Tuesday, August 1, 2017

ወቅታዊ ጉዳዮች በወፍ በረር ቅኝት -ምሕረት ዘገዬ- Ethiopian Semay

ወቅታዊ ጉዳዮች በወፍ በረር ቅኝት     
ምሕረት ዘገዬ
 
Desta Hotel Mekele

Mekele University graduation
 
Mekele City at night

              
በዚህ ዘመን ተማሪዎች “አጤሬራ” የሚሉት ፈሊጥ አላቸው፡፡ አጤሬራ ማለት አንድ ተፈታኝ ተማሪ ወደ ፈተና ክፍል ወይም አዳራሽ ሲገባ ደብቆ ይዞት የሚገባው በአጭር በአጭሩ የተጻፈ ማስታወሻ ማለት ነው፡፡ ዘመኑ የኩረጃና የማጭበርበር ነው፡፡ ኮራጅና ከማስታወሻ ገልባጭ ተማሪ “እየተመረቀ” አገር ምድሩን እየሞላው ነው፡፡ ስሙን አስተካክሎ የማይጽፍ የከፍተኛ ትምህርት ተቋም ተመራቂ ማግኘት የማያስገርመው ኢትዮጵያ ውስጥ ብቻ ነው፡፡ ለማንኛውም ከተማሪዎቹ ለየት የሚለውና በሀገራችን ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ይበልጡን የሚያተኩረው የኔ አጤሬራ ከዚህ በታች ቀርቧል፡፡

ሰሞኑን በአንዳንድ የአማራው አካባቢዎች ተዘዋውሬ ነበር፡፡ ስለታዘብኳቸው ነገሮች ፎቶግራፎች አሉኝ፡፡ ግን በጣም የታወቀን ነገር ለማሳወቅ መድከም እንደማያስፈልግ በመረዳት አሁን አልለጥፋቸውም፡፡ እንዳስፈላጊነቱ ወደፊት አቀርባቸዋለሁ፡፡
የአማራው ክልል፡- 

  መንገድ የለውም፡፡ ትምህርት ቤት የለውም፡፡ ፋብሪካና ኢንዱስትሪዎች የሉትም፡፡ አብዛኛው ሕዝብ እልም ባለ ድህነትና ኋላ ቋርነት ውስጥ ይገኛል፤ ልብሱ በላዩ ላይ አልቆ፣ መጫሚያ ሳይኖረው ባዶ እግሩንና እርቃኑን ተጎሳቁሎ ስታዩት አንጀታችሁ በሀዘን ይኮማተራል፡፡ የሕዝቡ ኑሮ ከ26 ዓመታት በፊት ከነበረውም እጅግ በወረደ ሁኔታ ከፍተኛ ስቃይ ውስጥ ነው፡፡ ትምህርት ቤትና የጤና ተቋማት በአንዳንድ ቦታዎች አሉ ቢባልም ኋላ ቀርና የሰውና የቁሣቁስ ድህነት የሚያጠቃቸው ናቸው - እንዲያው ለስሙ ብቻ፡፡ ጥሩ ሞት እንኳን እንዳይሞት ይህም ዕድል ሆነና በቶሎ ምድርን እንዳይሰናበት ተከልክሎ ቀስ እያለና እየተሰቃዬ እንዲሞት በወያኔ የተፈረደበት ሕዝብ መሆኑን በዐይኔ በብረቱ ታዝቤያለሁ፡፡ ምሥክርነቴ የማተቤን ነውና አልዋሻችሁም - ዋሽቼስ ምን ላገኝ? ደስ የሚለው ግን በዚህች ምድር ለዘላለም የሚኖር ምንም ዓይነት ሕይወት ያለው ፍጡር አለመኖሩ ነው፡፡ ገዳይም ሟችም የመጨረሻ ፍርዳቸውን የሚያገኙበት ሌላ ፍትሃዊ ዓለም መኖሩን ስለማምን በበኩሌ በዚያ ብቻ እጽናናለሁ፡፡ “ሁሉም ነገር የከንቱ ከንቱ ነው፤ ንፋሰንም እንደመከተል…” ብሏል ነቢዩ ሶሎሞን ቀደም ሲል፡፡ ስለዚህም አንድ ሰው ቀን ሰጠኝ ብሎ የክፋቱን ጥግ ሲያሳይህ የዚያን ግልባጭ ከወዲሁ በመመልከት ልታዝንለት እንጂ ብዙም ልትፈርድበት አይገባም፡፡ ቀላል ሰው እንደብረት ድስት ነው፡፡ ብረት ድስት ለቅዝቃዜም ለሙቀትም እጅግ ቅርብ ነው፡፡ ቀትረ ቀላል ዜጋም እንዲሁ ነው፡፡ አስተሳሰቡ ከአፍ እስካፍንጫው እንኳን የማይደርስ በመሆኑ ነገን ቀርቶ የዛሬይቱን ምሽትም አያይም፡፡ በብልጭልጭቷ ዓለም ታውሯልና፡፡

አንድ ት/ቤት ጎበኘሁ፡፡ 

አጥር የለውም፡፡ መማሪያ ክፍሎቹ በርም ሆነ መስኮት የላቸውም፡፡ ማለቴ በሮቹም መስኮቶቹም ወላልቀው ጠፍተው ክፍሎቹ የዓሣማ ጋጣ ይመስል በጭቃና በወረቀት ተሞልተው በነዚያ ውስጥ ነው ተማሪዎች “የሚማሩት”፡፡ የመምህራን ማረፊያና ቢሮዎች እንደነገሩ በአንድ ላይ ተጫፍረው አሉ ለማለት አሉ እንጂ በአግባቡ የሉም፡፡ ከተለጣጠፉ የማስታወቂያ ወረቀቶች እንደተረዳሁት መምህራኑ ራሳቸው እንግሊዝኛውን ይቅርና አማርኛውንም እያወላገዱት ነው - እያልኩ ያለሁት አማርኛ ቋንቋ በአማራው አካባቢም ፈተና ላይ ወድቃለች ነው፡፡ ወያኔ ትግሬ አማራውን ለመበቀልና የአማራን ዘር ለማጥፋት ምን ያህል ርቀት እንደተጓዘ ለመረዳት ምቹ ቦታ ተቀምጦ በተባራሪ ወሬና አሉቧልታ ራስን ከመደለልና በወያኔ ፕሮፓጋንዳ ከመወናበድ ይልቅ የአማራ አካባቢዎችን ተዟዙሮ በመጎብኘት እውነቱን ማወቅ ተገቢ ነው፡፡ አማራ እያለቀለት ነው! ቅስቀሳ እያካሄድኩ አይደለም፡፡ እውነቱን እየተናገርኩ እንጂ፡፡ እውነትን መናገር ደግሞ ከዘረኝነትም በሉት ከጎጠኝነት ይለያል፡፡ እውነትን መደበቅ ወይም ለመናገር አለመፈለግ ነው ይልቁንስ ዘረኝነት፡፡ ዘረኝነት ከእንስሳም የሚያሳንስ እጅግ አደገኛና መርዘኛ ሥነ ልቦናዊ በሽታ መሆኑን አውቃለሁ፡፡ አማራን እናድን ብሎ መጮህ ግን ከዘረኝነትና ከጎጠኝነት የሚያስመድብ ሳይሆን ፍትህን ከመናፈቅና ለሰው ልጆች ደኅንነት ከማሰብ የሚመነጭ ነው፡፡

በብዙ የአማራ አካባቢ መብራት የለም - የሌለው ደግሞ ለሰዓታት ወይም ለቀናት ብቻ ሣይሆን ከናካቴው ነው - ለ15 ቀናት አንድ ከተማ ውስጥ ተቀምጬ ከ30 ይሁን 40 ደቂቃ በስተቀር ሁልጊዜ ጨለማ ነበር፡፡ ለምን እንደሆነ አልገባኝም - ሲፈልጉ ለደቂቃዎች ብልጭ ያደርጉትና በዕንቁልልጭ የአማሮችን አንጀት ያበግኑታል - በተለመደው እውነተኛ አገላለጽ አማራ በጨለማ ውስጥ ቆሞ ጌቶቹን ትግሬዎች መብራት ይዞ ራት እያበላ ነው፡፡ ሕዝቡ ለመሠረታዊ ፍላጎቶቹ የሚጠቀመው የቻለ ትናንሽ ጄኔሬተሮችን በመግዛት ያልቻለ እንደጥንቱ ክትክታን በመቀጥቀጥ ችቦ እየሠራ ነው - ጄኔሬተር ሻጮቹም እነማን እንደሆኑ ግልጽ ነው - በአንድ ጥይት ሁለት ወፍ፡፡ ቡና ቤቶችና የግል ሐኪም ቤቶች የሚበላሹ ነገሮቻቸውን በፍሪጅ ለማስቀመጥ ጄኔሬተር መግዛት ይኖርባቸዋል - ለተወሰነ ሰዓት እንኳን ለማቀዝቀዝ ያህል፡፡ ሞባይሌን ቻርጅ ለማድረግ ለአንድ ጊዜ ቻርጅ አምስት ብር ከፍዬ ነው ቴክኖሎጂያዊ ግንኙነቴን የቀጠልኩት፡፡ አማራ አካባቢ መኖር አሣር ነው፡፡ በሺዎች ዓመታት ወደኋሊት መጓዝ ማለት ነው፡፡ ትግሬዎች በአማራ ነፍሰ ሥጋ እየተጫወቱ ነው፡፡ ድመት በቁጥጥሯ ሥር ያስገባቻትን ዐይጥ ከመመገቧ በፊት ወደላይ እየወረወረች በማፍረጥ ብዙ ከተጫወተችባት በኋላ ትበላታለች፡፡ አማራም እንደታወረች ዐይጥ ሆኖ በወያኔዎች መጫወቻ ሆኗል፡፡ ይህን ጽሑፍ የምታነብ አማራ ለእውናዊም ይሁን ምናባዊ በቀል እንዳትነሳሳ፡፡ በቀልን ለተበቃዩ መለኮታዊ አካል ብቻ ካንጀትህ ሆነህ ስጠውና አንተ ግን ወደ ኅሊናህ ተመለስ ይልቁንስ፤ ተመልሰህም ከሰማያዊ አባትህ ጋር አሁኑኑ ታረቅ - መጣላትህ ነው ለዚህ ዓይነቱ ጉግማንጉግ መንግሥት የዳረገህ - ከቃልቻና ባለዛር ጥንቆላ፣ ከደብተራ መተት፣ ከአንደርብ፣ ከአጋንንት ጉተታ፣ ከስኒ ምልከታ፣ ከኮከብ ቆጠራ፣ ከአውሊያና ከቆሌ ባዲገዝ ቦረንትቻ፣ ከእጀሰብ ሰይጣናዊ የመርዝ ቅመማ፣ ከተንኮል፣ ከምቀኝነት፣ ከድንቁርናና ከባዕድ አምልኮ ወዘተ. ታቅበህ ወደ ፈጣሪህ ብቻ ጩኽ፡፡ ያኔ ጀርባውን ያዞረብህ አምላክህ ይታረቅሃል፤ እነዚህን እሾሆችም ነቃቅሎ ይጥልልሃል፡፡ እነዚህን መሰል ትኋንና መዥገር ዳግመኛ እንዳያመጣብህም በሃይማኖትህ የጸናህ ሁን፡፡ እምነትህን መቀያየሩ፣ ሃይማኖትህን እንደሸሚዝ መለዋወጡ ፋይዳ እንደሌለው እመን፡፡ እዚህ ቤት ያለው እሳት እዚያም ቤት አለና እምነትህ በፈጣሪ እንጂ በሰዎች አይሁን፡፡ ሰው ምን ጊዜም ሰው ነው፡፡ የሰው ትልቅ ደግሞ እንደሌለ ከተሞክሮህ ተማር፡፡ በንግግርና በአለባበስ አትማረክ፡፡ ሦስተኛውን ዐይንህን ክፈት፡፡ የሚያብለጨልጭ ሁሉ ወርቅ አለመሆኑንም ተገንዘብ፡፡ ማንም በቀላሉ እንደከብት እየነዳ ወደ መታረጃ ቄራ አይውሰድህ፡፡ መጻሕፍትን አንብብ፡፡ ታላላቆችን ጠይቅ፡፡ መረጃዎችን አትናቅ፡፡ ከስሜታዊነት ውጣና የምክንያት ሰው ሁን፡፡ መረረም ጣፈጠም ምክንያታዊነትን አጥብቀህ ያዝ፡፡…

በነገራችን ላይ ሁሉም ሊሆን የግድ ነው፡፡ የሚሆነው ሁሉ ሆኖ ሲያልቅ ለሚሆነው ተዘጋጅ እንጂ ሊሆን ባለው ነገር ጊዜህን በከንቱ አታባክን፡፡ ለመጨረሻው አርማጌዴዎን ግን ስንዱ ሁን፡፡ ያም ቀን ቀርቧል፡፡ ዛሬ ማታ ወይ ነገ ጧት፡፡ ካልሆነም ሰሞኑን ጠብቅ፡፡ ቃሉ እንጂ ሰማይና ምድርም ቢሆኑ ያልፋሉ፡፡

በአማራው አካባቢ እንኳንስ ለትልቅ ፋብሪካ የሚሆን ለጥቃቅን የጎጆ ኢንዱስትሪ የሚሆን የኤሌክትሪክ ኃይል የለም፡፡ በዐዋጅ የታገደ ነው የሚመስለው፤  በገሃድ አይታወጅ እንጂ በርግጥም ዕግድ ነው፡፡ አማሮች በወያኔ ከተደገሰላቸውና ላለፉት 42 ዓመታት ሲጎነጩት ከቆየው አስከፊና ዘግናኝ የዕልቂት ዐዋጅ አኳያ ሲታይ በአማራ አካባቢ የልማት እንቅስቃሴን ማሰብ ራሱ ከህልም ያለፈ ቅዠትና የቅንጦት ያህል ሊቆጠር የሚገባው ዘበናይነት ነው፡፡ አማራን እወክላለሁ የሚለው በትግሬዎችና በክልሶች የሚመራው ብኣዴን የሚባለው ወፍ ዘራሽ መናጆ ደግሞ ምን እየሠራ እንደሆነና ምን ዓይነት አፍዝ አደንግዝ እንደተዞረበት ማወቅ አልቻልኩም፡፡ አጠገቡ የምትገኝ ትግራይ በልማትና በቴክሎጂ ስትንበሸበሽ አማራው ግን በዳፍንት ውስጥ ሲንጠራወዝ ብኣዴን ተብዬው ይህን የአሜሪካንና የቱምቡክቱን መሰል ልዩነት ሳያይ ቀርቶ አይደለም፡፡ ከአማራው ወደ ትግራይ ክልል ስትገቡ ከአቸፈር ጎጃም ወደ አውሮፓ የገባችሁ ያህል ይሰማችኋል፡፡ ትግራይ እያንዳንዱ ገጠር ውኃና መብራት ገብቶለታል፡፡ በሣምሬን በኩል ነው ወደ መቀሌ ያለፍኩትና ሁሉን ታዝቤያለሁ - ትግራይ ውስጥ ሰው ታጣለህ እንጂ ሥልጣኔና ስይጣኔ በሽ በሽ ናቸው፡፡ በልዩነታችን ሳቢያ አንድ ሀገር ውስጥ መኖራችንን ትረሱታላችሁ፡፡ ተለያይተናል! የልዩነታችንን ክፍተት ለመሙላት የመቶ ዓመት ጊዜም አይበቃም፡፡

አማራው አካባቢ በሚዲያም እንደሰማሁት አንድም የኤሌክትሪክ ማስፋፊያ ፕሮጀክት በኤልፓ በኩል አልተካሄደም፡፡ ምክንያቱም የፌዴሬል ተብዬውን መሥሪያ ቤቶች ሙሉ በሙሉ የተቆጣጠሩት ወያኔ-ትግሬዎች በመሆናቸው ከትግራይና በተወሰነ ደረጃ ከኦሮሞው አካባቢዎች በስተቀር በሌሎች በተለይም በአማራው አካባቢዎች ምንም ዓይነት የልማት ሥራ እንዳይከናወን ሆን ተብሎ ተከልክሏል - ባሕር ዳር አካባቢ እዚህና እዚያ የሚታዩ የዘይት መጭመቂያና የዳቦ መጋገሪያ ማሽኖች ቢኖሩ ለታይታ ነውና ከቁም ነገር የሚቆጠሩ አይደሉም - ከነዚያም ብዙዎቹ ነባር ናቸው፡፡ ማንም ሰው ወደ አማራው አካባቢ ሄጄ ላልማ ቢል በነፍጠኝነትና በዱሮ ሥርዓት ናፋቂነት ተከስሶ ወህኒ ሊወርድ ወይም ከሀገር ሊባረር ይችላል፡፡ የደሴ ቴርሼሪ ሆስፒታል ፕሮጀክት ተዳፍኖ የቀረበት ምክንያትም ከዚሁ ወያኔ-ትግሬዎች አማራ ላይ ካላቸው ጥላቻና አካባቢው ምንም ዓይነት የልማት አውታር እንዳይኖረው ለማድረግ ቆርጠው ከመነሳታቸው የማይለወጥ ውሳኔያቸው ጋር የሚያያዝ ነው፡፡ ስለዚህ አማራም ሆነ ሌላው የኢትዮጵያ አካባቢ በፍትሃዊነትና በእኩልነት እንዲለማ ከተፈለገ ወያኔዎች ከኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ከጠቅላላዋ ምድራችን ተጠራርገው መጥፋት ይኖርባቸዋል - ይህም እውን ይሆናል፡፡ ወያኔ ስል ደግሞ አስተሳሰባቸውን እንጂ አካላቸውን ማለቴ አይደለም፡፡ ለብዙ ክፍለ ዘመናት ያወከን ወያኔያዊ የገብጋባነትና የጠባብነት አመለካከትና ፍልስፍና እስካልተወገደ ድረስ ኢትዮጵያ ሰላም እንደማታገኝ ግልጽ ሆኗል፡፡ 

ሙስናና ወንጀል የወያኔ እስትንፋስ መሆናቸው የታወቀ ሆኖ ሳለ በሙስና ስም ሰዎች እየታሰሩ የሚገኙት በሰበቡ አማሮችን ለማጥቃት መሆኑ ከሚያዙት ሰዎች ስም ዝርዝር ራሱ መገንዘብ ይቻላል፡፡ ለምሣሌ ስኳር ኮርፖሬሽን ይሠራ የነበረና ከሦስት ዓመታት በፊት ለቅቆ ወደሌላ መሥሪያ ቤት በውድድር አልፎ የገባ ሰው አሁን መታሰሩ የሚጠቁመው ሌላ ሳይሆን በዘሩ ሳቢያ ግለሰቡን ለማጥቃት ብቻ ነው - እንጂ የሙስና ቋንጣ የለውምና ለምን እስካሁን ሳያስሩት ቀሩ ብሎ መጠየቅም ይቻላል፡፡ እነሐጎስና እነግደይ፣ እነአብረኸትና እነፍሬወይኒ በሙስናና በዘረፋ ያከማቹት በቢሊዮን የሚቆጠር ሀብትና ንብረት ሀገር ምድሩን እያስጨነቀ ሳለ ጡጥም እንደፈስ ተቆጥራ ስንሻውና ገመቹ በሏት በተባለች የክትፎ ሙስና የሚሳደዱበትን ምክንያት ከሙስና ቁንጮዎቹ ከአቦይ ስብሃትና ከአባይ ፀሐዬ በስተቀር ማንም አያውቅም፡፡ ዕንቆቅልሽ ምናውቅልህ፡፡  እውነት ለመናገር በአሁኑ ሰዓት በወያኔ ሥርዓት ውስጥ የሚገኝ ምንም ዓይነት ግለሰብም ይሁን ተቋም ሰውን በሙስና ለመክሰስ የሚያበቃ የሞራል ብቃት የለውም፡፡ በዚህ አንገቴን እሰጣለሁ፡፡ አንድ ሰው ከሙስና ውጪ አይኖርም - ልኑር ቢልም አይችልም፤ ልሞክር ብሎ ቢነሳ እንኳን ዕብደት ነው - በችግር ይቆጋል፤ ማንም ሰው በተለይ የመንግሥት ተቀጣሪው ቴክኖክራትና የቀድሞው ንዑስ ከበርቴ ተብዬ በወር ገቢው መኖር የማይችልበት አሰቃቂ ድህነት ውስጥ ተዘፍቋልና የትም ስትሄድ እየተቁለጨለጨ እጅህን  የሚያየው ሠራተኛ ብዙ ነው፤ ፋይልህ በሥሩ የሚያልፍ ከሆነማ ወደህ ሳይሆን ተገደህ ነው የደንቧን ጠብ አድርገህ ጉዳይህን የምታስጨርሰው፡፡ የአንድ ሰው ደመወዝ በትልቁ አምስት ሽህ ብር ነው እንበል - ደግሞም ከ500 ብር ያነሰና እዚያም አካባቢ የሚንከላወስ የደመወዝ መጠን መኖሩንም አትዘንጋ፡፡ አሁን አንድ ኩንታል ጤፍ ስንት ነው? እኔው ልንገርህ - 

በአማካይ 2500 ብር ነው፡፡ የቤት ኪራይ ስንት ነው? ይህንንም እኔው ልንገርህ፡- መሀል ከተማ ላይ 3 በ3 የሆነች አንዲት ክፍል የመኖሪያ ቤት ለመከራየት ብትፈልግ ከ3 ሽህ ብር በታች አታገኛትም፡፡ አንዲት ኪሎ ምሥር ክክ 60 ብር፣ አንዲት ኪሎ ወደቤት የምትወሰድ ሥጋ በአማካይ 200 ብር፣ አንዲት ኪሎ ቅቤ 280 ብር፣ አንዲት ሊትር ዘይት 70 ብር፣ አንጀት ጠብ ለማትል የሆቴል ቤት ምሣ በዝቅተኛ ደረጃ 60 ብር፣ ለአንዲት ስኒ የካልዲስና የትሪዮ ቡና 15 ብር፣ ለጥንድ አንሶላ 700 ብር፣ ለአንድ የክንዴ ቡቲክ ሳልቫጅ ጃኬት 1000 ብር … እየከፈልክ በትልቁ የ5 ሽህ ብር ደሞዝ ብቻ ተወስነህ ከጉቦና ከሙስና ነፃ ሆኜ እኖራለሁ ካልክ የሚሌኒየሙ ዕውቅ ኮሜዲያን መሆን አለብህ፡፡ ከፖሊስ እስከ ዳኛ፣ ከሚኒስትር እስከዘበኛ፣ ከኮሚሽነር እስከ ፓርላመኛ፣ ከልሂቅ እስከ ደቂቅ ሁሉም ተነክሮበት የሚጨማለቅበት አንድ ብቸኛ የጋራ ገመድ ቢኖረን ሙስና ነው፤ የምርትና የአገልግሎት ጥራትና የሀገር ብሔራዊ ስሜት በሙስና ተለውጠው ዛሬ ዛሬ የሀገሪቱን ሰነድ ብቻ ሣይሆን ሀገሪቱን ራሷን ባወጣች ከመቸብቸብ የማይመለሰው ዜጋ ቢሰላ ስፍር ቁጥር የለውም፡፡ ሀገር ሀገር የምንለው ጥቂት የዕድሜ ባለጠጋዎች እንጂ አብዛኛው ዜጋ ኢትዮጵያ ብትጠበስ ብትቀቀል የማትሸተው ግዑዝ ነገር ሆኗል፡፡ በአንዲት ሀገር ውስጥ የዜግነት ደረጃ መለያየት ትርፉና ኪሣራው ምን ሊመስል እንደሚችል ዕድሜ ለወያኔ በሚገባ ተምረናል፡፡ አይበለው እንጂ ሀገር በባዕዳን ብትወረር ሀገሬ ብሎ ማን ሊዋጋ እንደሚችል አንድዬ ይወቅ፡፡ እነቦሌዎች ወይንስ እነኮተቤዎች? መጪው ጊዜ እጅግ አስፈሪ ነው፡፡

ያም አለ ይህ በሙስና ሰውን መክሰስ በኢትዮጵያ ውስጥ የቧልታይና ድንቃይ ድራማ ነው (“ሙሰኛ”ን ሊያስር የሚሄደው ፖሊስ ራሱ በሣቅ ፈንድቶ መሞት አለበት! ለምን ቢባል ከደቂቃዎች በፊት ራሱም ሞስኗልና! ሙስና የሕይወቱ ክፋይና የደም ዝውውሩ አካል ነዋ! እንዴ፣ ሙስና እኮ እንደብርቅ የሚቆጠር ሳይሆን ለዕድሜ ማራዘሚያ እንደሚወሰድ ኤአርቪ መድኃኒት ከኪስ የማይለይ ተራ ነገር ነው፤ እንደነውር ከመቆጠር ካለፈም በጣም ቆይቷል፤ አንድ ነገር ገዝተህ እኮ ደረሰኝ ጻፉልኝ ብትል “ስንት ብር አድርጌ ልጻፍልህ?” ነው የምትባለው)፡፡  በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያ ቦታ የሌላት ለምሁርና በንጽሕና ልኑር ለሚል ነው -  ቦታ ያላት ለደናቁርትና ለማይማን ብቻ ነው፡፡ ወያኔዎች እውነቱን አጥተውት ሳይሆን ይህን የሙሰኝነት ካርድ የሚጠቀሙበት ሰውን ለማጥቃት ብቻ ነው፡፡ አሻንጉሊቱን ኃ/ማርያምን ጨምሮ ሁሉም የማፊያው ቡድን አባላት ካለሙስና ለአንዲትም ሴከንድ በሕይወት መቆየት አይችሉም፡፡ ይህን ሕዝቡም ሆነ ሌላው የዓለም ማኅበረሰብ ያውቃል፡፡ ነገሩ የሌባ ዐይነ ደረቅ መልሶ ልብ ያደርቅ እንዲሉ ነው፡፡ እንትን ላይ ተቀምጦ ፈስ ገማኝ አይባልም፡፡ በግልጽ ለመናገር አንድ ቆማጣም ቆማጣን ቆማጣ ብሎ ሊሰድብ አይቻለውም፡፡ እንደዚህ ዓይነት ነገር ቢገጥም የለዬለት ድንቁርና ወይም ራስን ከመርሣት የሚመነጭ ደደብነት ነው፡፡ ስለዚህ የወያኔን የሙስና ክስ በዚህ መነጽር ብናየው ጥሩ ነው፡፡

ወያኔ እንደልቡ የሚፈነጭበትን የቀድሞ ኢቲቪ አምኖ በወያኔዎች የፀረ-ሙስና እስርና የዜጎች እንግልት የሚደሰት ወይም “ወያኔ አሁን ገና ወንድ ሆነ!” ብሎ ጮቤ የሚረግጥ ዜጋ ካለ እርሱ የመጨረሻ ገልቱና ከነሱም የባሰ ደንቆሮ ነው፡፡ ወያኔን የሚያውቅ በወያኔዎች አይታለልም፡፡ መታሰርና መሰቀል ያለባቸው ወንጀለኛ ወያኔዎች አንድም ሰው የማሰር ብቻም ሳይሆን በወንጀል የመጠርጠር መብት የላቸውም፡፡ ሁሉም ቃሊቲ ሊታጎሩ ሲገባቸው ወንበሩን ስለያዙት ብቻ አንዳንዴ እንደነሱ ወንጀለኞችን ብዙውን ጊዜ ደግሞ ንጹሓንን በካንጋሩ ፍ/ቤቶቻቸው በስልክ የመሰላቸውን ፍርድ እያስተላለፉ ሲያሰቃዩ ይታያሉ፡፡ ቀን የሰጠው ቅል ድንጋይ ይሰብራል፡፡

ግብር ጣልን አሉ፡፡ ግብር የጣሉት ከትግሬ ውጪ ላለው ነጋዴ ነው፡፡ የሚገርመው ደግሞ “የግንዛቤ ማስጨበጫ” በሚሉት ጉንጭ አልፋ የቀበሌ ዲስኩራቸው አሳመንናቸው የሚሏቸው ተላላኪ አሽቃባጮቻቸው የሚናገሩት ሁሉ ከእውነቱ የሚጣረስ መሆኑ ነው፡፡ አንድ ሺ አንድ ግንዛቤ ቢጨብጡ በቀን አንድ መቶ ብር የማታገኝ የመንገድ ዳር ቡና አፍይ ሴት በምን ሂሳብ በቀን 1200 ብር እንደምታገኝ ተሰልቶ ከፍተኛ የቀን ግብር እንድትከፍል የተደረገበትን አመክንዮ ለሰው ማስረዳት ቀርቶ ለራሳቸውም ሊረዱት አይቻላቸውም፤ መቁሽሽ ስለተከፈላቸው ብቻ ቲቪ ላይ ቀርበው በሉ የተባሉትን ይዘላብዳሉ - ሲነጋ ያፍሩበታል፡፡ ዐይናቸውን በጨው ያጠቡ ወያኔዎች ድንጋይን ዳቦ ነው ብለው የማሳመን ችሎታ እንኳን ቢኖራቸው ይህን አዲሱን የግብር አጣጣል ለማሳመን መቼም ቢሆን አይቻላቸውም፤ በኃይል ከሆነ ልክ ነው፡፡ አንድ ወቅት የመለስ ፍየል ጠፋችና ፌዴራል በያቅጣጫው ፍለጋ ገባ አሉ፡፡ በመጨረሻም አንዱ ቡድን አገኛትና ወደ መለስ ቤተ መንግሥት ይዟት ቀረበ፡፡ መለስም ወጣና አያት፡፡ ሲያያት ግን በዱላ የተቀጠቀጠችና ደም በደም የሆነች ትንሽዬ የመንደር ውሻ ናት፡፡ “እንዴ! የጠፋኝ እኮ ፍየል ነው፤ እንዴት ይቺን ውሻ ፍየል ናት ብላችሁ ታመጣላችሁ” ብሎ ያፈጥባቸዋል አሉ፡፡ እነሱም ቀበል አደረጉና “ብፃይ መለስ፣ ስንደበድባት ፍየል መሆኗን አምናለች፡፡” አሉት አሉ፡፡ በዚህ መልክ ነው  እንግዲህ ላለፉት 26 ዓመታት አናት አናታችንን እየተቀጠቀጥን እርቦን ሳለ እንደጠገብን፣ ታርዘን ሳለ እንደለበስን፣ ተጎሳቁለን ሳለ እንዳማረብን፣ ከስተን ሳለ እንደወፈርን… አምነን እንድንቀበልና ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብም እንድንመሰክር በወያኔ ትግሬዎች እየተገደድን አሳራችንን ስንበላ የከረምነው፡፡ ሰይጣን እጁን ታጥቦ ከጠፈጠፋቸው አጋንንታዊ ሥሪቶቹ መካከል እንደወያኔ መቶ በመቶ ስኬታማ የሆነ አለ ብዬ አላስብም፡፡

የማፊያው የወያኔ ቡድን አባላት ከንጉሥም በላይ ናቸው፡፡ መግደልን ጨምሮ የፈለጉትን ወንጀል ቢሠሩ፣ ዘረፋና ንጥቂያ ቢያካሂዱ ማንም አይነካቸውም፡፡ ሕግ የለም፡፡ ፖሊስ የለም፡፡ ዳኛ የለም፡፡ ፍርድ ቤት የለም፡፡ ለነሱ ምንም ነገር አይሠራም፡፡ አዲስ አበባ ውስጥ - ሰሞኑን - አንድ ሰው መኪናውን ከበስተኋላው አንድ ሰው ይገጭበታል፡፡ ተገጪው ወርዶ መኪናውን ሲያይ በጣም ተጎድታበታለች፡፡ ገጪውም ይወርድና “አሥር ሺህ ብር ልስጥህና እዚሁ እንገላገል” ይለዋል፡፡ ተገጪው ግን የመኪናው ጉዳት ከባድ በመሆኑ ትራፊክ ፖሊስ ያስመጣል፡፡ … ጉዳዩ ወደ ፖሊስ ጣቢያ ሲሄድ ነገሩ ይዞርና ወንጀሉ ወደ ተገጪው እንዲዞር ይደረጋል፡፡ ትራፊክ ፖሊሱም “ወንድሜ! ባለሥልጣን አይከሰስም፡፡ እሳቸው ባለሥልጣን ስለሆኑ በሰላም መገላገል ከፈለግህ ዝም ብለህ ወደቤትህ ሂድና የራስህን በራስህ አሠራ፡፤ ኋላ ነግሬሃለሁ!”  ብሎ ያባርረዋል፡፡ ወደፊት ልግፋ ቢል ዘብጥያ ሊወርድ ሆነ፡፡ መኪናውን 50 ሺህ ብር አውጥቶ አሠራት፡፡ ይህ ሰው አሁን “ሀገሬ የት ነው? እኔስ ማን ነኝ?” እያለ እንደመወፈፍ አድርጎታል፡፡ እርግጥ ነው - ሀገር የለንም፡፡ ባለሥልጣን ከሆንክና በዚያ ላይ ትግሬነትን ከደረብክበት ሁሉ በጅህ ሁሉ በደጅህ ነው፡፡ ትግሬ ሆነህ ማንንም ከቀየው አፈናቅለህ ያሻህን ቦታና የመኖሪያ ቤት ብትይዝ ዳኛህ ኅሊናህ እንጂ በኢትዮጵያ አንድም የሚገዳደርህ ህግ የለም፡፡ ማሳሰርና ማስፈታት፣ ማስገረፍና ደብዛን ማስጠፋት መብትህ ነው - ከአንተ የሚጠበቀው ወያኔ ትግሬ መሆን ብቻ ነው፡፡  ይህችን የዘመን ህግ መርሳት የለብህም፡፡ አደራህን ግን መከራህ ተዝቆ አያልቅምና አማራ ሆነህ መፈጠርን እንዳትመርጥ! ኦሮሞ መሆን ትችል ይሆናል፤ ነገር ግን ከወንድሞችህ ጋር እንዳያጣሉህ ጠንቀቅ በል! ነገም ሌላ ቀን ነውና፡፡  

የምትጠላውን ገድለህ ወይ አስገድለህ ተንቀባረህ የምትኖርባት ሀገር - ኢትዮጵያ! የፈለግኸውን ወንጀል ሠርተህ በገንዘብህና በነገድህ ተማምነህ በነፃነት የምትኖርባት ሀገር - ኢትዮጵያ! በድለህ ዘንጠህ የምትኖርባት ሀገር - ኢትዮጵያ! ደንቁረህ እንደምሁር የምትቆጠርባት ሀገር - ኢትዮጵያ! ሳትማር የፈለግኸውን ዲግሪ የምትጭንባት ሀገር - ኢትዮጵያ! ወንጀለኞችን አቅፎና ደግፎ አሞላቅቆ የሚይዝ የወሮበሎች መንግሥት ያለባት ብቸኛዋ ሀገር - ኢትዮጵያ! ጊነስ ቡክ ኦፍ ሪከርድስ ባላወቀውና ባልመዘገበው ሁኔታ ቤተ መንግሣቷን ወላድ አይያችሆች የሚፈነጩባት ጉደኛ ሀገር - ኢትዮጵያ! አዲዮስ ኢትዮጵያ፡፡ እንደኢትዮጵያ የተሟላ ውድቀት ገጥሞት የሚያውቅ ሌላ ሀገር ቢኖር ይገርመኛል፡፡

  አሁን ደግሞ በወያኔ የተጠለፈችው ቤተ ክርስቲያን ሕዝቡ እንዳይቀበር ዋጋ ቆልላለች፡፡ ለአንድ አስከሬን 4 ሺህ ብር! አራት ሺህ ብር ካልተከፈለ ወስዳችሁ የፈለጋችሁት ቦታ ጣሉ እየተባልን ነው፡፡ ጉድ ፈላብን፤ ጉዳችን ተንተከተከ፡፡ አፄውና ደርጉ በጉያቸው ይዘውት የነበረው ገመናችን ወጥቶ ፀሐይ እያንቃቃው ነው፡፡ ካህናቱም ከፓትርያርክ እስከ ዲያቆን የአጋንንት ውላጅ ሆኑብንና ከወያኔው ባልተናነሰ ከዱርየው የወያኔዎች መንግሥትና ከዲያብሎስ ጋር እየተሸራሞጡ ቁም ስቅላችንን እያሳዩን ነው፡፡ የቀብር ቦታ ይሸጣሉ፤ በጉቦና በሙስና ሥራ ያሲዛሉ፤ ከዝቅተኛ ደብር ወደ ትልቅ ደብር በሊቀ ገበዝነት ወይም በቅስናና በዲቁና አገልግሎት ለመዛወር በመቶ ሺዎች የሚገመት ጉቦ ይከፈላል፡፡ የማይሠራ ወንጀልና ኃጢኣት የለም፡፡ ብለው ብለው እኛንም ያለችንን ብቸኛ መጽናኛ ሞትንም ሊከለክሉን ነው፡፡ ቆመን ዕዳ፤ ሞተንም ዕዳ - እንኑር እምቢ - እንሙትም እምቢ፡፡ ለሞተውስ ግዴለም - ተገላገለ፡፡ ወስፋቱን የሚሸነግልበት ቤሣ ቤስቲን የሌለው ድሃ ቤተሰብ አንድ ወገኑ ሲሞትበት ቆጥሮት የማያውቀውን የገንዘብ መጠን ለሬሣ ማስቀበሪያ ይጠየቃል፡፡ እግዚአብሔርም ከሰው ተደርቦ ጨከነ፡፡ ዝም አላቸው፡፡ ዝምታውም የመቃብር አዘቅት ያህል እጅጉን ገነነ፡፡ ወዮ በሉ! ወዮ ለኢትዮጵያ! ለአንዲት ከርስ መሙያ ለብጣሽ እንጀራ ብሎ ሀበሻ ሊጨራረስ ነው!

አሥራት አብርሃም ሰሞኑን ግሩም መጣጥፍ ጻፈ፡፡ ግን ምን ዋጋ አለው - “ወጣ ወጣና እንደሸንበቆ ተንከባለለ እንደሙቀጫ” ሆነና ዐረፈው፡፡ አሥራት ወያኔን አያውቅም ወይም ሞኝነት ያጠቃዋል፡፡ ከዚህ አልፌ እርሱን በድጋፍ ሰጪነት መፈረጅ ግን ኅሊናየ አልፈቀደልኝም - ምንም እንኳን የሕወሓት ቫይረስ የሚሞተው በሺዎች ዲግሪ ሴልሼስ የሙቀት መጠን መሆኑን ብረዳም፡፡ አሥራት ወያኔን ቢያውቅ ኖሮ ከመጣጥፉ የጠቀስኩትን ከዚህ በታች ያለውን ሃሳብ በጽሑፉ ውስጥ አይጨምርም ነበር፡፡ ወያኔ ከመቼ ጀምሮ ነው ተከሶ ፍርድ ቤት ቀርቦ የሚያውቅና የተፈረደበት? “የዕብድ ገላጋይ ድንጋይ ያቀብላል” ይባላል፡፡ አሥራት ትልቅ ስህተት ፈጽሟልና በዚህችስ አደራችሁን ጠይቁልኝ፡፡ ክፉኛ ታዝቤዋለሁ፡፡ “ወያኔ በአንጻራዊነት የተሻለ ደረጃ ላይ ይገኙ የነበሩትን ነፃ ፍርድ ቤትን፣ ዴሞክራሲን፣ ሰላምን፣ ፍትህን፣ እኩልነትን፣ የሕዝብ አንድነትን፣ የሀገር ግዛትን … ድራሻቸውን አጥፍቶ በምትካቸው ስደትን፣ ሞትን፣ ግድያና እስራትን፣ ችግርንና ስቃይን በማስፈኑ አይደለም ወይ ይሄ ሁሉ ሀገራዊ ትርምስና ዕልቂት የተፈጠረው” ብላችሁ ለአሥራት ንገሩልኝ፡፡ አሥራት በዚህች ሃሳቡ ብቻ የኢትዮጵያን ሕዝብ ይቅርታ መጠየቅ እንደሚኖርበት አምናለሁ፡፡ ወያኔ ከሳሽ፣ ወያኔ ዳኛ፣ ወያኔ ጠበቃ፣ ወያኔ ዐቃቤ ህግ፣ ወያኔ ፖሊስ፣ ወያኔ እስረኛ ጠባቂ፣ ወያኔ ሁሉም ነገር በሆነባት ሀገር ውስጥ ማን ነው ማንን የሚከሰው? በማወቅም ይሁን ባለማወቅ እንዲህ የሚል ሰው ለማያውቁት ይታጠን፡፡

I don’t know whether he wants to legitimize TPLF or not, nevertheless; he shouldn’t dare say ‘TPLF must bring TPLF to the court of TPLF whose prosecutors and judges are TPLFites themselves’. So funny! What, perhaps, an absolute innocence!

“… ባለአንድ መኝታ ቤት ተመዝጋቢዎች ደግሞ የጋራ ኮሚቴ ማቋቋምና መንግስት[ን] መጠየቅ አለባቸው። ጉዳዩም ወደ ፍርድ ቤት ነው መሄድ ያለበት። ምክንያቱም ፕሮግራሙ አሁን በታደለው የክራውንና የሰንጋ ተራ ኮንዶምኒየም በግልፅ የታጠፈ በመሆኑ ከዚህ በኋላም በሌሎች ኮንዶምኒየም ባለአንድ መኝታ እንዳለማወቅ አይቻልም። ስለዚህ ተመዝጋዎቹ ጉዳዩን ወደፍርድ ቤት መውሰድ ነው ያለባቸው የሚል እምነት ነው ያለኝ። (አፅንዖት የተጨመረ)
mz23602@gmail.com

No comments: