Friday, September 22, 2023

ታጣፊ አልጋቸውን ይዘው መሥርያቤታቸው ውስጥ የሚተኙ ታታሪ ወያኔዎች የልደቱ ምስክርነት ሲፈተሽ ጌታቸው ረዳ Ethiopian Semay 6/21/2023

 

ታጣፊ አልጋቸውን ይዘው መሥርያቤታቸው ውስጥ የሚተኙ ታታሪ ወያኔዎች የልደቱ ምስክርነት ሲፈተሽ

ጌታቸው ረዳ

Ethiopian Semay

6/21/2023

አንብበው ከጨረሱ በላ ቪዲዮውን ከታች ይመልከቱ

የልደቱ “ወለም ዘለም” ባህሪ ብዙ ጊዜ ስለጻፍኩ በዚህ ሰውየ አልጽፍም ብየ ነበር፡ ሆኖም ወያኔዎች የልደቱን ንግግሮች ስለወደዱለት ደጋግመው ስለሚጠቀሙበት እርሱም ደግሞ ደጋግሞ ወያኔዎችን ግማሹ መላእክት ፤ግማሹ ሰይጣን እያደረገ በመሳል ሥርዓቱን እንደ ሥርዓት ከመመዘን ይልቅ የወያኔ ናዚ አባል ግለሰቦችን << ታጣፊ አልጋቸውን ይዘው መሥርያቤታቸው ውስጥ የሚተኙ አገር ወዳድ ታታሪ ‘ወያኔዎች’ >> እያለ የበጎ ተምሳሌት እንደሆኑ በመሳል የሥርዓቱን ትክክለኛ ስዕል እንዳይታይ ዛሬ የተወለዱና ለወደፊቱም ለሚወለዱ ወጣቶችን ለማሳሳት “ዘር አጥፊና አገር አጥፊውን ‘ኔቲቭ ኮሎናይዘሩን’ ወያኔን”  “የተዛባ ሥርዓት” ብሎ በመጥራት የሚለፋ ከንቱ ሰው ነው።

 የወያኔ ግለሰቦችን (ልክ ፕሮፌሰር መስፍን ወ/ማርያም የወያኔን የደህንነቱ ሹም የነበረ ክንፈ ገብረመድህንን ልክ እንደ ልደቱ ሲያቆለጳጵሱት እንደነበሩት) ሁሉ ልደቱም ግለሰቦችን በምሳሌ እያጣቀሰ (ያውም ስም ሳይጠቅስና እንዳፈተሹም፤ ለአቃቂር እንዳናቀርባቸው) ታሪክን ማዛባት (ዲስቶርሺን) በእውነትና በማስተዋል ላይ የሚደረግ የማዛበት ጥቃት ነው። ከሙሉ ኩንታል እንክርዳድ አንዳንድ ጥሩ ስንዴ አገኘሁ እያለ የሚያወራ አውቆ እያወቀ ታሪክ እያጣመመ “ልዩ ፖለቲከኛ ሆኖ ለመታየት” ታሪክ የሚያዛባ ከንቱ ፖለቲከኛ ነው።

ልደቱ እያደረገ ያለው ገዢዎቻችን እና አራጆቻችንን እንደ ሥርዓት ከማየት ይልቅ ሥርዓቱን በግለሰቦች እየመዘኑ እራሳችንን፣ ማህበረሰባችንን እና የወደፊት ግቦቻችንን እንዴት እንደምንረዳ ያለፈውን መረዳት እና ማስታወስ እንዳይኖረን “አምታች” ግለሰብ ነው።

ዛሬ ዛሬ የመጣ አዲስ ፖለቲካ ደግሞ በልደቱ ብቻ ሳይወሰን “ሞገስ ተሾመ ዘውዱ” የተባለ የገበታ ሚዲያ አዘጋጅ “አማራዎች ሲታረዱ አላውቅም ፤ ማን እንደሚያርዳቸውም አላውቅም”፤ አራጆችን “አራጆች” ብለን ባንጠራቸው ጥሩ ነው፤ የሚል ፤ “ምክንያቱሳ?” ተብሎ ሲየጠየቅ “ነገሩን 'ሲጅ' ማድረግ ነው ፤ ሁኔታውን ያባብሳል..” የሚል (ሁለት ሰዎች ተኝተው አንድ ጅብ መጥቶ አንድ እግሩን በልቶት ሁለተኛውን እግሩን እንዳይደግመው “ዝም እንበል” እንደሚለው ሰውየ፡ ዛሬ የበቀሉ ፖለቲከኞች ደግሞ “አራጆችን አራጆች ብንላቸው እንደገና እንዳያርዱና ተከታይ ትውልድም ያንን እንዳይደግም” የሚል የክሕደትና “የፍጅትን ክብደት የሚያሳንስ አዲስ የ2015/2016 ፖለቲካ ቅስቀሳ ብቅ ማለት ጀምሯል (አዲስ ባይሆንም ያንን በእነ ደመቀ መኮንን እና ተከታዮቹ ሲባል የነበረ ቢሆንም)።

 “ወያኔ” <<ሁሉም አማራ በየቀኑ አልገደለም፤ሁሉም አማራ ቢገድል ኖሮ አሁን አማራ የሚባል ባልኖረ ነበር>> የሚለው ልደቱ ወያኔ አማራ ሕዝብ ላይ በማኒፌስቶውና በተግባር “አማርኛ ቋንቋን ፤ ሰንደቃላማችንን፤ ኦርቶዶክስን፤ አማራን እና ኢትዮጵያን” አከርካሪያቸውን ለመስበር፤ ትግራይ ጫካ 17 አመት እና 27 አመት በመንግሥትት በተጠቀሱት ላይ ምን እንደፈጸመ ልደቱ ቢክድም ታሪክ ዘግቦታል።

ልደቱ እያደረገ ያለው “ወያኔ በባሕሪው ዋና የአማራ የዘር ጨፍጫፊነቱን ለመሸፈን የማይቻል ሆኖ ስላገኘው ያንን ግን “በዘዴ የወንጀሉን ክብደት ለመቀነስ” “የሚጠቀምበት” ሙግት ነው።  ልደቱ እንዲህ ያለ ሙግት ሲያቀርብ ወያኔዎች ንግግሩን ስለ ወደዱለት በወያኔው ዘፋኝ በጸረ አማራው “እያሱ በርሄ” የተዘፈነ “ክላሲክ ለስላሳ ሙዚቃ” እየታጀ እዚህ የተለጠፈው ቪዲዮ የለጠፉት ወያኔዎች ናቸው። ወያኔዎች ልደቱን እንደ ማስረጃ በመጠቀም ሃቁ ይሄው ነው እያሉን ነው።ልደቱ ዋናው ምስክራቸው ነው።

የልደቱ ክርክር፤ ወያኔ በአማራ ነገድ ላይ ያነጣጠረው የዘር ፍጅት ወንጀል ለማጣጣልና ለመካድ ነው። ለዚህም ሥርዓቱን በዘር አጥፊና “በነቲቭ ኮሎናይዘርነት” ሳይሆን ልደቱ የወያኔን ሥርዓት የሚጠራው “ዲሞክራቲክ የሆነ፤ የሰደቡትንም ጭምር የማያስር” የመጻፍ ፤የመናገር፤ ትችትን የፈቀደ፡ ነገር ግን <<የተዛባ ሥርዓት>> በሚል ነው የሚገልጸው።

አንባቢዎቼ ልብ ልትሉ የሚገባ “የየ አገሮች የፋሺስት እና የናዚ ባሕርያቶችን አካሄዶች እንደየ አገሩና ዘመኑ ይለያያሉ”። ልደቱ ይህንን ላለመጠቀም የግድ ባንድ ዘመን የተፈጸመው በሌላ አገር እና በሌላ ዘመን ተመሳሳይ እርምጃ መወሰድ ነበረበት የሚል “ፋውል ፍልስፍና” ይጠቀማል።

ልደቱ ከንቱ  ሰው ነው የምልትም “በተዛባ ሥርዓት” ውስጥ “አስተዳደራዊ ብልሽት” እንጂ “የዘር ጭፍጫፋ” አይካሄድም። የዘር ፍጅት የሚካሄድበት ሥርዓት “በዘር፤ በቋንቋ የሚያስተዳድር፤ በሃይማኖት፤ በቆዳ፤ በርዕዮተ ዓለም፤ በአገር ወረራ…” ልዕልና የሚያምን ቡድን ሲፈጠር ነው። የዘር ፍጅት የሚካሄድ “በተዛባ ሥርዓት” ውስጥ ሳይሆን “ሆን ተብሎ በውይይት ታቅዶበት ተመክሮበት፤ተዘጋጅቶበት አመቺ ሁኔታዎችን በመጠቀም አንድን ዘር/ነገድ/ብሔረሰብ የመኖር ሕልውናውን እያስጨነቀ የጥላን ትርክት እየተጎተተ ቀስ ብሎ እያደገ ከጥንት በቅሎ የሚመጣ ነው።

 ይህንን እውን ለማድረግ እንደ ጀርመን ናዚ ገጣሚዎችና የኪነት ሰዎች ወያኔዎችም አማራን ቀለብ ለማስገባት  በመጀመሪያው ማኒፌስቶውና በዘፈኖቹ እና በሚገጥማቸው ግጥሞቹ ሁሉ “አማራን ቀለበት ውስጥ” በማስገባት የዘር ፍጅት አካዷል። ፍጅት ለማካሄድ የታጠቀ የቡድን ልዕልናን ወይንም መንግሥትነትን ሲቆጣጠር ነው።  በጀርመን ውስጥም ናዚ ባስተዳዳራቸው አገሮች ሁሉ ሁሉም አይሁድ አልጨፈጨፈም። ባነዚ ባለሥልጣናት ቤት ውስጥ ተቀጥረው ሲሰሩ የነበሩ ይሁዶች በቀጣሪዎቻቸው ደግንትና (ባልተገለጸ ምክንያታቸው) ከሞት እንዲድኑ ያደረጉ ናዚዎች ነበሩ (ልደቱ ታጣፊ አላጋቸውን ይዘው ሥራ ውስጥ የሚያድሩ በጎ ወያኔዎች ነበሩ የሚላቸው አየነት፤ ‘’ምን ሲያደርግ እንዳያቸው’ ባይታወቅም)።

በስልት እና በድፍረት ፍርሓትን በመጋፈጥ “ኖርዲክ ጀርመን” መስለው አለፍ ብሎም አንዳንድ ጊዜ አይሁዶች ከአሰቃቂ እጣ ፈንታ ለመራቅ ሲሉ ሌሎች አይሁዳውያንን ያወግዙበት የነበረውን የውግዘት ባህል አንብበናል። “አለምነህ መኮንን” የመሰለ “አማራን ያወገዘና የተሳደበ” ወራዳ ግን በስልት ህይወቱን ለማዳን ሳይሆን ለማገልገል ቢሆንም ፡ ልደቱ ድሮ “አማራ አይደለሁም” ባለው አንደበቱ  ወያኔዎች ልደቱን በአማራነት ሳይሆን ያሰሩት (ታስሬ ነበር የሚለውን ንግግሩን) በሚያምታታው ፖለቲካው ነው።

 በሚገርም ሁኔታ ልደቱ  በተጫወተው የጮሌ ፖለቲካ ወያኔዎች “ሽጉጥ” አስታጥቀውታል፤ (ያንን አርሱም ሲክድ አልሰማንም) ፤ከዚያ እልፎ በወያኔ ናዚ ፓርላማ በመግባት በሚሰራው የጮሌ ፖለቲካ “መኖር ብቻ ሳይሆን ደሞዝ እንዲግጥ” ሲፈቀድለት ስለ አማራ ጭፍጨፋ የተቃወሙት አንጋፋ የሰብኣዊ ተሟጋቾች እንደ እነ ሐኪም አስራት ወልደየስ እና ብዙ ሰዎች  ግን ተገድለዋል።

ልደቱ የወያኔም ሆኑ የናዚዎችና የፋሺሰቶች ባሕሪ የኖሩበት ዘመንና የጭካኔ አዋሳሰድ ስልቶችና ልዩነቶችን ሳይለይ ወያኔ እና ናዚዎችን ባንድ መደብ በመመደብ የግድ ሁለቱም ዘር አጥፊዎች ከሆኑ አንድ አይነት አፈጻጻምና ጭካኔ መታየት ነበረበት የሚል የልደቱ የክርክር አዝማሚያ “ወያኔ ናዚ አይደለም፤ ወይንም ዘር አጥፊ አይደለም” ስለሆነም መላው አማራ ስላላጠፋ ወያኔ ናዚ ሊሆን አይችልም ነው ክርክሩ።

ልደቱ በለመደው ምላሱ አንዴ አማራ አይደለሁም ይልና ቆየት ብሎም “እኔ አማራ ነኝ” ከሚለው እና እዚህ በዚህ ቪዲዮ የምናደምጠው አማራ በየቀኑ አልተገለደም ከማለት አልፎ ፤ ሁሉም አማራ ቢገደል ኖሮ እዚህ ድረስ አሁን አማራ የሚባለው ዘር አይኖርም ነበር” ከማለት ተሻግሮ “አዎ አማራ የዘር ጥቃት ተፈጽሞበታል ስለዚህ አሁን ፋኖ እያደረገው ያለው ትግል የሕልውና ትግል ነው” የሚለው ተለዋዋጭ ንግግሩ የሚያሳይን ከጊዜው ጋር የሚገለባበጥ እራሱን ለማመጻደቅ ‘አቋሜ አንድ ነው’ ይበል እንጂ “ተለዋዋጭና አቋመ ቢስ” ነው”።

መካድ የዘር ማጥፋት ዋና አካል ሲሆን ፣ በተለይም ክሕደት የዘር ማጥፋት ዘመቻው እየተካሄደ ባለበት ወቅት/ዘመንፕሮፓጋንዳ” እናየጅምላ ግድያ ማስረጃዎችን ከመደበቅ” ጀምሮ እስከ የልደቱ አይነት “ሁሉም አማራ በጅምላ አልተገደለም” የማስተባበያ ንግግርን ክሕደት ውስጥ ይጠቃለላል

ልደቱ ይጥላው አይቀበለው deliberate mass murder (ሆን ተብሎ የጅምላ ጭፍጫፋ በወያኔ ዘመን አማራው ላይ ተካሂዷል። “ሁሉም አማራ በየቀኑ አልተገደለም” የልደቱ የወያኔ ጥብቅና ወያኔን ከጅምላ ገዳይነቱ ነፃ አያወጣውም።የወያኔም ሆነ የናዚ ጀርመን የጅምላ እልቂት ስልታዊና  በመንግስት የተደገፈ “state-sponsored” ፍጅት  ነበር። ልደቱ በየቀኑ አማራ አልተገደለም ክርክሩን ትምሕርት ቢሆነው የወዳጄ ሐኪም ዶክተር አሰፋ ነጋሽ  << PERPETRATING GENOCIDE OR PROMOTING FAMILY PLANNING? THE UNETHICAL USE OF BIRTH CONTROL PROGRAM AS INSTRUMENT OF AMARA ETHNOCIDE by Assefa Negash, M.D.Amstelveen, Holland – the 17th of July 2017) >> የሚለው ጽሑፍ እንዲመለከት እጋብዘዋለሁ። ይህ የናዚና የወየኔ የፍጅት ስልት አንደነትን ያሳል።

ይህ ብቻ ሳይሆን << Why Have the Amaras Once Again Become Victims of Ethnic Cleansing by TPLF? By Assefa Negash, M.D. 18th of April 2012 >> የሚለውም ጉጉል በማድረግ ልደቱ እንዲመለከተውና እራሱ ልደቱም << እኔ እየነበርኩበት ባለው አዲስ አባባ  ኢትዮጵያ ውስጥ ነው አማራ ሁሉ እየተፈጀ ነው፤ ትግሬ ሁሉ እየተጠቀመ ነው፤ የሚለው የውሸት ትርክት እተነገረ ያለው?>> ስለሚለው የልደቱ ውዥምብራም ክርክሩ የዶ/ር አሰፋ ጽሑፍ ይረዳዋልና ይመልከተው።

 ጀርመን ውስጥ የይሁዲ “ጥላቻ” የጀመረው “ሆሎካስት/ጀነሳይድ/ የሚባለው ፍጅት” ከመከሰቱ በፊት አውሮጳ ውስጥ ለዘመናት የተከሰተ ነበር፤ ትግራይ ውስጥም ወያኔ ወደ መንግሥትነት ከመምጣቱ በፊትና ፍጅቱን ከማካሄዱ በፊት ትግራይ ውስጥ ለዘመናት በዮሐንስና በምንሊክ ዘመን (ሸዌና ትግሬ የሚል የትግራይ ጠባብ ብሔረተኞች “ንጉሥነታችንን ተነጠቅን” ከሚለው ትርክት) ጀምሮ ብቻ ሳይሆን አንዳንዶቹ ወደ 13ኛው እና 14ኛው ክፍለ ዘምን በአምደጽዮን እና በዘመነ ዘርአ  ያቆብ ዘመን በመውሰድ “በትግሬና አማራ” ጥላቻ እንደተጀምረ የወያኔ ናዚዎች በመጽሕፍታቸው ጠቅሰውታል። ስለዚህ ዕቅዱ ሲጋተት በሂደት እየጎለበተ የመጣ “ወያኔ የተረከበው ጥላቻ” መንግሥት ሲሆን ጥላቻውን ወደ የዘር ፍጅት አሳድጎ “ተግብሮታል”።

ስለዚህ አማራ በማኒፌሰቶው አማራን በጥቃት ኢላማ “ሲያስቀምጥ አላነበብኩም” የሚለን ልደቱ አያሌው እና ዛሬ አማራ ለምን በወያኔ ቀለበት ለጥቃት ተጋለጠ ብላችሁ ግራ ለምትጋቡ መልሱ ከላይ የጠቀስኩት ነው (የትግራይ ብሔረተኞች በአማራ ላይ ያላቸው ጥላቻ ከምን የመነጨ ነው?” በሚለው መጽሐፌ  ውስጥ በሰፊው አሳይቻለሁ። ወያኔ አማራን ለመጨፍጨፍ ማኒፌሰቶ አላስፈለገውም ነበር። በማኒፌሰቶ ተነደገፍም አልተነደፈም ጀርመኖት በይሁዶች ከጭፍጨፋው በፊት አውሮጳ ውስጥ ጥላቻቸው ተንሰራፍቶ እንደነበር ሁሉ “ትግሬዎችም” በአማራ ላይ ሥር የሰደደ የንግሥና ቁርቁሳቸው አማራን በጥላቻ ቀለበት ማስገባት የጀመሩት በ1967 የጀመረ ሳይሆን በ13ኛው እና 14ኛው ክ/ዘመን እንደነበር ሳይደብቁ ጽፈውታል።

 ልደቱም እግረመንገዱን ይህንን ቢመረምር ጥሩ ነው። ነገዶች “የግድ” እደግመዋለሁ “የግድ” እንደ እነ ዚያኛዎቹ የ16ኘው ክፍለ ዘመን የታየው በከብት አርቢዎቹ ወራሪዎች ቢላዋ ከምድረገጽ የጠፉት 26 ብሔረሰብ ጎሳዎች ለምን አማራ ዛሬም እንደነሱ ሊጠፋ አልቻለም የሚለው የልደቱ ከንቱ ሙግት ዘመኑና የክፍለዘመኑ የግድያ ስልት፤ ብስለት፤ ዓለም አቀፍ ሕግና “ስልታዊ ጥንቃቄ” ልዩነት መኖሩን ያላገናዘበ ሙግት ነው።

ስለሆነም ሁሉም አማራ በየቀኑ አልተጨፈጨፈም፤ሁሉም አማራ አልተገደለም፤ የሚለው የልደቱ ከንቱ የወያኔ ውዳሴ፤ ለምን በጸጉር ስንጠቃ መራቀቀቅ ውስጥ መግባት እንዳስፈለገው ባይገባኝም፤ ወያኔ መላው አማራ “ዛሬም ድረስ እየተካሄደበት ያለው የጅምላ ጭፍጨፋና” በአማራ ማሕበረሰብ ህይወት ላይ ያሳደረው የ48 አመት << ቱራማ ፤ ፍጅትና ስደት>>  ወያኔ ከዘር ማጥፋት ወንጀለኛነቱን ነጻ አያደርገውም።አንብበው ከጨረሱ በላ ቪዲዮውን ከታች ይመልከቱ

አመሰግናለሁ

ጌታቸው ረዳ (Ethiopian Semay)