Sunday, June 23, 2019

ብጄኔራል አሳምነው ጽጌ! የዘመናችን ታናሹ በላይ ዘለቀ ጌታቸው ረዳ (ኢትዮ ሰማይ Ethio semay)


ብጄኔራል አምነው ጽጌ! የዘመናችን ታናሹ በላይ ዘለቀ
ጌታቸው ረዳ (ኢትዮ ሰማይ Ethio semay)
ቅዳሜ ከከተማየ ወጣ ብየ ነበር። አንድ ወዳጄ ደውሎ አዲስ ዜና አለ አለኝ። ስንጓዝበት የነበረው ድልድይ ረዥም እና  ስልክ ለማስተላለፍ ስለማያመች “በደምብ ማድመጥ ስላልቻልኩ ዘጋሁት”። ትኩስ የተባለውን ዜና ለማድመጥ ቸኩዬ ሲመሻሽ እቤት ስገባ ላንድ የቅርብ ወዳጄ ስልክ ደውየ፤ ምን ተፈጠረ? አልኩት። የሆነውን ሁሉ ነገረኝ። በስፋት ለማወቅ ድረገጾች ላይ ስፈትሽ ወዳጄ ከነገረኝ ጋር ተመሳሳይ ነው። ዜናው ባሕርዳር ከተማ በብርጋዴር ጀኔራል አሳምነው ጽጌ መሪነት ‘መፈንቅለ መንግሥት’ እንደተካሄደ እና የተወሰኑ የ “ብኣዴን” (የቅርብ ስያሜው ‘ኣዴፓ’) ሰዎች ጉዳት እንደደረሰባቸው አደመጥኩ።

መፈንቅለ መንግሥት የሚለው ስያሜ ምን ማለት እንደሆነ ባይገባኝም፤ የተከሰተው የመገዳደል ትዕይንት ዞሮ ዞሮ በፋሺሰት ግልገሎችና “አንጀታቸው በበገነ አገራውያን” መካከል የተከሰተ የዓላማ አለመጣጣም ውጤት ነው።  ግብግቡ ቅጽበታዊ ሳይሆን “በአገራውያን እና በፋሺሰት ግልገሎች መሃል” ለብዙ ጊዜ ሲብላላ ሲቋሰል የቆየ ውስጣዊ  ፍጥጫ ነው። አሳምነው ጽጌ ግጭቱን እንደመራው ይወራል። መያዙንም ተነግሯል። እውነትነት ካለው ብ/ጀኔራል አሳምነው ጽጌ ፋሺሰቶችን ለሁለተኛ ጊዜ አልገዛም ብሎ ማርበድበዱ ስሙ በልዩ ጀግኖች ማሕደር ውስጥ ያስመዘገበዋል።

ተንታኞች የተለያዩ እያታዎች ሊተነትኑት ይችላሉ። ሆኖም የአሳምነው “አንጀት እየበገነ መምጣቱ” በቅርብ ሳምንታትና ወራት ከተናገራቸው ንግግሮቹ ስንገምግመው፤ ጀኔራል አሳምነው ‘አናርኪሰቱን ስርዓት’ አገሪቱን ከድጡ ወደማጡ እየከተታት መሆኑን ስለገባው (በተለይም አማራው የተጋረጠበት ከበባ) ትዕግሰቱን ለመጨረሻ ጊዜ የተፈታተነው ስለሆነ ግለልጽ ብስጭት እንደገባ ያሳያል።

ከወር በፊት የክልሉ የጸጥታ ሓላፊ ሳያውቀው ከማንኛውም የአማራ ክልል ዜጎች ታፍነው ወደ ፌደራል እንደማይወሰዱ “ጥብቅ ማስጠንቀቂያ” ማሳለፉን ታስታውሳላችሁ። ጀኔራሉ ወታደር እንደመሆኑ መጠን ‘ሽኩቻው እየከረረ አንጀቱም እየበገነ መምጣቱ” እና ግልገል ፋሺሰቶቹ “እሱን በሚያምኑ ጓዶቹ እና በራሱ ላይም እየሸረቡበት” መኖሩን የሚያሳይ ምልክት እንደነበር ግልጽ ነው። እነ መኮንን ደመቀ እና ንጉሡ “አሳፋሪ እና አማራዊ ያልሆነ ባሕሪ” እያሉ “ቢለቀልቁም አሳፋሪዎቹ ግን እነሱ መሆናቸው መታወቅ አለበት። የአማራ ብሕል እና አማራነታቸውን አውልቀው ለ28 አመት አማራውን ምን ሲያደርጉት እንደነበር ዘንግተውት አሁን ስለ አማራ ባሕሪ እተመጻደቁ አሳምነውን ለማውገዝ ምላሳቸው ማሾል እንደ እባብ በጓዳቸው ማሾል ጀምረዋል።

ስለዚህም ጀኔራሉ በአዲስ አበባው የአናርኮ ፋሺሰት የኦሕዴዱ ቡድንም ሆነ ድሮ “አማራዊ ቆዳ፤የትግራዋይ ጭምብል”  ከአንድ አመት ወዲህ ደግሞ “አማራዊ ቆዳ፤ኦሮሞዊ ጭምብል” በለበሱ ወለዋይ የፋሺሰቶቹ ‘ግልገሎች’ ላይ የመጨረሻ አቋም መውሰዱ “በላይ ዘለቀ” በባንዳዎች ላይ የወሰደው አንጸባራቂ ርችት የሚያስታውስነን ክስተት ነው። ስለሆነም አሳምነው ለሁለተኛ ጊዜ በስርዓቱ ላይ ማመጹ አሳምነው የዘመናችን “ታናሹ በላይ ዘለቀ” ሆኗል።

የሚገርመኝ ደግሞ ‘ምሁራን ተብየዎች እና አሳፋሪ ተቃዋሚ ተብየው’ “ዛሬም” በየክልሉ እና በየከተማ ገጠሩ ሕዝባችንን ቁም ስቅሉን እያሳዩት ያሉት “ፋሺሰቶች” መሆናቸውን በመካድ ከታች  ያሉት ሹማምነቶች እንጂ “አብይ ብቻውን ምን ያድርግ ነው የምትሉት? ምንስ ያድረግ ሰው ነው መልኣካዊ ክንፍ የለውም” እያሉ የደርግ ጊዜ አለቅላቂዎች የሚመስሉ ሻለቃ ዳዊት በልዩ ደብዳቤአቸው ለመንግሥቱ በጻፉት ላይ “እረስዎ ብቻ ለአገርዎ ሲቆረቆሩ ከሥርዎ ግን አላሰራም የሚሉ በአድሃሪያን ሹማንቶች መከበብዎን ስመለከት አዝንለዎታለሁ..” ያሉትን ዓይነት ዛሬም በተቃዋሚ እና በምሁራን ተብየዎች አሳፋሪ ታሪክ እየተደገመ እያደመጥናቸው ነው። ስለዚህ ፋሺሰቶችን እና ግልገሎቻቸውን ለማስወገድ ሁሉንም መንገድ መደርገ አለበት!

 ይህንን ክስተት አስታክከው ‘የአብይ ነጭ ባንዲራ አውለብላቢ ሁላ’ “የአማራን ሰቆቃ” ሳይሰማው ለዘመናት አፉን ዘግቶ ከርሞ ‘ዛሬ ለፋሺት መንግሥት ያልተምበረከከው ጀግናው አሳምነው ጽጌን በመኮነን” ባንተ ላይ ያደረገው ጥቃት ነውና እናወግዘዋለን ብሎ “ለአማራ ሕዝብ” መልዕክት እያሉ ቢያስተላልፉም፡ የጸረ ፋሺሰት ታጋዮች ክንድ ማስቆም አያቻላቸውም! ፋሺሰቶቹና አለቅላቂ ግልገሎቻቸው አሁንም በአማራ ሕዝብ ላይ የተደረገ ጥቃት ነው የሚሉት “ለ28 አመት እስካሁን ድረስ የአማራ ሕዝብ ሲጠቃ የት ነበሩ?

የተለያዩ ዜናዎች እንደሚጠቁሙት ከሆነ፤ ጭቅጭቁ የተፈጠረው አጣየ እና በመሳሰሉ አካባቢዎች ‘ኦነጋዊ የኦሕዴድ ፋሺቶች’ ያደረሱት ጥፋት ተጠያቂዎችን ለይተው በማስቀመጣቸው በአሳምነው እና በአምባቸው ላይ የተሸረበ ሴራ ነው የሚሉ ትንተናዎች እየወጡ ነው። ከነዚህም ጥቂቶቹ እንዲህ ይላሉ፤-

“ምድረገኝ ሲባል የነበረው የጋላ (ኦሮሞ) ዘመን ወራሪዎች ‘ከምሴ’፤ እንዲሁም አጣዬና ማጀቴ’ በተባሉት አማራ ‘ክልል’ ስፍራዎች የደረሰው ጭፍጨፋ በ’ኦነጋዊ ኦሆዴዶች’ እንደሆነ እና በመንግሥት ውስጥ የተሰገሰጉ ኦሕዴዶች እንደሆኑ አምባቸው መኮንን፤ አሳምነው ጽጌ፤ ሰዓረ መኮንን፤ምግባሩ ከበደ፤አዘዝ ዋሴ ተፈራ ማሞ እና የድሮ የግንቦት 7 እና የኢሳት ባልደረባ የነበረው ዛሬ አገር ውስጥ የገባው ‘መቶአለቃ አበረ አዳሙ’ አጣሪ ሆነው ባገኙት አጠቃላይ ምርመራ ያለተደሰቱ ኦሕዴዶች እና ኦነጋዊ የውስጥ አርበኛ ባለሥልጣኖች የሸረቡት ሴራ ነው,፣’ ሲሉ አሰተያየታቸውን ይገልጻሉ። ለዚህም ያናርኮ ፋሺሱ አብይ ቅጽበታዊ ወታደራዊ ልብስ ለብሶ (ውቃቢው ርቆ፤ማዕረጉ በመቀስ ተበጥሶበት ለፍርድ የቀረበ ሞኮንን ቢመስልም) በቲ/ቪ መግለጫ መስጠቱና የእርሱ አለቅላቂ (አፈቀላጤ) የሆነው የጃዋር አድናቂ “ንጉሡ” የተባለው “ብኣዴናዊው አባል” ክስተቱን በሚመለከት በቅጽበት ወደ ሕዝብ መግለጫ ማድረጋቸው ነገሩ ከጀርባ የተሸረበ ነው የሚሉ ጥርጣሬዎችም አሉ። ያውም የተደጋገመ የአብይ አሕመድ የውሸት ባሕሪ ግምት ውስጥ ሲገባ።

ያም ሆነ ይህ አሳምነው ጽጌ ባለፉት ጥቂት ወራቶች በሥርዓቱ ላይ ግልጽ ብስጭት ይንጸባረቅበት እንደነበር ግልጽ ነው። 

በቅርቡ ከንግግሮቹ ውስጥ..;

 የአማራ ሕዝብ ከዚህም ከዚያም የመከበብ አደጋ ተጋርጦበታል!በተለይ ከ500 ዐመት በፊት አጋጥሞት የነበረ አሁን ካጋጠመው ጋር የሚመሳሰል ችግር አጋጥሞት ነበር። ያንን ፈተና አባቶቻችን ተጋፍጠው አልፈውታል። አሁን የገጠመንን  ፈተና በተለይም በዘራችን የመጠቃትና ራሳችንን የመከላከል ሓላፊነት ግን የዚህ ትውልድ ሓላፊነት ስለሆነ ራሳችንን መከላከል ይገባናል!” (ብ/ጄ አሳምነው ጽጌ ባሕር ዳር ፖሊስ ኮማንዶዎች ሰልጠንው ሲመረቁ ያደረገው ንግግር)።

ከዚህ እና ከመሳሰሉ ክስተቶች ስንመለከት አሳምነው ከግልገል ፋሺሰቶች ጋር እና ከሥርዓቱ መሪዎች ጋር ያለመጣጣም እንደነበረው ጥርጥር የለኝም።

እኔ በግሌ ዜናውን ስሰማ “ከነጭ ባንዴራ አውለብላቢ ‘ተቃዋሚ ተብየዎቹ” በየይቱብ ላይ ሕዝቡ ከመንግሥቱ ጋር እንዲቆም የተማጽኖት እና ጀኔራሉን የማውገዝ መልዕክት ያስተላለፉትን ሳደምጥ ይበልጥ ነገሩ አበሳጨኝ። የነኚህ የነጭ ባንዴራ አውለብላቢ ቡድኖች “ውግዘት” ሳደምጥ፦

“ጨቋኙን አውርዱ ማውረዱ ይበጃል
ይዋል ይደር ማለት ጠላት ይደራጃል!

የሚለው የየካቲቱ 66 ገጣሚ የግጥም ትዝታዎች ጭንቅላቴ ላይ አቃጨለ። የነጭ ባንዴራ አውለብቢዎቹ ጉደኞች ስርዓቱን እየመራ ያለው “ዛሬም የፋሺሰቶቹ ቡድን” መሆኑን ‘አሌ’ እያሉ ‘የፋሺሰት ግልገሎች በተነኩ ቁጥር’ “ውግዘትና ሙሾ ማውረድ” ለምደውታል። ያውም አንዳንዶቹ እማ “የጦር አበጋዞች” ይመስል እውጭ አገር ሆነው ጎጃምወሎ/ሸዋ እና በመላው አገሪቱ ያለው አማራ ልዩ መልዕክት አስተላልፈዋል። አማራው በየጥሻው በፋሺሰት ተገንጣይ ኦሮሞዎች እና በፋሺሰት ተገንጣይ ትግሬዎች እንዲሁም በአብይ አሕመድ ድርጅት “በኦሕዴድ” ሲፈናቀል እና ግፍ ሲፈጸምበት “የከፋ እንዳይመጣባችሁ እየተፈናቀላችሁ እየተገደላችሁም ቢሆን ዝም በሉ” እያሉ የሕዝቡን እሮሮ ለማዳከም የተቻላቸውን ያህል ፕሮፓጋንዳ በመስራት ላይ ናቸው። ሰለዚህም አገራውያን ትግላቸውን በማንኛውም መንገድ መቀጠል አለባቸው።የጊዜ ጉዳይ እንጂ ፋሺሰቶች በጥቂት የቁርጥ ቀን አገራውያን ቆራጥ ትግል ይወገዳሉ!

የቁርጥ ቀን ልጅ የብ/ጄ አሳምነው ጽጌ ቁጭትና አገራዊነትን የሚያጠለሹ ሁሉ የነጭ ባንዴረ አውለብላቢ ቡድኖች ናቸው! ስለሆነም ታቀቡ እንላለን።የጸረ ፋሺሰት ታጋዮች ትግል በግልገል ፋሺሰት አቀንቃኞች አይታጠፍም!

አመሰግናለሁ:
ጌታቸው ረዳ (ኢትዮ ሰማይ ድረገጽ አዘጋጅ Ethio Semay) getachre@aol.com




No comments: