጣ በኋላ በትክክል ወደ እሚያምንበት አቋሙ መመለስ ሲችል፤ በታሪክ ሂደት በትግራይ ላይ ለደረሰው ጥፋት ማካካሻ ይሆን ይመስል፤አፋሮችና ኩናማዎችን በግድ ለሻዕቢያ አስረክቧቸዋል። ኢትዮጵያ ያለ ባሕር ብር አስቀርቷታል።

አስተዋዩ የዓፋር ሕዝብ ግን በ1990 ዓ.ም የባድመን ሕዝብ በግድ ኤርትራዊ ለማድረግ በሻዕቢያ ሲንቀሳቀስ (“የለመደች ጦጣ” አይደል የሚባለው?...)”የእኛ ወንድሞች በግድ ወደ ኤርትራ ሲጠቃለሉ ማን ደረሰልን?... ብለው ላለመበቀል አልሞከሩም፤ ባድመ ድረስ ሄደው አጥንታቸውን ከስክሰዋል።

ለዓፋርና ለኩናማ ኢትዮጵያዊያን መከበር ፤የትግራይ ህይወት መስዋዕት መሆን ይበዛበታል የሚል አቋም ያለው ወገን  አለ ብዬ ለመገመት ስለምቸገር ህወሓት ታሪካዊ ስሕተት ፈፅሟል ቢባል ለምንድ ነው በትግራይ ሕዝብ ክብር ላይ እንደተሰነዘረ ዱላ የሚቆጠረው? የትግራይ ሕዝብ ከኢትዮጵያ የባሕር በር አልባነት እንዴት ነው የሚጠቀመው?”

እነሆ እስክንድር እንዳለው ዛሬ “ዓፋሮች” ከኢትዮጵያዊነታቸው ጎን ቆመው ከሃዲውንና ወረበላውን ወያኔ  እየተፋለሙ ይገኛሉ። እስክንድርም ኢንተርሃሙዌው ኦሮሙማውን መሪ ከዘጋበት የጭለማ እስር ቤት ውስጥ ሆኖ እየታገለው ይገኛል።

ክብር ለእስክንድር እና ለመላው ቤተሰቦቹ ይድረስልኝ!!!

አመሰግናለሁ

ጌታቸው ረዳ (Ethio Semay)