Saturday, November 1, 2008

“አሰከ መገንጠል” ሞግዚት ላጣች አገር የተመረጠ የመግደያ መርዝ

“አሰከ መገንጠል” ሞግዚት ላጣች አገር የተመረጠ የመግደያ መርዝ
ጌታቸዉ ረዳ ባለፈዉ ርዕሴ ማርክሲዝም እና ሌኒኒዝም አገርንና ሕዝበን አስመልከቶ እነ ዋለልኝ እና ስለተራማጆቹ ተማሪዎች እንቅስቃሴ በመጠኑ አንስቼ ነበር። የኔ ትንተና እስከ ዕንጥላቸዉ የሞላባቸዉ አንዳንድ ምሁራኖቻችን ላይጥማቸዉ ቢሆንም በዛዉ አንጻር የወደዱት እንደነበሩም ከተላኩልኝ በርከት ያሉ የግል ደብዳቤዎች መረዳት ችያለሁ። ማርክሲዝም መጥፎም ደግም አለበትና እንደ “ሽቱ” አንዱ ሲወደዉ ሌላ ሊጠላዉ ስለሚችል ሁሉም ይረብርበዉ ማለት አይቻልምና በልዩነታችን እንቀጥል።
ክፍል 1 ትንታኔየ በአንድ ድረ-ገጽ “በማሕደር.ዳት ካም” ብቻ ሲለጠፍ “በአሲምባ እና በደብተራዉ” ድረ-ገጽ ግን የላኩሁላቸዉ መሆነኔን ቢታወቅም “አልወደዱትምና” አንባቢ “ግንዛቤዉ” እንዲያሳርፍበት “አገዱት”። ለምን ለሕዝብ እናዳለቀረቡት ደፍሬ ባልጠይቃቸዉም፤የቁርጥ ቀን ወንድሞቼ ናቸዉና ቅር አላለኝም። ደግነቱ የራሴዉ የሕዋ ሰሌዳ መኖሩ በበቂ አንባቢ መነበቡ ከተዘገቡት የእንግዶች ቁጥር መቀበያ ማወቅ ችያለሁና ክፍል ሁለት የመጨረሻዉ ትንታኔየ ዛሬ ይቀርብና ወደ ሌላ ርዕስ እንሸጋገራለን።
ማርክሲስቶች እና ስታሊኒሰቶች አስካሉ ድረስ ዛሬም ኢትዮጵያን በጣረሞት አፋፍ ላይ ሰቅዞ የያዛት ብሔር/ብሐረስብ እስከመገንጠል የሚባለዉ መርዛቸዉ ዛሬም ለወደፊቱም ከመፈታተን ስለማይቦዝን ከሁሉም በፊት በቅድሚያ የሚቀርብ የፖለቲካ አጀንዳ ነዉና ይህነኑ አስመልከቶ እንወያያለን። በዚህ ክርክር ዛሬም ለወደፊትም ሁሌም የሚጠብቀን ደንቃራ ፈተና ነዉና እያንዳንዳችን ራሳችንን ማዘጋጀት ይጠበቅብናል።
በኢትዮጵያ ታሪክም ሆነ በአፍሪቃ የማይታወቀዉ እንግዳ የማርክሲሲቶች የብሔሮች፤ብሔረሰቦች፤ሕዘቦች… መብት “አስከ መገንጠል” ፍልስፍና በኢትዮጵያ ተማሪዎች እንቅስቃሴ እና ግስጋሴ ማርክሲስቶቹ ቀዳሚ መመሪያ አድርገዉ ተግባራዊ ለማድረግ ብዙ ትግል እና ትምህርት ሰጥተዋል። በዚህ በኩል በግምባር የሚጠቀሱ ቀን ቀንቷቸዉ ወደ ስልጣን የመጡት እነ ወያኔ እና ለአንድ ዓመት በላይ ቢሆን አብሮት ስልጣን ላይ ወጥቶ ከፍተኛ ብሔራዊ ጉዳት ያደረሰዉ የሌንጮ ለታ “ሃይማኖት” የነበረዉ “ኦነግ” የተባለዉ ወንጀለኛ የፓለቲካ ድርጅት አማርኛን በላቲንና በዓረብኛ ቋንቋ ተክተዉ የብሔሮች መብት አስከ መገንጠል በሕገመንግሥት አጽድቀዉ የኢትዮጵያዊነት ስሜት ከህዝቡ መንፈስ እንዲገፈፍ ከፈተኛ ጉዳትና ሚና ተጫዉተዋል። (በነገራችን ላይ ሌንጮ የኮሎኒዉ ጥያቄ ያፍላ ወጣትነት የማርክሲስቶች ንቃተ ሕሊና ቅስቀሳችን ስለነበር ዛሬ አርጅቼ ልብ ገዝቻለሁና የኮሎኒዉ ጥያቄ ጥየዋለሁ በማለት በብርሃኑ እና በአንዳርጋቸዉ ራዲዮን በሰጠዉ ቃለ መጠይቅ ማረጋገጡ አንድ እርምጃ ነዉ። አዘጋጁ አፍላ የራዲዮን አዘጋጅ በመሆኑ ወይም ሌንጮንና የኦነግ ታሪክ ካለማወቅ ይመስለኛል “እንደርስዎ ያለ የፖለቲካ ስብዕና የተላበሰ…” በማለት ቢያመካሸዉም፤ ሌንጮ ሸርተቴ ነዉና ለማንኛዉም እቀድመን ከመካብ ተቆጥበን በጊዜ የሚታይ ነዉና ሂደቱን በንቃት እንከታተል።)
ብሔር/ብሔረስብ አስከ-መገንጠል የሚለዉ የስታሊኒስቶች መመሪያ “ኦሪት” ለሆነችዉ አገራችን የዉጭ ጠላቶች -እና የቆየ የሙሶሊኒ ከፋፋይ መምሪያ ተግባራዊ ለማድረግ የተወሰነዉ ካሁን በፊት በጦር ሞክረዋት አልሳካ ያላቸዉን መርዛማዉ የመገነጣጠል ሴራቸዉ ዛሬ ያላንዳች የዉጭ አስፈራሪነት በልጆቿ እጅ መርዙን ተግታ/ጠጥታ እንድትሞት ተደርጎ፤ ሞቷ ጊዜ ፈጅቶ ቀስ በቀስ እየኮሰመነች ብሔራዊ ሃይሏ እየተዳከመ ሕዝቦቿ እርስ በርስ በስድብ እየተቦጫጨቁ ጥላቻዉ ተስፋፍቶ መጨረሻ ግብአተ መሬቷ ከጊዜዉ እና ከመንፈስ መዳከም ጋር እንደሚከናወን እየተፈጸሙ ያሉ ሂደቶች እና ሁኔታዎች እያመላከቱን ነዉ።
በሴራዉ ምክንያት እርስ በርስ ከመጠላላት አልፎ ያንድ ሀገር ልጆች በሕዝብ ስም በፓለቲካ እና በሐይሞኖት ስም እየተነሱ ሽበር እና ግድያ በመፈጸም ሰዉን ከነ ሕይወቱ ወደ ገደል ገፍትሮ መግደል እና ህጻናት በትምርት ገበታ ላይ እንዳሉ እሳት ለኩሶ መፍጀት፤ ዕዉራን አረጋዊያን ብልታቸዉ በሰላ ተቆርጦ በሙት/ሬሳ አፍ ላይ ማጉረስ፤ እናቶች በቢላዋ ጡታቸዉን መቁረጥ፤እመጫት ህጻንዋን ታቅፋ ከሞት ለማምለጥ ስትሸሽ በጥይት እንደ ዥግራ እያባረሩ መግደል፤ወዘተ፡ በኢትዮጵያ ምድር የታየበት ዋናዉ የጭካኔዉ መነሾዉ ከሰዉ ልጆች ጭካኔ ጋር የተያያዘ ባሕሪያዊ ምንጭ ቢሆንም አንዳንድ ጭካኔዎች ካለመማር ተጨምሮበት ለጭካኔዉ ተጨማሪ ነዳጅ የሚሰጡ አፍራሽ የሆኑ ቅስቀሳዎች ያላስፈላጊ መተላለቅ ሊያስከትል እንደቻለ ከላይ የጠቀስኩዋቸዉ በምደሪቷ የተፈጸሙ ክስተቶች የተጠቀሰዉ የግራኛዉ ፍልስፍና ምንጮች ሰበብ መሆኑን መረጃዎች ይጠቁማሉ። ለተከሰቱት በጥላቻ የመተላለቅ እና የመጠላላት ምንጮች ሁሌም ገዢ መደቦች እና የሥልጣን ጥመኞች በሚከተሏቸዉ መርሆዎች የሚከሰቱ ናቸዉ።
በሙሶሎኒያዉያን ወያኔዎች እና በ“ግራ አወንዛፊዎቹ”/ክንፎች (ማርክሲሰስቶች) የፍልስፍና መመሪያ ተመርተዉ የአገሪቱን ሕዝቦች በጎሳ ካፋፍለዉ የአንድነት አርማ የሆነዉን የኢትዮጵያ ገበሬ ለማናቆር ወያኔዎች ወደ ሥልጣን እንደመጡ ተግባራዊ ለማድረግ ቅድሚያ የተጣደፉበት አጀንዳ አገሪቷን በብሔሮች (አገሮች) እና በብሔረሰቦች ቀጥሎም በነሱ አጠራር “ሕዝቦች” ሁሉ ተደራጅተዉ አስከ መገንጠል ድረስ የሚለዉን መብታቸዉ አንደሆነ ነበር የሰበኩት።
ለዚህ ሥራ አስፈጻሚ እንዲሆኑ ለሰበካዉ ከተመዘዙት የወያኔ የፍልስፍና ካድሬዎች ዉስጥ ወያኔን በአምበሳደርነት ያገለገለዉ በጸረ-አማራ ፕሮፖጋንዳዉ “እኝኝ” የሚል ግለሰብ ዛሬ በጥሮታ ተገልሎ በመደበኛ አምደኛነት በወያኔዉ ሰሌዳ በዓይጋ-ፎረም ላይ ዘወትር ስለ ብሔር እና ስለ አማራ ወንድሙ ከሆኑት ከተለያዩ ቋንቋ ተናጋሪ ከደቡቡ ህዝብ ጋር የነበረዉ ግኑኝነት የሻከረ እንደነበር አድርጎ የሕሊና ደንቆሮዎችና የጥላቻ ቅኔኛዎች የገጠሙትና ያሰላሰሉትን የመሸታ ቤት “ጸረ-አማራ” ምሳሌና ግጥም ለቃቅሞ በህዝቦች ላይ ጥላቻ እንደነበረ አስመስሎ ለወያኔ ፖለቲካ ዉሃ እያጠጣ የሚያስነብበን አቶ ተስፋየ ሃቢሶ፦በሽግግሩ ወቅት ወሎ ክፍለ ሃገር ድረስ ሄዶ ገበሬዎችን ለመመረዝ ቅስቀሳ ሲያደርግ፤ ገበሬዎቹ የተናገሩትን በገዛ ብዕሩ ያሰፈረዉ ልጥቀስ እና የወሎ ገበሬዎች በሚከተለዉ አንደበታቸዉ ምዕዳናቸዉ (ረዚስታንስ) ለወያኔ ቢያሰሙም እነ ወያኔ እና እነ ኦነጎች ለሕዝብ ከበሬታ የላቸዉምና በወቅቱም ሆነ ዛሬም ዋጋ/ከበሬታ አልሰጡትም።
ልጥቀስ፦ (እኛ በሽግግሩ ወቅት የብሔር ጥያቄዎችን በተመለከተ በየክልላችን ስንዘዋወር ነበርን። የምናስተምረዉን ትምህርት የሚያዳምጠዉ ሕዝብ ትምህርታችን አልጣመዉም ነበርና አንድ አባት ገበሬ ተቃዉሞአቸዉን በሎሆሳስ ሲገልጡ “ይሄ በብሔር በጎሳ መደራጀት የምትሉት ነገር በተለይም ገበሬዉን አላስደሰተዉም። ልጆቻችን/ ይልቁንስ እኛ ታሪክ እንንገራችሁ። የምታስተምሩትን ነገር ከታሪክ ብቻ ሳይሆን ከተፈጥሮ ጋር አገናዘባችሁ ብታዩት ጥሩ ነዉ። የዱባ ተክል አንድ ቦታ ነዉ የሚበቅለዉ። የሚያብበዉ እና የሚያፈራዉ ግን ተንሰራፍቶ ሄዶ ሌላ ቦታ ለይ ነዉ። ያንን ዱባ ወደ ሗላ ወደ በቀለበት ብትመልሱት ይበሰብሳል። ይሞታል። የኢትዮጵያም ሕዝብ ታሪክ ይኸዉ ነዉ። በመቶ ዓመት ታሪክ ዉስጥ የኢትዮጵያ ሕዝብ አማራዉ ፤ትግሬዉ፤ከንባታዉ ፤ጉራጌዉና፤ወላይታዉ በአሁኑ ጊዜ የሚገኘዉ በመላ ሀገሪቱ ተንሰራፍቶ ነዉ። እስቲ የኛ ሕዝብ ያለበትን ተመልከቱ። ያንን በሀገሪቱ የሞላዉን ሕዝብ በቋንቋና በጎሳ ክልል ብቻ ታጥረህ ተቀመጥ የሚል ትምህርት ብታስተምሩ ሕይወታችን (በዚሁ ጉዳይ ላይ ሲናገሩ) የጥፋት ዘመን መሆኑን ብቻ ነዉ የምታስረዱን” አሉ።
ሌላዉ አባት “ብሔረተኝነትና ሐይማኖት በጥንቃቄ ካልተያዘ አደጋ አለዉ። ብሔረተኝነትና አረቄ አንድ ናቸዉ። እና ድሮ አጋሰስ ለመሸጥ ስንፈልግ አጋሰሱን አረቄ እንግተዋለን። ፈረሱ ወዲያዉኑ ጊዜያዊ ጉልበት ያገኝና ጮሌ ሰንጋ ፈረንስ መስሎ አርፍ ይላል። እናም ጥሩ የደረስ ዕቃ ጭነን ወደ ገበያ ወስደን እንሸጠዋለን፡ ያ ፈረስ አረቄዉ ከላዩ ላይ ተንኖ ሲያልቅ ግን ወደ ጌኞነቱ ይመለሳል። ስለዚህ እናነተ አሁን የምታስተምሩን ነገር ከሕዝቡ ጥቅም አንጻር የሚያዋጣ ስላይደለ ይህን መሰሉን ትምህርት ከእኛ ብታርቁልን እንመርጣለን” ብለዋል።
ሲል ሕዘቡ በቋንቋ፤በጎሳ… መደራጀቱ አደገኛነቱ ገና ከጥንቱ ከጥዋቱ ያስጠነቀቃቸዉ ቢሆነም አገሪቷ ሞግዚት ያጣች አገር ነበረችና እንዲገድሉዋት ከጠላቶቿ ከነ ሞሶሎኒ የተሰጣቸዉን መርዝ ያግቷት ጀመር።ያ ሁሉ ሆኖም ወያኔ እና የጎሳ አቀንቃኞች ምኑ ያክል ቢጥሩም ዉጭ ሲጓዙ ማን ብሎ እንደሚጠራቸዉ ካደሬዎቻቸዉ ሳይቀሩ እንዲህ ሲሉ ይመሰክራሉ፦ “በአሁን ጊዜ ወዴትም አገር ብንሄድ “አንተ ኢትዮጵያዊ ነህ?” ይላሉ እንጂ እንተ “አማራ፤አሮሞ አንተ ወላይታ ወይም ትግሬ ብሎም የሚጠራን የለም።…….” (ተስፋየ ሓቢሶ) የአፍሪካ ሰላምና የግጭት ማነጅመንት ጥናት መዕከል ሰኔ 30 ቀን 1993 ዓ.ም በኢትዮጵያ ሕዝቦች የመወራረስ ታሪክ ላይ ዉይይት ተካሂዶ በነበረበት ወቅት ከተገኘዉ ሰነድ።
ለመሆኑ ይሄ ብሔር ብሔረስብ የሚባል ቃል ማርክሲሲቶቹ እና ወያኔዎች እንደሚተረጉሙት ያገራችን የቋንቋ ጠበብት የሚተረጉሙት ልክ እንደነሱ ነዉ? አስፈላጊ ሆኖ አግኝቸዋለሁና አንድ ነገር ሲተረጎም የቃሉ ትርጉም ምን ማለት እንደሆነ ከአገሬዉ ቋንቋ ጋር ካልሄደ የተሳሳተ የዉጭ ትርጉም ተይዞ ለጥፋት ስለሚዉል የቃላቱ አተረጓጎም ትከክለኛነቱ እና ስሕተቱን ለማወቅ ይረዳን ዘንዳ በአገር ወዳድ እና በአንድነት ሃይሎች የተወገዘዉ ጎሰኝነትን ከትዉልድ ትዉልድ አስተላልፎ ለማለፍ ከከጀለዉ ከታወቀዉ ጎሰኛዉ የወያኔዉ ምክትል ያዲስ አበባ ከንቲባ፤እና “የወያኔዉ ያማርኛ ፕሮፖጋንዳ ክፍል” የሚባለዉ የኢሕአዴን/“ብአዴን” ታጋይ የነበረዉ “የአማራዉ ሕዝብ ከየት ወዴት” መጽሐፍ ደራሲ “እንዳርጋቸዉ ጽጌ” በጻፈዉ ጸረ አማራ እና ጸረ-ኢትዮጵያዊነት መጽሐፉ ለመተቸት በሞረሽ ቅጽ 2 ቁጥር 2 (1986) የቋንቋ እና የተለያዩ ዘመናዊ እና ጥንታዊ ትምርቶች ጠቢብ የሆኑት ክቡር ፕሮፌሰር ጌታቸዉ ሃይሌ ቋንቋ እና ብሔርን በሚመለከት አንዳረጋቸዉም ሆነ ወያኔዎች በተሳሳተ መንገድ እንዴት እንደሚተረጉሙት እና ራሳቸዉን አሳስተዉ አዲሱን ትዉልድ እንዴት እንዳሳሳቱት የአመራዉ ሕዝብ ከየት ወዴት” ደራሲ የለበሰዉን አደናጋሪ የዉሸት ልብስ ፕሮፌሰሩ ሲያጋልጡት እንመልከት። (ብሔር የመታወቂያ ባንዴራ) በሚል ንኡስ ርዕስ እንዲህ ይላሉ። ደራሲዉ የተቃዋሚዉን አፍ ለማስያዝ የሞከረዉ ገጽ 7-8 ላይ ባሰፈራቸዉ ከዚህ በታች ባሉት ቃላት ነዉ፦ “በኢትዮጵያ ዉስጥ ከሰባ የሚበልጡ ብሄር ብሄረሰቦች መኖራቸዉ ተቀብለዉ ነገር ግን ብሄረተኝነት ጥያቄ ሲመልሱ በኢትዮጵያ ሚገኘዉ ብሄረተኝነት አንድ ኢትዮጵያዊ ብሄረተኝነት ብቻ ነዉ የሚሉ አልታጡም። እንዲህ የሚሉ ሃይሎች ሊመልሱት የማይችሉት ጥያቄ አለ። ብሄረተኝነቱ ኢትዮጵያዊ ከሆነ ምን ዓይነት ቋንቋ ባህል ታሪክ ወግ፤ወዘተ፡ በአጭሩ ይዘቱ ምን ይሆናል የሚለዉን ነዉ።”
ክቡር ዶክተር ጌታቸዉ ሃይሌ ለዚሁ ሲመልሱ እንዲህ ሲሉ እርቃኑን አስቀሩተዉታል።
{ “በደራሲዉ አስተሳሰብ የብሔር ማወቂያ (ባንዴራዉ) ቋንቋዉ ነዉ።በኢትዮጵያ ዉስጥ ብዙ ቋንቋዎች ስላሉ ብሔረሰቦችም ቁጥራቸዉ በዚያዉ ልክ ሊሆን ነዉ-- ከዚያም ላይበልጥ ከዚያም ላያንስ። በ ኢትዮጵያ ዉስጥ አንድ ቋንቋ ብቻ ቢኖር ኖሮ ቢሔርተኝነታችን ኢትዮጵያዊ ብቻ ይሆን ነበረ ሊል ነዉ። በብሔረተኝነት የሚጫረሱ ሶማሌዎች የሚናገሩት አንድ ቋንቋ እንደሆነ ደራሲዉ ያዉቅ ይመስለኛል። ሰዉ ጎሳቸዉን (ብሔራቸዉ) አንድ ያደርግባቸዋል እንጂ እነሱ ቢጠይቋቸዉ ሱማሌነታቸዉ ቢያምኑም ጎሳችን አንድ ነዉ አይሉም። ተጠራቅማችሁ አንድ ብሔር፤ አንድ ሕዝብ፤አንድ አገር፤አንድ መንግሥት ሁኑ ብላ ያስቸገረቻቸዉ እንደ አቶ አንዳርጋቸዉ የምታስብ እንግሊዝ ናት። ዩጎዝላቢያ ዉስጥ በብሔረተኝነት የሚተላለቁት ሰርቦች፤ክሮዋቶች ቦዝኒያዉያን በቋንቋ አንድ ናቸዉ። ግን አንድ ጎሳ (አንድ ብሔር) ነን አላሉም። የብሔረተኝነት ምንጩ ቋንቋ ብቻ ቢሆን አይሪሾች ግማሾቹ ከእንግላንድ ጋር መሆኑንን ሲመርጡ ሌሎቹ መለይትን አይመርጡም ነበረ። አሜሪካና ካናዳ ሁለት አገር ሁለት መንግሥት ባልሆኑም ነበር።ጌርማኒያንና ነምሳ ሁለት አገር፤ሁለት መንግሥት ባለሆኑም ነበር። የአሜሪካን ዩሁዲዎች ቋንቋቸዉ እነደሌላዉ የአሜሪካ ሕዝብ እንግሊዝኛ ነዉ። የኦሮሞ ጎሳዎችን ጨፍልቆ አንድ ጎሳ (ወይም ብሔር) የሚያደርጋቸዉ ሃይል አስካልመጣ ድረስ ቋንቋቸዉ አንድ ስለሆነ ብቻ አንድ ጎሳ (ወይም ብሔር)ናቸዉ ማለት የሌለዉን አለ ብሎ መናገር ነዉ። ጎንደሬዉንና ጎጃሜን የሚናገረዉ ቋንቋ አንድ ስለሆነ አንድ ጎሳ (ወይም ብሔር) ማድረግ ከነሱ የተለየ ቋንቋ የሚናገረዉን ትግሬዉን በቋንቋዉ ከጎንደሬዉ ይለያል ማለትን ያስከትላል። የእንግዲሁን አናዉቅም አንጂ አስከ ዛሬ እንዲህ አልነበረም።”
አንዳረጋቸዉ ጽጌ (በመጽሓፉ በገጽ 12 ላይ) እና የዛዉ ፍልስፍና ደቀመዛሙረቱም ጭምር እንደሚሉት “በኢትዮጵያ ብሄረተኝነትም ይኖራል። የብሄረተኝነት መፈጠር የራሱ መሠረት ስላለዉ ብቻ እንጂ በጉትጎታና በቅስቀሳ የመጣ አይደለም።” በማለት ጭልጥ ያለ ዉሸቱን/ታቸዉን አዲሱን ትዉልድ መርዙን ሊግቱት ሞክረዋል። ሃቁ ግን እሱ አይደለም።
ፕሮፌሰር ጌታቸዉ ሃይሌ የሚከተለዉ ያስተምሩናል፦
{እዉነታቸዉ ግን በጉትጎታና በቅስቀሳ የመጣብን እዳ ነዉ። የደራሲዉን አስተያየት የሚቀበል በኢትዮጵያ የብሔረተኝነት ታሪክ የማያዉቅ ሰዉ ነዉ።ታሪኩን የሚያዉቅ (እንዲያዉም ራሷን ይቺን ቁንጽል መጽሐፍ በጥሞና የሚያነባት) በኢትዮጵያ ብሔረተኝነት የተፈጠረዉ በሻዕቢያ አምላክነት እነደሆነ አይሰወረዉም።አፈጣጠሩም ብዙዎች ደጋግመዉ እንደጻፉትና እንደተናገሩት “ኤርትራን ከኢትዮጵያ ለመገንጠል የሚቻለዉ የኢትዮጵያን ሕዝብ በብሔረተኝነት በማተራመስ ነዉ” በሚል ፍልስፍና ነዉ። ሻዕቢያ ሐሳቡን ያገኘዉ ከቅን ገዢዉዎች ነዉ። ቅን ገዢዎች ኢትዮጵያን ለመግዘት አለዚያም ለማዳከም ሚቻለዉ በሃገሩ ላይ ብሔረተኝነትን እሳት በማቀጣጠል ብቻ ነዉ። ብለዉ በጊዜዉም ተጠቅመዉበታል። ዛሬ ኤርትራ ራሷን የምትችል ሀገር ብትሆንልን በሃገራችን የጎሰኝነት ጉዳይ ገብ ይልልን ነበር።ኤርትራ ረሷን አስካልቻለች (ግን የምትችል አይመስልም፡ ሐረግ ሬሳይቱ ያለዋርካዉ ድጋፍ ራሷን ችላ አልቆመችም፡) ወይም የኢትዮጵያ ሕዝብ በዲሞክራሲ አስካልተዳደረ ድረስ ሻዕቢያና ወያኔ ቅድሚያ ሚሰጡት ሀገሪቱን ለማዳበር ሳይሆን ጎሰኝነትን ለማፋፋም ነዉ። ከሁሉ አስቀድመን መገንዘብ ያለብን ብሔረተኝነት ከዉጭ የመጣ ሓሳብ እንጂ እኛ ኢትዮጵያዉያን ከጥንት ጀምሮ የምንወግነዉ ለሀገራችንና ለሃይማኖታችን ነዉ። ብሔረተኝነት አለ ቢባል ሃይማኖታዊ ግፋ ቢል ጎጣዊ ነዉ። ካዲሰቱ ኢትዮጵያ ይጠበቅ የነበረዉ ሃይማኖትን የግል ብቻ አድርገን ዉገናችንን በሀገር ላይ ብቻ ነበር። ….አሁን ግን “ጎሳ የጋራ፤ሃይማኖት የሚያጣላ፤ሀገር የግል” የሚል ፈሊጥ ሊያመጡብን ነዉ። }
እንግዲህ ከላይ እንደተመለከትነዉ ባጭሩ በማያሻማ ተብራርቷል። በመጨረሻ ምሁሩ ሲያብራሩ ለመሆኑ ይህ ዛሬ ብሔር እየተባለ የሚጠቀስ የዘመኑ ቃል ባገሪቷ ቋንቋ አጠቃቀም ብሔር ስንል ትርጉሙ ምን ማለት ነዉ?
አሁንም ፕሮፌሰሩ ያስረዳሉ፦
“ብሔር/ብሔረስብ የሚባለዉ ቃል በዛሬ ትረጉሙ በቋንቋችን አልነበረም። የተፈጠረዉ አሁን በኛ ዘመን ነዉ። የፈጠሩትም የ ኢትዮጵያ አንድነት ጠላቶች ናቸዉ። እዚሁ ሀገራችን ዉስጥ የበቀለ ቢሆን ኖሮ ሀገራችን ዉስጥ እንደበቀለዉ እንደማንናቸዉም ነገር ሁሉ ስም ይዞ እናገኘዉ ነበር፦…” ይሉና አስቀድመን የጠቀስነዉ “የአማራዉ ሕዝብ ከየት ወዴት” መጽሐፍ ደራሲ “አንዳርጋቸዉ ጽጌ” እና የዛሬዎቹ ማርክሲስቶች ስለብሔር ያላቸዉ የተሳሳተ ትርጉም ፕሮፌሰሩ ሲገልጹ፦ ደራሲዉ
ብሄር ሲባል ከቀጥታ ትርጉሙም ከስሜቱም ተነስተን በምዕራፍ 1 ከቀረበዉ ሀተታ ጋር አገናዝበን ስናየዉ ኦሮሞ ትግሬ አፋር ቢል ትክክልም ተገቢም ይመስላል” ይላል። ተሳስቷል፤ትክክልም ተገቢም አይመስልም፤አይደለምም። “ብሔር” የግዕዝ ቃል ሲሆን ትርጉሙ “ሀገር” ማለት ነዉ። ቃሉ ምድርን እንጂ ሕዝብን አያመለክትም። እንዲህ ከሆነ አንድ ኢትዮጵያዊ ብሔሩን ሲጠይቁት፤ አትዮጵያ፤ ቡልጋ፤ጎንደር ኤሉባቡር፤ መንደፈራ ቢል ምኑ ነዉ “ግር የሚያሰኘዉ”? (ገጽ 14 )? ወደድንም ጠላንም ለዚህ ስንጠቀምባቸዉ የነበሩ ቃላት “ዘር”፤”ነገድ”፤”ጎሳ”፤”ቤት”፤”ወረ” (ለምሳሌ ወረ ቃሉ ወረ ኢሉ ወዘተ)።” ናቸዉ)።
የቋንቋ፤የሐይማኖት፤ እና የተለያዩ ዘርፈ ብዙ ዘማናዊ ትምሕርት ሊቁ ፕሮፌሰር ጌታቸዉ ሃይሌ ያብራሩልንን ባለፉት ወደ አርባ አመታት አንዱ ጎሳ በሌላ ጎሳ ተጠቅቷል እየተባለ በእነ ወያኔዎች እና በተቀሩት ግራኛ ሃይሎች ለዘመናት የተናፈሰዉ/የተሰበከዉ አናካሽ ጽሁፋቸዉ/ቅስቀሳቸዉ አፍራሽ እና ፈሩን የሳተ፤ካገሪቱ ሁኔታ ያልሄደ የተሳሳተ የፖለቲካ መርሆ መሆኑን እላይ በሙሁራን መዝገብ አስደግፌ ለማመብራራት እንደገለጽኩት ደንቃራነቱ የት እንደሆነ ግልጽ እንደሚሆንላችሁ እርግጠኛ ነኝ።ለማጠቃለል፦”ብሔር” ግራኛዎቹ አሁን በሚተረጉሙት መልክ ያገራችን ግዕዝ እንደማያዉቀዉ” ግልጽ ነዉ። “ርዕሰ ብሔር” ሲል የሀገሪቱ/የምደሪቱ መሪ ማለት እንጂ ሌላ ትርጉም እንደሌለዉ እናዉቃለንና የሀገራችን ቋንቋዎች ለፖለቲካቸዉ መጠቀሚያ በማድረግ እያምታቱ ሕዝብን የሚያጋጩ ሁሉ ነቅተን እንጠብቅ። /-/ -*/ ኢትዮጵያ አምላክ ይጠብቅ። www.Ethiopiansemay.blogspot.com

No comments: