Tuesday, August 20, 2019

ትንቢትን በሤራና በግድያ ማስቀረት አይቻልም! ትንቢቱ ደረሰ (ከአዲስ አበባ) Posted at Ethio Semay


ትንቢትን በሤራና በግድያ ማስቀረት አይቻልም!
ትንቢቱ ደረሰ (ከአዲስ አበባ)
Posted at Ethio Semay
የባህር ዳሩን የአማራ ባለሥልጣናት ጭፍጨፋ አስመልክቶ ሄኖክ የሽጥላ በዩቲዩብ ያቀረበውን ሀተታ ተከታተልኩ፡፡ እነአቢይና ወያኔዎች ይህን ግድያ ማቀነባበራቸውን በፊትም የምንጠረጥረው ነገር ነው፡፡ በተለያዩ አጋጣሚዎች እንደተገለጸው የአማራ ጠላቶች እጅግ ከመብዛታቸውም በተጨማሪ አንዳንድ ወፍዘራሾች “ከናካቴው የለም” የሚሉትን ይህን ጎሣ በማጥፋት ረገድ ሁሉም ይተባበራሉ -- እነሱ ራሳቸው የማይስማሙና እንደዐይጥና ድመት አጥፊና ጠፊ  ሆነውም ቢሆን - ቤንዚንና እሳት ሆነውም ቢሆን በአማራ ላይ ያላቸው አቋም ግን አንድ ነው - ይህንን የኢትዮጵያ አለኝታ ነገድ ከሥሩ መንግሎ ማጥፋት፡ - ትልቅ ምክንያትም አላቸው - እርሱ ወደ ሥልጣን ከመጣ እንደልባቸው የሚዘባነኑበት በሙስናና በዘረፋ የሚገኝ የሀገር ሀብት፣  ለየደናቁርት የጎሣ አባሎቻቸው እንደገና ዳቦ እንዳፈተታቸው የሚያቃርጡት የይስሙላው የፌዴራል ሥልጣን አይኖርም፤ “ወርቃማ ጊዚያችን ይህች ናት!” ብለው ስለሚያምኑ ይህን የኳስ አበደች ዘመን በፍቅር ይወዱታል - በዚህ ዘመን የሚመጣባቸውን ሁሉ ግም ለግም እየተረዳዱ “አንድ ሰውና አንድ ጥይት” እስኪቀራቸው ይዋጉታል፡፡ ለዚህም ነው “በህገ መንግሥታችን አንደራደርም” በሚል እንደ አሠርቱ ትዕዛዛት ጉያቸው ውስጥ ወትፈው ያን ከሽንት ቤት ወረቀትነት ያነሰ ዋጋ ያለውን ሕወሓታዊ ሠነድ ጣዖታዊ ቤተ መቅደሳቸው ውስጥ አኑረው የሚፎክሩበት፡፡

 አማራ ካልጠፋላቸው ዕንቅልፍ የሚባል በዐይናቸው አይዞርም፡፡ እነዚህ የአማራ ጠላቶች የትግራይ ወያኔዎችና የኦሮሞ ኦነጋውያን ናቸው፡፡ እነዚህን የሚያሰማሩ የአዲሱ ዓለም ሥርዓት አዋላጅ የሆኑት ኢሉሚናቲዎችም መዘንጋት የለባቸውም (The so called  Illuminati who are by now at the(ir) peak to form the New World Order after destroying nearly 80% of the world’s population....)፡፡ እነዚህን ፍናፍንት ዜጎች በአማራ ጠላትነት እያነሳሱና እያደራጁ፣ በበጀትና በዘመናዊ ጦር መሣሪያም እያጠናከሩ፣ ዘመናዊ የሣተላይት መረጃ እየመገቡ በኢትዮጵያ ላይ ጃዝ ብለው ይለቋቸዋል፡፡ ይህም ትንቢቱ ይፈጸም ዘንድ ነው፡፡ የፈዘዝነውም ሆነ የተበታተንነው ትንቢቱ ይፈጸም ዘንድ ነው፡፡ አንድ ያልሆነውም ሆነ በትንሹም በትልቁም የምንንነታረከው ትንቢቱ ይፈጸም ዘንድ ነው፡፡ ብዙ ሆነን ሳለ ጥቂት የሆንነው፣ ኃያል ሆነን ሳለ ደካማ የሆንነው፣ ሀብታም ሆነን ሳለ ድሃ የሆንነው፣ አንበሣ ሆነን ሳለ ከዝንጀሮም ያነስነው ትንቢቱ ይፈጸም ዘንድ ነው፡፡ ይህን ካልኩ ዘንዳ የትንቢቱን ፍጻሜ ልንገርህ፡፡ የምታውቁትን ነገር እንደአዲስ በመቁጠር “ያበጠው ይፈንዳ” በሚል  ብሂል ቆዳየን አላዋድድም፡፡ እውነቱ ግን ይሄው ነው፡፡ ጠላቶችም መከራቸውን የሚያዩትና ከዳር እዳር ኅብረት ፈጥረው አማራንና የአማራን ብቸኛ መመኪያ ኢትዮጵያን ከምድረ ገጽ ለማጥፋት የሚራወጡት የመጨረሻውን ትንቢት እነሱም ስለሚያውቁና ያንን የማይቀር ትንቢት የቀለበሱ መስሏቸው ነው፡፡ ይህን እያስገመገመ በመምጣት ላይ የሚገኝን ገሃድ እውነት መናገር ድፍረት ሊመስል ይችላል፡፡ ግን ምንም ማድረግ አልችልም፡፡

አማራ ማንሠራራቱ ዕንቅልፍ እንደነሳቸው ገልጸናል፡፡ እነአሣምነው እየተጓዙበት የነበረው ሀገርን የመፍጠር እንቅስቃሴ እነአቢይንና አክራሪ ኦሮሞዎችን፣ አክራሪ ትግሬዎችን፣ ከየጎሣው ያሉ ሆዳምና ነቀዝ ዜጎችን በጠቅላላው ዕረፍት ነስቷቸው ነበር፡፡ ስለዚህም ያንን ግልጽ የግድያ ዘመቻ ካላንዳች ይሉኝታና ሀፍረት በመፈንቅለ መንግሥት ሰበብ ማካሄድ ነበረባቸው - ያ “ዓለም አቀፍ ማኅበረሰብ” የምንለው የኢሉሚናቲዎች ጭምብልም ከጎናቸው ስለሆነ ማንንም አይፈሩም፤ አያፍሩምም፡፡ “የማይመስል ነገር ለሚስትህ አትንገር” ይባላል፡፡ እነአቢይ የሚገድሉትን ሁሉ ከገደሉና መረጃ ካጠፉ በኋላ ያን ከእውነት የራቀ ነገር መደስኮራቸው በሕዝብ ንቃተ ኅሊና ላይ ጢባጢቤ ከመጫወታቸውም በላይ የነሱን ማይማዊ ዕብሪት አጉልቶ ያሳያል፡፡ አክራሪ ኦሮሞዎች በከሚሴና በቤንሻንጉል ጉሙዝ በኩል ሊሠሩት ያቀዱትንና የጀመሩትንም አማራን በጎጥና በሸንተረር የመከፋፈል እንዲሁም በሳል አመራር የማሳጣት እንቅስቃሴ እነአሣምነው ቀድመው ነቅተውባቸው ሊያከሽፉባቸው በመነሳታቸው በአማራ ልሂቃንና አመራሮች ላይ ያ ሁሉ ውርጅብኝ ወረደ፡፡ መሆን ስለነበረበት ነው የሆነው ብለን በአርምሞ እንቀበለዋለን፡፡ አንድ መሆን ያለበት ነገር ደግሞ ይዘገያል እንጂ ከመሆን አይዘልም፡፡ አሁን እንደምንሰማው ያ በአክራሪ ወያኔዎችና ኦህዲድ/ኦነጎች የተጠነሰሰ ዘመቻ “ዘመቻ ቅንጸላ” ይባል ነበር፡፡

ቅንጸላ ምን ማለት እንደሆነ በውል አላውቀውም፡፡እንደሚመስለኝ  ግን “ማምከን፣ ማስቀረት፣ መቀምጠል፣ ማጉደል፣ ማክሸፍ...” ሳይሆን አይቀርም፡፡ የአማራን ትንሣኤ ለማስተጓጎልና እስከወዲያኛው ለመቅበር የተደረገ ሙከራ እንደሆነ ወዲያና ወዲህ ከሚያቅነዘንዛቸው ዕረፍት ያጣ ተግባራቸው መገንዘብ ይቻላል፡፡ አሁን አሁንማ ይሠሩትን አጥተዋል፡፡

ይህ አማራን የማጥፋት ሁለገብ ዘመቻ በነአቢይ አህመድ ይመራ እንጂ አንዳንድ ሆዳም የብአዴን አባላትም የጥፋት ዘመቻውን መተባበራቸው የታወቀ ነው፡፡ ዱሮውንም ሆዳም ፍቅር አያውቅም፡፡ ሆዳም ሚስቱንም፣ ልጁንም፣ አባቱንም፣ እናቱንም ለገንዘብና ለጥቅም አሳልፎ ይሸጣል፡፡ ይሁዳ ጌታውን በ30 አላድ እንደሸጠ ሁሉ የባሰበት ሆዳም አማራም አማራን አይሸጥም ተብሎ አይታሰብም፡፡ የአማራ መከራ የበዛው የራሱ ልጆች ሳይቀሩ ከታሪካዊው ጠላቶቹ ጋር በመተባበር ለከርሳቸው ሲሉ ስለሸጡት ነው፡፡ ያለ ነው፡፡ ወደፊትም ይህን መሰሉ አስቀያሚ ክህደትና ሽርሙጥና አይቀርም፡፡ ዋጋቸው ግን በሠፈሩት ቁና ልክ ይሠፈራል፡፡ እንጂ ለክህደት ለክህደትማ እነክፍሌ ወዳጆንና ገነት ዘውዴን ማን ይረሳቸዋል?

ዘመቻ ቅንጸላ ያደረገውን አድርጎ ለጊዜው የተሣካ ይመስላል፡፡ በዚያም ምክንያት በአማራው አካባቢ አሁን ለጊዜው መፍዘዝ ይታያል፡፡ ግን በዚህ መልክ አይቀጥልም፡፡ ምክንያቱም ትንቢቱ ደርሷልና፡፡ ንግርት ቢዘገይ እንጂ አይቀርም፡፡

ይህ ነው ትንቢቱ፡፡ መጀመሪያ ከሰሜን የመጡ አንበጦች ኢትዮጵያን እንደተምች ይወሯታል፡፡ ወርረውም እስከ አጥንቷ ይግጧታል፡፡ መሣሪያ ከትከሻቸው የማይወርድ እረኞች በሽምብራ ዛፍ ሥር ተቀምጠው ጠማማ ፍርድን ይሰጣሉ፡፡ እህል በሸሃኔ ይሠፈራል፡፡ ቀጣና ይበዛል፡፡ ርሀብና መከራ ይናኛል፡፡ ትልቅ ሰው ይዋረዳል፤ ትንሽ ሰው ይከበራል፡፡ በመጨረሻቸው ግን እነዚያ ጉዶች እንደጢስ በንነው፣ እንደጤዛ ረግፈው ይጠፋሉ፡፡ ይህን አሁን አይደለም እኛ የምንለው፡፡ ከልጅነታችን ጀምሮ በ50 እና 60ዎቹ ዕድሜ የምንገኝ ሁሉ የምናውቀው የቅርብ ዘመን ትውስታ ነው፡፡

ቀጥሎ ፊጋ ከብቶች ባዶውን በረት ይወርሳሉ፡፡ ለተወሰነ ጊዜም ባዶ ያገኙትን በረት እውነት መስሏቸው እምቡር እምቡር ይሉበታል፡፡ ዕውቀትና ጥበብ ባለፈበት መንገድ ያላለፉ የለዬላቸው ነፈዞች ናቸው፡፡ መሪያቸው ሃይማኖት የለውም፡፡ አለው ቢባልም ማስመሰያ እንጂ ከአንጀት አይደለም፡፡ ዕድሜው ከሦስት ዓመታት አያልፍም፡፡ የነሱም የመጨረሻ ዕጣ ልክ እንደአንበጣዎቹ ይሆንና ባላሰቡትና ባልጠበቁት ሁኔታ አከርካሪያቸውን ተመትተው ወደ ታሪክ ትቢያነት ይለወጣሉ፡፡ ያንን ጊዜ አንተ ወይም አንቺና እኔ ላናየው ብንችልም የማይቀር ስለመሆኑ ግን የዮዲትና የግራኝ አህመድ ወይም የመንግሥቱና የመለስ karmic  መጻሕፍት  ምሥክሮቼ ናቸው፡፡ ይህ እውነት መሃላ የማያሻው አጠቃላይ እውነት ነው፡፡

በመጨረሻው መጨረሻ እውነተኛ ኢትዮጵያውያን ከያሉበት ተጠራርተውና ኃይላቸውን አስተባብረው ኢትዮጵያን ይረከባሉ፡፡ በነሱም የኢትዮጵያ የቀድሞ ክብር ይመለሳል፡፡ ያም ጊዜ እጅግ ቀርቧል፡፡ይህን እውነት መናገር ማንንም አይጎዳም፤ ለማንምም የሥጋት መንስኤ ሊሆን አይችልም፡፡ እንዲያውም የምሥራች ነው፡፡ ለወፍ አራሾች ግን መርዶ ነው፡፡ (ባይገርምህ እናትና ልጅም ተገናኝተው ጥጃዋ ከእህትና ወንድሞቿ ጋር የእናቷን ጡት የምትጠባበት ጊዜ ይመጣል፡፡ ምን ያስቅሃል?)


እነዚህ የአሁኖቹ ከንቱዎችና ጌቶቻቸው ወያኔዎች ግን ትልቅ ጉዳት ያደርሳሉ፡፡ የነሱን የዓመታት መርዝ ለመንቀል ብዙ ትግልን ይጠይቃል፡፡ ብዙ ሕዝብ መስዋዕት ይሆናል፡፡ የደም ጎርፍ የማናመልጠው ዕዳችን ይሆናል፡፡ “ለኃጥኣን የመጣ ለፃድቃን ይተርፋል” እንዲሉ ነውና ብዙ አሣር ያገኘናል፡፡ መስዋዕቱን ለመቀነስ እንዲቻል (ትንቢትን ማስቀረት ባይቻልም) ወደ ፈጣሪ ተመልሰን በፆምና በጸሎት ብዙ መድከም ይኖርብናል፡፡ ኢትዮጵያ ቃል የተገባላት ምድር ናት፡፡ ጠላቶቿ ቀበርናት ሲሉ አፈሯን አራግፋ የምትነሣ፣ ገደልናት ሲሉ የምትድን ልዩ ሀገር እንደሆነች በተደጋጋሚ አስመስክራለች፡፡ ስለዚህ ምንም እንኳን ብዙ ዕልቂት ቢኖርም ከህመሟ ተፈውሳ በሚተርፏት ጥቂት ዜጎች ልዕልናዋን እንደገና ታስከብራለች፡፡ አራሙቻዎችም ተጠራርገው የጨለማው ንጉሥ ግዛት ወደሆነው ወደ መጡበት መቀመቅ ይወርዳሉ፡፡

   
በየከተሞች የሚታየው የሴቴኒዝም እምነትም በነፃነታችን ቶሎ አለመምጣት ላይ የበኩሉን ጽላሎት ማሳረፉ አይቀርም፡፡ ከጥግ እስከጥግ የቆሸሸውና በዘረኝነት፣ በሙስናና በድንቁርና የተበከለው ቤተ መንግሥታችን ብቻ አይደለም፡፡ ቤተ ክርስቲያንንና የእምነት ቤቶችን በጥቅሉ ሰይጣን ስለተቆጣጠራቸው እውነተኛ እረኞች የሉንም፡፡ ሰይጣን የሮማ ካቶሊክ ቤተ ክርስያንን ጨምሮ የእስክንድርያዋንና የኢትዮጵያዋን ኦርቶዶክስ ሙሉ በሙሉ ሊባል በሚችል ደረጃ ተቆጣጥሯል፡፡ ልጅ እየወለደ በድብቅና አንዳንዴም ልክ እንደቫቲካኑ የ15ኛው መቶ ክፍለ ዘመን አንድ ሊቀ ጳጳስ (ፖፕ ሮድሪጎ) በማንአለብኝነት በግልጽ የሚያሳድግ ፓትርያርክና ጳጳስ ባለባት ሀገራችን ውስጥ የእግዚአብሔር በረከትና ጥበቃ በቀላሉ ይገኛል ማለት ቀልድ ነው፡፡ በዚህ ዘመን መዳን ከባድ ነው፡፡ ይህ ሁሉ ግፍና በደል እየተሠራ እያለ አንድም የሃይማኖት አባት በግልጽ ወጥቶ አይቃወምም፤ ቂጡ ላይ ቁስል ያለበት ውሻ እንደልቡ አይጮህም፤ ፈስ ያለበትም ዝላይ አይችልም፡፡ “አባቶቻችን”ም በጠባያቸው ሰይጣናዊነት የተነሣ ፀጋ እግዚአብሔር ጎድሏቸዋልና በጎቻቸውን ተኩላና ቀበሮ ሲቦተራርፍ፣ ሀገርን ማንም ወስላታና ወለፈንዴ ፖለቲከኛ ነኝ ባይ ሲጫወትባት ትንፍሽ አይሉም፡፡ ምክንያቱም በሆነ ነገር አፋቸው ተሸብቧል፡፡ ለነፍሳቸው ያደሩ እንደነ አቡነ ጴጥሮስ ያሉ አባቶች ሞታቸው ሰማዕትነት እንጂ ተራ ዓለማዊ የሥጋ ሞት እንዳልሆነ ስለሚረዱ እውነትን መስክረው በጥይት ተደብድበው ሞተዋል፡፡ አሁን ግን የምዕመናንንና የሕንጻ ቤተ ክርስቲያን ማሠሪያ ገንዘብ እየዘረፉ፣ በዘረኝነት አሮንቃ እየዳከሩና በሴሰኝነት የወሲብ ንዳድ እየነፈሩ ስለነፍስና ስለሀገር ማሰብ የማይቻል በመሆኑ ቤተ ክርስቲያን በቅርጽ እንጂ በይዘት የለችም - የምለው ሀሰት ቢሆን ጌታ ይፍረድብኝ (ባይባልም አንዳንዶችን ደስ እንዲላቸው ግዴለም ልበለው)፡፡ ድንጋይ ይክባሉ እንጂ አእምሮ ላይ የሚሠሩት አንዳችም ነገር የለም፤ የነሱ የራሳቸው አእምሮም ባዶ ቀፎ ነው፡፡ አብዛኛው ካህንና ደብተራ ዐይኑ የሚጎለጎለው፣ መረዋ ድምጹ የሚጎላው፣ ቅኔውና ወረብ ሽብሸባው የሚሠምረው ገንዘብ ላይ ነው፡፡ ከሁለት ሰዓት የዐውደ ምሕረት ስብከት ውስጥ 30 እና 40 ደቂቃው ብቻ በተግባር ለማይተረጎም ሃይማኖታዊ ቃል የሚውል ሆኖ ሌላው ገንዘብ ስጡ ላይ ነው - መስጠት ብቻውን ያጸድቅ ይመስል፡፡ “ብዙ አየን” አለች አሉ ቦለቅያ፡፡



እንግዲህ እውነቱ እንዲህ ነው፡፡ ሴቴኒዝምን እንዋጋ፡፡ ዝርዝሩን መናገር ለቀባሪ ማርዳት ነው( Romans 1:18-32, Leviticus 20:13, 1 Corinthians 6:9-10, 1 Timothy. 1:9-10)፡፡ ነገር ግን ይህ የጨለማ ዘመን በቶሎ እንዲነጋ ለማድረግ የእውነት ዘገርን እንጨብጥ፡፡ ከላይ እስከታች የሠፈነውን ሙስና እንዋጋ፡፡ በመደበኛ ገቢያችን መኖርን እንለማመድ፡፡ በልጆች አእምሮ ላይ ብዙ እንሥራ፡፡ እንደሀገርም እንደሕዝብም እየጠፋን ነውና ከተሳሳተ መንገድ በቶሎ እንመለስ፡፡ ከሰሞነኛ ቅሌታችን ብጠቅስ ለምሣሌ - ፈተናን እየሠረቅንና በመምህራን እያሠራን መልስ በመበተን ትውልድን ከማደደብ በላይ ምን ወንጀል አለ? በምግብና በልብስ እንዲሁም በሌሎች የንግድ ዕቃዎች የሚሠራውን ፌክና አሻጥር አናንሳው፡፡ የጀሦና የሴጋቱራን እንጀራ፣ የቀይ ሸክላ በርበሬንና የሞራ ቅቤን  መመገብ ለምደን ሰው መሆን ቢያቅተን በርግጥም አይፈረደብንም፡፡ የምንገርም ሆነናል እኮ .... ሀገርና ሕዝብ በ30 ዓመታት ውስጥ ብቻ መጥፋት የሚችሉ ተራ ነገሮች ናቸው ማለት ነው?



ከነአቢይ አህመድ የሕይወት መመርያ ቀጣዩን ለአብነት ያህል እንመልከት፡-

Politics has nothing in common with moral. The ruler who is governed by the moral is not a skilled politician, and is therefore unstable on his throne. He who wishes to rule must have recourse to both cunning and to make believe. Great national qualities, like frankness and honesty, are vices in politics, for they bring down rulers from their thrones more effectively and more certainly than the most powerful enemy. (Source: Secret Societies and their Power in the 20th Century, by Jan Van Helsing)


ለዚህ ነው የሁሉም ችግር ማስወገጃ መንገዳቸው ውቃው ሆኖ የቀረው፡፡ ሰው ሰው የማይሸት ፖለቲካና ሃይማኖት፣ ከምክንያት ይልቅ ከራስ ወዳድነትና ከስግብግብነት ጋር የተቆራኘ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተራክቦ ገጥሞን ወደ ሮቦትነት እየተለወጥን ነውና ጨርሰን ሳንጠፋ እንምከር፤ እንነጋገር፤ ለዚሁ ጉዳይ መድረኮችም ይዘጋጁ፡፡ የኑሮ ውድነቱንም ለማብረድ ወደ ሰውነት እንመለስ፡፡ ሰውነት እጅጉን ርቆናል፤ ናፍቆናልም፡፡




No comments: