ትግራይ አምና እና ዘንድሮ
(ሀ) የማይረሳው የከሳቴ ብርሃን ት/ቤት ትዝታ --121
ከጌታቸው ረዳ Ethiopian Semay
4/7/25
ክደራሲው ለዛሬ ትወልድ ወጣት አንባቢዎች የተሰጠ ምክር!
ዛሬ ሃገራችን የምትለዋት ኢትዮጰያ ከሰማይ ተጋግራ የተሰጠቻችሁ ሃገር ሳትሆን ብዙ ለፍተን
፤ከጠላት ጋር ተታኩሰን፤ ሞተን፤ ተሰድበን፤ ብዙ ድካምና ደም የፈሰሰባት ምድር ያስረከብናችሁ መሆንዋን ዘንግታችሁ በምድሪቱ ሕልውና
ላይ ስታላግጡ በማየቴ የተስማኝን ውስጣዊ ሐዘንና ቅሬታየን እየገለጽኩ ታሪክ ወደ ኋላ ላስቃኛችሁና ሐዘን ተሰምቷችሁ ምናልባት ልብ
ብትገዙ ስለ ኢትዮጵያ የተከፈለው መስዋዕት እነሆ ከምጽሐፍይ ላስቃኛችሁ።
ቁስለኛና በሽተኛ የሚቀበለው ብቸኛው የከተማዋ ሆስፒታል ከየቀጠናው የመጡ የቆሰሉ ብዙ ሠራዊቶች በብዛት ስለተቀበለ ከአቅሙ በላይ ሆኖበት፤ በሆስፒታሉ የመተላለፊያ በረንዳዎች ላይ ሳይቀር እንዲተኙ በመደረጉ፤ ብቸኛው ሆስፒታል በቁስለኛ ስለተጨናነቀ፤ አማራጭ ሆኖ የተገኘው ከተማዎቹ ወደ እሚገኙ ትምሕርት ቤቶችና ህንጻዎች እንደመታከሚያና ማረፊያ ሆነው እንዲያገለግሉ ቅጽበታዊ ውሳኔ ተደረገ።ከነዚህ ውስጥ “ክሳቴ ብርሃን” ት/ቤት ነበር።፡ ህንጻው ብዙ ክፍሎች ስለነበሩት የቆሰለው ሠራዊት በብዛት በማስገባት በጊዜአዊ አልጋዮች እና ወለል ላይ እንዲተኛ ተደረገ።ከላይ እንደገለጽኩት ወቅቱ ክረምት በመኖሩ፤ የቆሰሉ ሠራዊቶች ወታደራዊ ቦቴ ጫማቸውና ልብሳቸው በጭቃ እና በደም የተለወሰ ሆኖ ለማየት እጅግ የሚያበሳጭ እና የሚያሳዝን ፈታኝ ወቅት ነበር። ሠራዊቶቹ አልጋ ላይም ሆኑ ወለል ላይ የተኙት አጣዳፊ የማጓጓዝ ስራ ሲሰራ በዛው ላይ ብዛት ስለነበራቸው-ጫማቸው፤ የቦምብ ትጥቃቸውና የጠበቀው ቀበቶአቸው ከነትጥቃቸው ተኝተው ይታያሉ።ይህ አሳዛኝ የሆነ የእርስበርስ ጦርነት ላየ ሰው እውነት ከባዕድ ጋር እንጂ
በአንድ አገር ዜጋ ልጆች የተደረገ ጦርነት አይመስልም።እጅግ የሚያሳዝነው ግን ያኔም ሆነ ዛሬ እስካሁና ደቂቃ ድረስ ወያኔዎች በሚያሰራጩዋቸው የፕሮፓጋንዳ መገናኛዎች “ውጊያው በጣሊያን እና በኢትዮጵያ ዜጎች መካካል እንደተደረገ
አድርገው በማየት ‘ወራሪ” የሚል ቃል በመጠቀም፤ የጦርነቱ ተከታታይነት
“ቀዳማይ ወራር፤ ካልኣይ ወራር“፤ ሳልሳይ ወራር..” (1ኛ ወረራ፤ 2ኛ ወረራ፤ 3ኛ ወረራ…) በማለት ኤርትራኖች የሚጠቀሙበትን “መሬት ለመንጠቅ የመጣ፤ ኮሎኒያሊስት/ ባዕድ” ለማለት የሚጠቀሙበት አገላለጽ ነው የትግሬ ወያኔዎች ሲጠቀሙበት የነበረው። ደርግ “ተገንጣይ ቡድኖች” ብሎ ሲገልጻቸው፤ ወያኔዎች ደግሞ በሚገርም አሳፋሪ አገላለጽ “ወራሪ ሃይል” በማለት ኢትዮጵያዊነታቸው በግልጽ የጣሉበት አጋላለጽ
ነበር።በወራሪና በባዕድ የተደረገ ጦርነት ብለው ስለሚያምኑም፤ የዓረቦች አሽከርነት ለማሳየት “ይመስላል” ከዓረቦች (ባሕሬን) እና ከሰሜን አፍሪካ (ሞሮኮ) አደባባዮች ዛሬም በሕዝብ መሰብሰቢያ አደባባይ ተተክለው የሚታዩት ከነዚህ ዓረብ አገሮች የተቀዳ ዓረባዊ ‘የሐውልት” ቅርጽ ቀድተው” መቀሌ ከተማ ውስጥ ለተሰውት ተዋጊ ሃይላቸው “ሃውልት” አቁመዋል።
ወደ ክሳቴ ብርሃን ት/ቤት ቁስለኛ ማቆያ ህንጻ ልውሰዳችሁ። ከሳቴ ብርሃን የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ/ክርስትያን ትምህርት የሚሰጥበት መንፈሳዊ ት/ቤት ነው። በሰራዊቱ ብዛት እና ድሕረ ውግያ መደረግ የነበረባቸው ጥናት ባለመደረጉ ቁስለኛ የሚመዘግብ፤ የሚያስተናግድ የሰው ሃይል ስላልነበረ አስቀድሜ እንደገለጽኩት ከነ-ቦምባቸው እና የታጠቁት ሽጉጥ ተጋድመው ያቃስታሉ።
በዛው ብርዳማ ወለል ላይ ያለ ብርድ-ልብስ፤ በትራሳቸው ላይ ጉዝጓዝ በሌለው ወለል ላይ በጀርባቸው ተንጋልለው፤ በጥይት እና በቦምብ የተመታው የቆሰለው ገላቸው፤ ስቃዩ አላስችል ብሎአቸው ፊታቸው በላብ ተጠምቆ፤ ገላቸው በትኩሳት ነድዶ፤ የስቃይ ድምፅ በማሰማት ለተጨማሪ ስቃይ ተጋለጡ።
የሰው ልጅ አንጀት ሰርስሮ በሚገባ ሲቃ እያቃሰቱት የነበረው የስቃይ ጽምፅ እንኳን ለሰው ልጅ አንጀት የአራዊት ጀሮ የሚያሰቆም፤ የሚያባባ ፤የሚያስለቅስ ድምጽ ስለነበር፤ በጆሮው የሰማ የመቀሌ ኗሪ ሕዝብ ፤ እንዲህ ያለ ስቃይ ለምን እና እንዴት ተከሰተ ለሚለው ምርምር ለምሁራን ትቶ፤ ባደመጠው የስቃይ ድምፅ
ስለባባ የማልረሳው በዓይነቱ ልዩ የሆነ ተስምቶና ታይቶ የማይታወቅ ኢትዮጵያዊ ሰብአዊነት የተመረኮዘ ያየሁትን የማስታውሰውን ለታሪክ ላስመዝግብ። እንደገለጽኩት የሚያርፍበት መጠለያ ስላልተዘጋጀለት ፤ ከሠራዊቱ ብዛት አኳያ ለተቀናጀ እንክብካቤ ስላላመቸና በሃላፊነት የወሰደ የሰራዊት አዛዦችም ከነበሩ እየተካሄደ ወደነበረው የውጊያ ቀጠናዎች ቀልባቸው ስለተጠመደ የተመደበው የሰው ሃይልም በቂ ስላልነበረ፡ የአካባቢው ባለሥልጣኖች፤ አጣዳፊ ዝግጅቶች
ካልወሰዱ እርምጃ (ሞት) ለመውሰድ የሚሽቀዳደም እንጂ በጥናት የታቀደ ሃላፊነቱን የማይሸከም ሥርዐት” ስለነበረ፤ ከሚመጣባቸው ‘ዱብ ዕዳ’
እርምጃ ለመሸሽ ሲሉ፤ የከተማው የመንግሥት ተጠሪ ቅርንጫፍ መስርያቤት ሃላፊዎች በመሰብሰብ፤ በየሰዓቱ በሄልኮፕተር
ከጦር ሜዳ የሚመጣው ቁስለኛ የት እና እንዴት ያለ እንክብካቤ መደረግ እንዳለበት፤ እንደየ ጉዳቱ አይነት እየለዩ በየክፈሉ ላመስተኛት ተወያይተው የተቻላቸውን ማድረግ ጀመሩ።
በሰራዊቱ ብዛት እና በመንግሥት ጥናት ባለመደረጉ፤
እየፈሰሰ ያለው የቁስለኞችን ደም ለማስቆም ለመሸፈን የቁስል ‘ሻሽ/ጐዝ ፤ መድሃኒት መውጊያም፤ የመርፌ መቀቀያ ‘ዳርፉር’ ፤ ብረት ድሰት’ ፤ የሕክምና ፕላስተር፤ የመሳሰሉ ጥቃቅን ነገሮች ሕዝቡ ከየቤቱ ካለው እንዲለግስ በተጠየቀበት መሰረት ያለውን ቁሳቁስ ሁሉ ከየቀበሌው እያሰባሰበ ወደ መጠለያ አመጣ። የሰራዊቱ ቁስለኛ ብዛት ስለነበረው፤ በዛው መጠን የሕክምና ባለሞያ ያንን የቁስለኛ ብዛት የሚሸፍን የሰው ሃይል ስለታጣ፤ በዚህ የተነሳ ቁስለኛውን የሚያክም ስላልነበረ፤ እንደየ ቁስሉ ስፋት ጥልቀትና ክብደት ጠረኑ እየለወጠ በመምጣቱ፤ ቁስለኛው ለቀናት አንዳንዱም ለሳምንት ሳይታከሙ በመቆየታቸው፤ ቁስሉ ‘ቂም’ (ኢንፌክሽን) በመያዙ ምክንያት በትኩሳት ‘ ነድሮ ፤ በደምና በመግል የተጣበቀው ቁስል በማከም ሂደት ውስጥ ወጣቱና ሕዝቡ፤ ጠረኑ አላስጠጋ ያለውን በደምና መግል የተጣበቀው ቁስል፤ በእጁ እያፈረጠ፤ በጨርቅና በጥጥ ውሃ እየነከረ ጠረኑ የለወጠ ቁስል እየሸተተውም ቢሆን በማጽዳት የማይረሳ ኢትዮጵያዊነቱን ያስመሰከረበት ወቅት ነበር።
እዚህ ላይ ልጠቅሰው የምፈልገው፤ የሕክምና ጥጥ እና ጎዝ/ሻሽ እጥረት ስለነበረ፤ የቁስለኛው ቁስል ስያክም ከየቤቱ ያመጣው አንሶላም ሆነ ንጹህ ስስ ጨርቅ በቀጭኑ እየቀደደ ነበር ቁስሉን እያጠበ ለቁስል መሸፈኛ የተጠቀመው ። እንደዚያ ያለው ትውልድ/ያ ሕዝብ ዛሬ በክረስቶስ ስም ለምነህ ለማስረጃ እንኳን ለሽታ የሚገኝ አይመስለኝም። ባጭሩ ‘ድንግል ኢትዮጵያዊ’ ነበር! ለቁስለኞቹ የተዘጋጀ የሌሊት (ፕሮን) ልብስ/ ፒጃማ/ የመሳሰሉ ስላልነበሩት፤ ቁስለኛው ሰራዊት፤ በውግያው ወቅት በደምና በጭቃ ተለውሶ፤ ወደ ደረቅ አጐዛነት የተለወጠው ወለል ጋር ተጣብቆ ለብሶት የነበረው ወታደራዊ ደምብ ልብስ ሕዝቡ ከየቤቱ የመጣለትን አንሶላና ነጠላ በማልበስ ፤ የቆሸሸው ልብስ በየወንዙና እቤቱ ድረስ ወሰዶ በማጠብ፤ በጭቃ፤ በላብና በደም የደረቀ የወታደሩ ልብስ አጥቦ አልብሶአቸዋል።ለቀናት፤ ለሳምንታት መጀመሪያ ሲመጣ ተንጋሎ በተኛበት ሳይላወስ የቆየውን ቁስለኛ ደግፎ በመስነሳት አከላዊ እንቅስቃሴ እንዲያደረግ፤ ወለል ላይ እና አልጋ ላይ በመተኛት የደነዘዘው አካላቱ እንዲፍታታ አድርጎ ትንፋሽ እንዲያገኝ ረድተዋል።
ከጦር ሜዳ ቆስሎ ሲመጣ በጥብቅ ከርሮ ታስሮ የነበረው ወታደራዊ ጫማቸው ለብዙ ቀናት ከእግራቸው ስላልወለቀ አግራቸው በማበጡ፤ ጫማቸውን አውልቀው የረጋወንና ደማቸውና ያበጠው እግራቸው በዘይትና በደረቁ በማሸት አንገቱን ቀና እንዲል ደግፈው፤ ከየቤታቸው ያመጡት ወተትና ምግብ አልከፈት ያለውን የቆሰለው ጉሮራቸው አለሳልሰው በማጉረስ ያደረጉት ሰብአዊ ርሕራሄ እና ዛሬ ያለው የትግራይ ሁኔታ ሳነጻጽር ሁኔታው እንቆቁልሽ ይሆንብኛል ። እንዲህ ያለ ጥንታዊ ርሕራሔና ሞራላዊ፤ ዜግነታዊ ግዴታ ‘ወድዶ ያለ ግዴታ’ በመፈጸም፤ መብራት ባልነበረበትና መብራት በሚቋረጥበት ክፍል ውስጥ ተኝቶ የነበረውን ቁስለኛ ሰራዊት፤ ከቤቱ ያመጣውን ሻማ አብርቶ፤ ቁስለኞቹ ከተኙበት አልጋ እና ወለል ደግፈው አንገታቸውን በማቅናት በስቃይ እና በኡኡታ የደረቀ ጉሮራቸው ‘ውሃ’ በማጠጣት፤ የደረቀው ከንፈራቸው፤ በጨርቅና በጥጥ እያራሱ፤ በትኩሳትና በጩኸት የተሰነጣጠቀው የደረቀ ከንፈራቸው እንዲርስ
አድርገዋል።
የመቀሌ ሕዝብ እንደዛሬ ሳይሆን፤ ውርቃማ ከሚባሉ የመጽሐፍ ቅዱስና ቁርአን ሕግጋቶች ከሚጠቀሱ ሰብአዊ "ላንተ እንዲደረግልህ የምትፈልገውን ነገር ለሌላው አድርግ" የሚለውን መርሆ ተነስቶ “የተደናገጠውን ልብ ያረጋጋ” ሕዝብ ነበር። "ነበር" ብየ የምገልጸው በዛሬው ጊዜ እማሃሉ ውስጥ ከሸገር አውራጃ እና ከወስጡ የበቀሉ አክራሪ ፋሺስታዊ ጎሰኛነት የሚያስተምሩ የተለከፉ ግለሰቦች እማሃሉ ውስጥ በካድሬነትና በከፍተኛ የመንግሥት መዋቅርና በየትምህርት ተቋማቱ እና በኪነት ባለሞያዎችና በየቤተጸሎቶች ተሰማርተው የሕዝቡን ስነ ልቦና በጎሰኛነት ስለበከሉት፤ “ነው” ከሚለው ቃል ይልቅ “ነበር’ የሚለው አማራጭ አድርጌ የገለጽኩት።
ይህ በዚህ እንዳለ፤ ሠራዊቱ የከተማው ኗሪ
ሕዝብ ዜጋዊ
እንክብካቤ ካገኘ በኋላ፤ ትንሽ ሕይወት የዘሩ ሰራዊቶች ከየአልጋቸውም ሆነ ከተኙበት ወለል እየተነሱ፤በምርኩዝም ሆነ በጓዶቻቸው ተደግፈው እያነከሱ በየክፍሉ እየዞሩ፤ የሰርዓቱን መሪዎች በማውገዝ፤ ሠራዊቱን በመቀስቀስ ፤ የጦር አለቆች እና ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣኖች ከያሉበት ቦታ እንዲጎበኝዋቸው አስቸኳይ የአድማ ጥሪ ቴሌግራም ይደረግ ብለው ስለተስማሙ፤ በጠየቁት መሠረት፤ ከጥቂት ቀናት ቆይታ፤ እንዲመጡላቸው የጠየቁዋቸው የጦር አለቆች ወደ መቀሌ መምጣት ጀመሩ። አለቆችም፤ በእያንዳንዱ ክፍል በመግባት ‘እንደምን አላችሁ?” እያሉ በመጠየቅ ቁስለኞችን መጎብኘት ጀመሩ።
አለቆቹ ወደ ክፍል ሲገቡ፤ ከአልጋቸው መነሳት ያልቻሉ ኩፉኛ የተጎዱ በተለይ እጆቻቸው ወይንም እግሮቻቸው ያጡ ቁስለኞች፤ ‘በእጆቻቸው እያወዛወዙ ወደ አልጋቸው ተጠግተው እንዲያነጋግሯቸው ሲጠሩዋቸው፤ የሠራዊቱ አለቆችም ወደ አልጋው ተጠግተው ‘ደህና ናችሁ ጓዶች?” ብለው ሲጠጉ፤ ምራቃቸውን ወደ አለቆቻቸው ሲተፉባቸው፤ አለቆቹም ተደናግጠው ከክፍሉ ሲወጡ፤ በምርኩዝ የሚሄዱ እንዳንዶቹ ቁስለኞችም ኋላ ኋላቸው እየተከተሉ ሲሰድቧቸው ሌሎችም ጥግ ጥግ በረንዳው ላይ የቆሙ እና የተኙ ቁስለኞች ‘በፉጨት’ እያፏጩ ይቀልዱባቸውና ቁጣቸውን ይገልጹ ነበር።
ልዩ ትዕይንት የነበረው ደግሞ፤ ችግራቸው የአገሪቱ የመገናኛ ማዕከሎች/ ራዲዮ/ ጋዜጣ እንደማይዘግቡላቸው ስለሚያውቁና በቦታውም የተገኙ ጋዜጠኞች ስላልነበሩ፤ በጣም ቀልጣፋ ተነጋሪዎችና በየክፍሉ በተፈጥሮ ስጦታቸው ቀልድ ነጋሪዎች (ኮመዲያን) የነበሩ ‘ቀልደኞች” በስቃይ የሚያቃስቱትን ጓዶቻቸውን ሲያዝናኑ የነበሩ ከየክፍሉ የተመዘዙ አባሎች፤ በየክፍሉ በመሄድ፤ አንዱ የመድረክ አስተዋዋቂ ፤ ዜና ሰብሳቢ፤ አንዱ ዜና አንባቢ፤ ሆነው በመመደብ፤ የጦር አለቆቹ ሲጎበኙዋቸው በዕለቱ የታየው የጉብኝት ትዕይንት
‘በዜና መልክ እና በቀልድ አጠናቅረው” በሚያስደንቅ አነጋገርና አማርኛ፤ ፖለቲካዊ ቅመም ጨምረውበት፤ ስለ ታየው ሩጫ እና አድማ
ያቀረቡት አቀራረብ እጅግ የማልረሳው ታሪክ ነበር። ከተማ ያደጉ ወጣት ወታደሮች ስለነበሩ አማርኛቸው ሲያንበለብሉት፤ አንዳንዱ ባዲስ አበባዎቹ (አራዳ የምትልዋቸው ይመስለኛል) ልሳን
እየተጠቀሙ ዜናውንና ቀልዱን “ያለምንም ጽሑፍ” በቃላቸው ሲያንበለብሉት የሰማ ጀሮ መደነቁን ለመግለጽ ቃላት ፈልጎ የሚያገኝ አይመስለኝም። ዜና አንባቢዎቹ እና ቀልድ ነጋሪዎቹ ባሯርዋጧቸው አለቆቻቸው ላይ ያጠናከሩት በያይነቱ ቀልድና ዜና ሲተነትኑት የሰሙ በከባድ ቁስልና ትኩሳት ተይዘው በሲቃ ሲጮኹ የነበሩ፤ ከተራ ወታደር እስከ መስመራዊ መኮንኖች የነበሩበት የቁስለኞች ክፍል ፤ ሳያስቡት ‘ፈገግ’ እያሉ ጥርሳቸው ብልጭ እያደረጉ የጭንቀት ፈገግታ ሲያሳዩ ማየት በትዝታ ፈለግ አሁን ሲታየኝ ልቤ ኩፉኛ ይሰበራል።
ሠራዊቱን ለማጽናናት ለመደገፍ በፈቃደኝነት ከተገኙ ኗሪዎች አንዱ እኔ ስለነበርኩ፤ ለእናት አገሩ ለኢትዮጵያ ሲል ሠራዊቱ በሲቃ ተይዞ፤ እንደ ጋለ ብረት የሚያቃጥል ገላው እየተለበለበ፤ ትንፋሽ አጥሮት ሲታገል ባስጨናቂ ትኩሳት እና ላብ ተነክሮ የደረቀው ከንፈሩና ጉሮሮው ደርቆ የትንፋሹ ጠረን ቀይሮ፤ “የውሃ ያለህ” ፤“እማየ ድረሺ” ሲል ገላውና
ከንፈሩ በቀዝቃዛ ውሃ እያራስኩ ሳጽናናው፤ በዛው ስቃይና የሞራል ጥንካሬና መስዋዕት የከፈለው ያ የመሰለ ሠራዊት ተመን የማይገኝለት መስዋዕት መክፈሉን በዓይኔ ስላየሁት፤ ወያኔ ሥልጣን ከያዘ በኋላ እነዚህን የዋሆች ወደ ለማኝነት ህይወት ወደ በረንዳ ሲጥላቸው፤ ከወያኔ ጋር የማይታረቅ ጸብ የፈጠረብኝ፤ አንዱ ምክንያቴ ይኸኛው ነው። አሁንም ሳስታውሰው እንጀቴ ይረበሻል! ወደ ታሪኩ ልመልሳችሁ። በእንደዛው የመሰለ አስጨናቂ
ክስተት እና ከባድ ቁስል እየተሰቃዩ፤ እርስ በርሳቸው በጠንካራ ሞራል ተደጋግፈው ያየ ሰው፤ የኋላ ኋላ የትም ቀርተው፤ በየበረንዳው እና በስደት ዓለም ተበትነው ማየት፤ እውነትም ኢትዮጵያ “የሞተልሽ ቀርቶ፤ ያልሞተልሽ በላ” የሚባለው እውነት ነው።
ይህንን ሳስበው አንድ ግጥም ትዝ አለኝ።
የዘመናችን “የኪነት ፈላስፋና የድምጸ መረዋው የቅዱስ ያሬድ ፍሬ’ የሆነው አገር ወዳዱ ዝነኛው ሙዚቀኛው ቴዲ አፍሮ “ሊስትሮ” በሚል ግጥሙ ውስጥ ያለውን ልጥቀስ።
ጫማ በመጥረግ ወደ ከፍተኛ ደረጃ ያደገ አንድ ሊስትሮ፤ ከዚያ ከድህንት ዓለም ወጥቶ አንድ ቀን ጫማ ለማስጠረግ ሊሰትሮ ጋር ሄዶ ፤ ከሊሰትሮዋ/ ከሳጥንዋ /ላይ ቆሞ ጫማውን
እያስጠረገ እንዳለ ውለታ ለዋለችለት የሊስትሮ ዕቃው የገጠመላትን ‘’ቴዲ አፍሮ” በእንዲህ ይገልጸዋል፦
“በጣሙን አዝናለሁ ውዷ የሊስትሮ ዕቃዬ፤
ምንም እንኳ ብትሆኚ ባለውለታዬ፤
በጫማ ብረግጥሽ አይክፋሽ ግድየለም፤
ባታውቂው ነው እንጂ ለዋለላት ሁሉ እንዳዛው ነው ዓለም።
ከስሜቴ ልውጣ እና እንቀጥል ወደ ታሪኩ ልውሰዳችሁ። ሁኔታው በሰራዊቱ እና በከፍተኛ አዛዦች እንዲሁም አዛዥ አና አዛዥ መካካል በሁኔታው የተነሳ ያለመጣጣም ስለተነሳ፤ ቁስለኛው ኮለኔል ታሪኩ ላይኔ የተባሉ ከፍተኛ የጦር አዛዥ እንጂ ሌላ እንዳይላክላቸው ስለጠየቁ፤ በጠየቁት መሰረት ኮለኔሉ ወደ መቀሌ መጥተው፤ ቁስለኞች ወደ ተኙበት ክሰቴ ብርሃን ት/ቤት መጡ። ቁስለኛው የቻለና ያልቻለ በምርኩዝ እና በሰው እየተደገፈ በየበረንዳው እና እመሃል መሰብሰብያው ላይ ተጠራርቶ በመሰብሰብ፤ ለኮለኔሉ ጥያቄ አቀረቡ። ተናጋሪዎቹ አስቀድሜ እንደገለጽኩት እሳት የበሉ ተናጋሪዎች ስለነበርዋቸው፤ ቅሬታቸውን አንበለበሉት። ቆም እያሉ ተናጋሪዎቹ ‘እምባ ሲተናነቃቸው” ያዩ አዛዡ በትዝታ ተጭነው በሐዘን ተውጠው ያደምጣሉ። አንዳንዶቹ ቁስለኛ ወታደሮች በዛው ጸጥታ በሰፈነበት አየር ንግግር ሲደረግ፤ ከበረንዳው ላይ ተንጋልለው ‘በሰለለ/ የደከመ/ ድምጽ የታጀበ፤ አንጀት የሚፈታተን የስቃይ ድምጽ ”የሰሙ በረንዳው ጥግ ላይ ካጠገቤ ጎን ቆመው የነበሩ ለእርዳታ የመጡ የከተማው ወጣት ሴቶች፤ ዓይናቸው ውሃ ቋጥሮ
በድንገት ሊፈነዳ የተቃረበ ‘ዕምባ’ ይተናነቃቸዋል።
በኮለኔሉ እና በቁስለኛው ሠራዊት መካከል የመደማመጥ መንፈስ ስለነበር፤ አንዱ የሁኔታቸው ነገር አጠቃላይ ንግግር ካስረዳ በኋላ፤ ሌላ ተናጋሪ፤ በመቀጠል፤ ሲጋራ፤ ወርሃዊ ደሞዝ ልብስ….. ወዘተ.. ወዘተ.. የመሳሰሉ ነገሮች ያስፈልጉናል ብለው ብዙ ዝርዝሮች ካቀረበ በኋላ “አባታችን” ይህንን እንደምታደርግልን ባለ ሙሉ ተስፋ አለን፡ እናከብርሃለን! ኑርልን! ብሎ ሲጨርስ፡ ኮለኔሉ በሰሜትና በሃዘን ተውጠው ከውስጥ የያዙት ንዴት እንዳለ መገመት በሚያስችል ንግግር ተናግረው ‘የጠየቃችሁትን በሙሉ ባጭር ጊዜ ይመጣል። ካልመጣ ወዲያውኑ መልእክት ላኩልኝ’፤ካሉዋቸው በኋላ የጠየቃችኋቸው ወደ ከፍተኛ ሕክምና የመዛወር ጥያቄም አስቸኳይ ጉዳይ በመሆኑ የምችለውን አደርጋለሁ፤ ጥያቄአችሁ ወደ እሚመለከታቸው ክፍሎች ባስቸኳይ አቀርብላችኋለሁ። ተስፋ አትቁረጡ! እናሸንፋለን! ኢትዮጵያ ወይም ሞት! ብለው ተሰናብተዋቸው ሔዱ። ከሰንት ጊዜ ቆይታ አንደሆነ ባለስታውሰውም ፤ ከባድ ቁስለኞች ወደ አዲስ አበባ እና የመሳሰሉ የሕክምና ተቋማትበአይሮፕላን እየተጫኑ ለሕክምና ይወሰዱ እንደነበር አስታውሳለሁ። ሆኖም አገሪቱ የነበርዋት የሕክምና ተቋሞች ከየቦታው በመጡ ቁስለኞች ስለተሞሉ፤ ብዙዎቹ እዛው ክሳቴ ብርሃን እና ሌሎች ት/ቤት ህንጻዎች ውሰጥ ተጠልለው፤ በቂ የሕክምና እና መድሃኒት ባለመኖሩ፤ “ድሬሰር/አድቫንስ ድሬሰሮች” ተብለው በሚጠሩ ዝቅተኛ የሕክምና ባለሞያዎች እየታገዙ ከፍተኛ ስቃይ ለነበራቸው፤ ጦር ሜዳ ላይ ያሉ እየመሰላቸው ትኩሳቱ ሲበረታቸው በቅዠት ‘ፉከራ እና የ ኡኡታ ጩኸት” የሚያቀልጡ ቁስለኞች ስለነበሩ፤ ከስቃያቸው እና ከቅዠታቸው ለማስታገስ ተብሎ በድሬሰሮች አማካይነት ያለ ምንም የመድሃኒት መጠን አሰጣጥ ቁጥጥር “ናርኮቲክ” (አስካሪ አደንዛዥ የስቃይ አስታጋሽ መድሃኒቶች) ‘ቡታዘሊዶን፤ ፌኖባርቢቶል፤ ሞርፊን…..እና የመሳሰሉ እንቅልፍ የሚያስተኙ፤ የሚያሰክሩ፤ መርፌዎች፤ ማታ፤ ማታ እንዲተኙ በሚል በብዛት እየተወጉ፤ ሱስ ውስጥ የገቡ ብዙ ነበሩ።አሳዛኙ ሁኔታ እዛው ላይ አላቆመም። የሕክምና ባለሞያ እና የሚንከባከባቸው ቋሚ ሠራተኛ እጥረት ስለነበረ፤ ቁስለኞቹ ከተኙበት አልጋ ወይንም ወለል የሚያገላብጣቸው የተመደበ ቋሚ ስላልነበረ፤ “ኒሞኒያ” እና “ቤድ ሶር” (ሳይገለበጡ ባንድ ጎን ለብዙ ወር/ሳምንታት በመተኛት የሚፈጠር ጥልቀት ያለው ጎድጓዳ ቁስል) እየተሰቃዩ ብዙ ጊዜ ቆይተዋል። ጦርነቱ ቀጣይ ስለነበረ፤ ተመሳሳይ ውግያ ሲደረግ፤ የዛሬው ትግራይ ሕዝብና ወጣት በወያኔ የጎሳ ፖለቲካ ከመበከሉ በፊት (እንደዛሬ አያድርገውና) የያኔው የትግራይ ሕዝብ ሠራዊቱ በያለፈበት ገጠርም ሆነ ከተማ ተጎድቶ ሲያልፍ የማይረሳ ዜጋዊ እንክብካቤ አድርጎለታል። ይህ ዜጋዊ እና ርህራሄ የተሞላበት እንክንካቤ ወያነ ትግራይ ብዙም ሳይቆይ በሕዝብ ደም ስር ገብቶ ሕሊናው ሳያበላሸው “የኢትዮጵያ ሰንደቃለማ እንጂ ፤ እንደ ዛሬ ቄሱም መነኩሴውም ሴቱም ፤ ልጁም፤ ምሀሩም ፤ቤተክረሰትያኒቱም “የወያኔ” ባለ ኮከቡ የቻይና ኮሚነሰት ባንዴራ ሳያውለበልብ በነበረበት እንዲህ ያለ የዜግነት ሥራ መስራቱን ለመጀመርያ ጊዜ ለታሪክ ተመራማሪዎች የመዘገበ የመጀመሪያ የትግራይ ሰው መሆኔ ኩራትና ደስታ ይሰማኛል ።
አመሰግናለሁ
ጌታቸው ረዳ (ከየትግራይ ብሔረተኞች በአማራ ላይ ያላቸው ጥላቻ ከምን የመነጨ ነው?) ከሚል ከታተመው ከ2010 ዓ.ም ከገጽ 121 መጽሐፌ የተቀነጨበ) Ethiopian Semay